Sunday, December 3, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

አንድ በውጭ የሚኖር ተቃዋሚ ለክቡር ሚኒስትሩ ስልክ ደወለላቸው

[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ ኢንቨስተርን ሆቴል ቀጥረው እየጠበቁት ነው]

  • ይቅርታ ክቡር ሚኒስትር አረፈድኩኝ አይደል?
  • አሥራ አምስት ደቂቃ እኮ አስቀመጥከኝ፡፡
  • መንገድ ተዘጋግቶብኝ ነው፡፡
  • በሌለኝ ሰዓት ከየት አመጣዋለሁ፡፡
  • በጣም ይቅርታ ክቡር ሚኒስትር፣ ከውጭ እንግዶች መጥተውብኝ ነው፡፡
  • የምን የውጭ እንግዳ?
  • አገራችን ውስጥ ኢንቨስት የሚያደርጉ ናቸዋ፡፡
  • በዚህ ወቅት አገራችን ኢንቨስት ማድረግ የሚፈልጉ ባለሀብቶች አሉ?
  • አይ ያው ለረዥም ጊዜ ስንነጋገርበት የነበረና ሲጠና የነበረ ፕሮጀክት ነው፡፡
  • አሁንም ኢንቨስተሮች በመንግሥታችን ላይ እምነት አላቸው ማለት ነው?
  • በሚገርም ሁኔታ እኛም ይኼንኑ ነበር ስንወያይ የነበረው፡፡
  • እና እዚህ ኢንቨስት ማድረግ ይፈልጋሉ?
  • አሁን አሁን እንኳን እነሱን ማሳመን እየከበደኝ ነው፡፡
  • ምኑ ነው የከበደህ?
  • እዚህ ኢንቨስት ማድረግ አይፈልጉም፡፡
  • ለምን?
  • ይኸው ሦስት ዓመት ሙሉ ብጥብጥ ስለነበር እምነታቸውን አጥተዋል፡፡
  • ለዚህች አገር እኮ ይኼ የሰላምና መረጋጋት ጉዳይ ዋነኛ ችግር እየሆነ ነው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር እነዚህ ሰዎች ለአገሪቱ ምን ያህል ጥቅም ያለው ፕሮጀክት ነበር ያሰቡት፡፡
  • ምን ታደርገዋለህ?
  • ባይገርምዎት ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ ከሁለት ኢንቨስተሮች ጋር ለመሥራት ተስማምተን እንደዚሁ ፈረሰብኝ፡፡
  • ምን ትቀልዳለህ?
  • በኢንዱስትሪ ፓርኮቻችን ሥራ ሊጀምሩ አስበው በፀጥታው ሁኔታ ተደናግጠው ነው የሄዱት፡፡
  • እነሱ እንኳን አይጠቅሙንም፡፡
  • እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
  • እኛ ቱሪስት ኢንቨስተር አንፈልግም፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • በየአገሩ እየዞሩ ይጠቅመኛል አይጠቅመኝም ብለው የሚሠሩትን ሳይሆን የምንፈልገው ከእኛው ጋር ሁሉን ነገር የሚጋፈጡትን ነው፡፡
  • አልገባኝም ክቡር ሚኒስትር?
  • እነዚህ ኪራይ ሰብሳቢዎች ናቸው፡፡
  • እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
  • እንደዚህ ዓይነቶቹ ኢንቨስተሮች በየቀኑ ነው እኔ ጋ ቢመጡም ፊት አልሰጣቸውም፡፡
  • ለምን ክቡር ሚኒስትር?
  • እነዚህ ወዲያው በልተው ወዲያው መጥፋት ነው የሚፈልጉት፡፡
  • ታዲያ ምን ዓይነቶቹን ነው እኛ የምንፈልጋቸው?
  • ከእኛ ጋር በችግሩም በደስታውም ጊዜ የሚሆኑትን ነዋ፡፡
  • አሁን እኮ ደስታ የሚባል ነገር ጠፍቶ ይኸው ለሦስት ዓመት ችግር ነው የሰማነው፡፡
  • አየህ ሊነጋ ሲል ይጨልማል ስለሚባል ለዚያ ነው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር እርስዎን በሚኒስትርነት አውቅዎታለሁ፣ በኢንቨስተርነት አውቅዎታለሁ፣ በነብይነት ግን አላውቅዎትም፡፡
  • ከአንተም ጋር ተደፋፈርን ማለት ነው?
  • ኧረ እኔ ለጨዋታ ነው፣ እኔ ለነገሩ ችግር የለብኝም፡፡
  • ምን እያልክ ነው?
  • ዛሬ ከኢሕአዴግ ጋር እንደ ሠራሁት፣ ነገም ሌላ ከመጣ ከእሱም ጋር መሥራት አይከብደኝም፡፡
  • ምን አልክ አንተ?
  • ምነው ክቡር ሚኒስትር?
  • እንዴት እንደዚህ ልታስብ ትችላለህ?
  • ምን ችግር አለው ክቡር ሚኒስትር፣ እኔ እኮ ነጋዴ ነኝ፡፡
  • በዚህ ሥርዓት አይደለም እንዴ ከአፈር ተነስተህ እዚህ የደረስከው?
  • እሱንማ አልክድም ክቡር ሚኒስትር፣ ብዙ ተጠቅሜያለሁ፡፡
  • ታዲያ እንዴት ከሌላ መንግሥትም ጋር ቢሆን መሥራት እችላለሁ ትላለህ?
  • ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር ዝግጁ ነኝ ስላሉ እሱንም ማሰቡ አይከፋም ብዬ ነዋ፡፡
  • እኔማ መቼ ሰላማዊ የሥልጣን ሽግግርን ተቃወምኩ?
  • እና ለሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር ዝግጁ ነዎት?
  • በሚገባ እንጂ፣ እኔን ያስፈራኝ ሌላኛው ሽግግር አይኖርም ብዬ ነው፡፡
  • ሌላኛው ሽግግር ምንድነው?
  • ሰላማዊ የሀብት ሽግግር!

