ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. የተካሄደው ጠቅላላ ምርጫ ዴሞክራሲያዊ፣ ፍትሐዊና በኅብረተሰቡም ዘንድ ተዓማኒ አልነበረም በማለት፣ የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ተቃውሞውን አሰማ፡፡ በዚህ ምክንያትም የምርጫውን ውጤት እንደማይቀበለው አስታውቋል፡፡
በተደጋጋሚ ሲያጋጥሙ የነበሩ እንቅፋቶችና ችግሮች በምርጫው ፍትሐዊነት፣ ዴሞክራሲያዊነትና ተዓማኒነት ላይ ችግር እየፈጠሩ መሆናቸውን በማሳሰብ በቅድመ ምርጫ ወቅት የገጠሙን ችግሮች መፍትሔ እንዲያገኙ ከፍተኛ ጥረት ቢያደርግም፣ ችግሮቻቹ መፍትሔ እንዳላገኙ ኢዴፓ ጠቁሟል፡፡ ‹‹ችግሮቹ ከመፈታት ይልቅ ይበልጥ በመባባስና ታቅዶ የሚፈጸም በሚመስል ሁኔታ ጫናዎች የፓርቲያችንን እንቅስቃሴ በሚፈታተን ደረጃ ተጠናክረው ቀርበዋል፤ ያለው ፓርቲው፣ በቅድመና በድኅረ ምርጫ ገጠሙኝ በማለት የነቀሳቸውን 22 ተግዳሮቶች በባለ አራት ገጽ መግለጫው ውስጥ አካቷል፡፡
ፓርቲው ይህን ያስታወቀው ግንቦት 29 ቀን 2007 ዓ.ም. በግዮን ሆቴል በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት ሲሆን፣ መግለጫውን የሰጡት ደግሞ የፓርቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደና ሌሎች የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ናቸው፡፡
ፓርቲው በቅድመ ምርጫውና በምርጫው ዕለት አጋጠሙኝ ካላቸው ችግሮች መካከል የዕጩዎች መዋከብ፣ ከሥራ ገበታቸው መፈናቀል፣ ከዕጩነት ራሳቸውን እንዲያገሉ ማስፈራራት፣ በአካባቢያቸው የፀጥታ ችግሮች ቢፈጠሩ ተጠያቂ እንደሚሆኑ በመግለጽ ማሸማቀቅ፣ መደለያ መስጠት፣ ማሰር፣ የምርጫ አስፈጻሚዎች በግልጽ የኢሕአዴግ የመወዳደርያ ምልክት ያለበትን ካኔቴራ ለብሰው ኢሕአዴግን ምረጡ በማለት በአደባባይ ሲቀሰቅሱ ምርጫ ቦርድ በዝምታ መመልከቱ፣ እንዲሁም ተቃዋሚዎች ፀረ ሰላምና የልማት ሒደታችንን ያደናቀፉ ኃይሎች ናቸው በማለት በአንድ ለአምስት አደረጃጀት በየመንደሩ የጥላቻ ሐሳቦችን በኅብረተሰቡ ውስጥ መበተን ተጠቃሾች ናቸው ሲል ኢዴፓ ገልጿል፡፡
በተጨማሪም ታዛቢዎችን በመደለል እንዳይታዘቡ ማድረግ፣ ማስፈራራትና ይህን ሁሉ ተቋቁመው ወደ ምርጫ ጣቢያ የሄዱትን ማባረርና ማሰር፣ በምርጫ ጣቢያ ውስጥ የታጠቁ የፖሊስና የመከላከያ ሠራዊት አባላት በመገኘት መራጩን ሕዝብ በማሸማቀቅ ተፅዕኖ ውስጥ መክተት፣ እንዲሁም በቅሬታ አቀራረብ ደንብና አሠራር መሠረት ቅሬታዎችን ለመቀበል በየትኛውም ደረጃ ያሉ የምርጫ አስፈጻሚ አካላት ፈቃደኛ አለመሆናቸው በምርጫው ዕለት የገጠሙት ችግሮች እንደሆኑ ኢዴፓ አስታውቋል፡፡
‹‹በሒደቱም ሆነ በምርጫው ዕለት የተፈጸሙትን ድርጊቶች በነቂስ የመረመረው የኢዴፓ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ፣ ምርጫው በየትኛውም መመዘኛ ነፃ፣ ፍትሐዊና ዴሞክራሲያዊ እንዳልነበር አረጋግጧል፤›› በማለት ሒደቱንና ውጤቱን ፓርቲው ተቃውሟል፡፡
‹‹ኢትዮጵያ ውስጥ ከሌላው ዓለም በተለየና በላቀ ሁኔታ የፖለቲካ አስተሳሰብ ልዩነት ያለ ቢሆንም፣ የምርጫው ውጤት ግን ይህንን ፈጽሞ በማያሳይ ሁኔታ ተጠናቋል፡፡ በዓለማችን ዴሞክራሲያዊ ምርጫም ሆነ የይስሙላ ምርጫ በሚያካሂዱ አገሮች ላይ እንደዚህ ዓይነት ውጤት ተመዝግቦ አያውቅም፡፡ ውጤቱም ሆነ ሒደቱ ምርጫው ዴሞክራሲያዊ፣ ፍትሐዊና ነፃ አለመሆኑን ያረጋገጠ ነው፤›› በማለት አትቷል፡፡
ይህን መግለጫ ለመስጠት ለምን እንደዘገዩ ከሪፖርተር ጥያቄ የቀረበላቸው የፓርቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደ፣ ‹‹ፓርቲያችን ሕግ መከበር፣ በመርህ ላይ የተንተራሰ ሥራዎች መሠራት እንዳለባቸው ይገነዘባል፡፡ እንደ ሌሎች ፓርቲዎች ቀድመን መግለጫዎችን ያልሰጠንበት ምክንያት በጥናት ላይ መመሥረትና ምክንያታዊ መሆን ስላለብን፣ እንዲሁም ደግሞ ከሁሉም የአገሪቱ ክልሎች የሚደርሱን መረጃዎች እውነትና ተዓማኒ መሆናቸውን እስክናረጋግጥ ሒደቱ ጊዜ በመውሰዱ ነው፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
ኢዴፓ ፓርቲው የጉዳዩ ባለቤት የሆነው ሕዝብ ‘እኔ ምን አገባኝ’ ከሚልና ከዳር ተመልካችነት ስሜት ራሱን በማራቅ፣ ለዚህች አገር ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ የሚያደርገውን ሁለንተናዊ አስተዋጽኦ ይበልጥ እንዲያጠናክር ጥሪ አቅርቧል፡፡