በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን በተመለከተ በሰጡት መግለጫ ማብራሪያ እንዲሰጡ በኢትዮጵያ መንግሥት መጠየቃቸው ታወቀ፡፡
በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ማይክ ሬነር የካቲት 12 ቀን 2010 ዓ.ም. በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተጠርተው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን በተመለከተ ለሰጡት አስተያየት፣ ማብራሪያ እንዲሰጡ መጠየቃቸውን የሪፖርተር ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊዎች የአምባሳደሩ አስተያየት ጠቃሚና አጋዥ እንዳልነበር፣ ችግር ሲኖር ሐሳብ በመለዋወጥና በመወያየት በጋራ መፍታት ሲቻል መግለጫ ማውጣቱ ለሁለቱ አገሮች ጠቀሜታ እንደሌለው ለአምባሳደሩ ገለጻ እንዳደረገላቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡
አምባሳደሩም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርን ሐሳብ እንደሚረዱና አስተያየታቸውም በአሉታዊ ከማሰብ እንዳልሆነ መግለጻቸውን፣ ወደፊት በመመካከር ለመሥራት ፍላጎታቸው እንደሆነ መናገራቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ ኢትዮጵያ ያወጣችውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በተመለከተ አሜሪካ፣ የአውሮፓ ኅብረትና የእንግሊዝ መንግሥት መግለጫ አውጥተዋል፡፡ ሦስቱም ኢትዮጵያ ያወጣችውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በፅኑ የተቃወሙ ሲሆን፣ ይህን በተመለከተ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከፍተኛ ኃላፊ አስተያየታቸውን እንዲሰጡ ተጠይቀው ‹‹አስተያየቱ ጠቃሚና አጋዥ አይደለም›› ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ባወጀ በሰዓታት ልዩነት ውስጥ በኢትዮጵያ የአሜሪካ መንግሥት መግለጫ ያወጣ ሲሆን፣ በመግለጫው እንደተገለጸው ኢትዮጵያ ያወጣችውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አሜሪካ በፅኑ ተቃውማለች፡፡
በሚኒስትሮች ምክር ቤት ዓርብ የካቲት 9 ቀን 2010 ዓ.ም. ለስድስት ወራት የሚቆይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መታወጁ የሚታወስ ሲሆን፣ ይህን አዋጅ የእንግሊዝ መንግሥትም ተቃውሞታል፡፡
በእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ሰሞኑን ባወጣው መግለጫ፣ ኢትዮጵያ ያወጣችው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ተገቢ አይደለም ብሏል፡፡ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ኢንቨስትመንት በመሳብ በርካታ ሥራዎችን እያከናወነች ባለችበት ወቅት፣ ይህን ዓይነት ዕርምጃ መውሰድ ትክክል እንዳልሆነ መግለጫው ጠቁሟል፡፡
መንግሥት እስረኞችን እየፈታና ሕዝቡ ለሚጠይቀው ጥያቄ ምላሽ እየሰጠ ባለበት ጊዜ፣ ይህን መሰል ዕርምጃ መውሰዱ ተገቢ እንዳልሆነ በመግለጫው ተጠቁሟል፡፡ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የታወጀው ለረዥም ጊዜያት እንደሆነና ይህ ደግሞ በአገሪቱ የከፋ ችግር ሊያደርስና የዜጎችን ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ለመጣስ መደላድል ሊሆን እንደሚችል በመግለጫው ተጠቅሷል፡፡
ኢትዮጵያና እንግሊዝ በኢንቨስትመንት፣ በንግድና በተለያዩ ዘርፎች ግንኙነት ያላቸው አገሮች ናቸው፡፡
የአውሮፓ ኅብረት በበኩሉ ኢትዮጵያ ያወጣችውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተቃውሟል፡፡ በአውሮፓ ኅብረት የአፍሪካ ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ባወጣው መግለጫ እንዳመለከተው፣ ኢትዮጵያ ያወጣችው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በምንም መሥፈርት ተቀባይነት የለውም ብሏል፡፡