[አንድ በውጭ የሚኖር ተቃዋሚ ለክቡር ሚኒስትሩ ስልክ ደወለላቸው]

  • ሄሎ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • የእኛ ኪራይ ሰብሳቢ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር በቃ አበቃላችሁ እኮ፡፡
  • ምኑ ነው ያበቃው?
  • ተበላችሁ እኮ፡፡
  • ምኑን ነው የተበላነው?
  • ቁማሩን ተበላችሁ፡፡
  • ምን እያወራህ እንደሆነ አልገባኝም?
  • ይኸው ሕዝቡ እስረኛ አስፈታችሁ፣ አሁን ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ሊያስቀይራችሁ ነው፡፡
  • እናንተ ለዚህ ነው ይህችን አገር ለመምራት ብቃቱም፣ አቅሙም የላችሁም የምንለው፡፡
  • ምን እያሉ ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • እኛ እኮ እስረኞቹንም ለመፍታት ሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሥልጣን እንዲወርዱ ከተስማማን ቆየን፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር እጃችሁን ተጠምዝዛችሁ እንጂ ተስማምታችሁ አይደለም፡፡
  • ስነግርህ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሥልጣናቸውን መልቀቅ ከፈለጉ ቆይተዋል፤ እኛ እስክንተካቸው ነበር የቆዩት፡፡
  • እናንተማ መቼም እንደማታምኑ አውቃለሁ፡፡
  • ስማ ምንም ይፈጠራል ብለህ እንዳታስብ፡፡
  • እሱንስ እንኳን ይተውት፡፡
  • ማለት?
  • እኔ አሁን ጮቤ እየረገጥኩ ነው፡፡
  • ለምኑ?
  • በቃ ክቡር ሚኒስትር አብቅቶላችኋል፣ እኔም ሻንጣዬን እያዘጋጀሁ ነው፡፡
  • ምን ለማድረግ?
  • አገሬ ለመግባት ነዋ፡፡
  • እስቲ አታስቀኝ?
  • ይኸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር ይኖራል እያሉ አይደል እንዴ?
  • ዶሮ ብታልም ጥሬዋን አሉ፡፡
  • አገሬ መግባቴ አይቀርም ስልዎት፡፡
  • ለነገሩ ይኼንን ማሰቡ አይከፋም፡፡
  • እንዴት?
  • አንድ ቀን አገራችሁ ትገቡ ይሆናል፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር እርስዎም ውስጥዎት ያውቀዋል በቅርቡ መሆኑ አይቀርም፡፡
  • በነገራችን ላይ አሜሪካ ጥሩ ቤት አለህ አሉ፡፡
  • እሱንም ትቼው እምጣለሁ፡፡
  • እኔም እዚህ ጥሩ ቤት ስላለኝ አንድ ነገር አስቤ ነበር፡፡
  • ምን ክቡር ሚኒስትር?
  • ብንቀያየር ብዬ ነዋ፡፡
  • ምኑን?
  • ቤታችንን!

[ለክቡር ሚኒስትሩ አንድ ደላላ ይደውልላቸዋል]

  • ክቡር ሚኒስትር ተቸገርን እኮ፡፡
  • ምንድነው የተቸገርከው?
  • ምንም ሥራ መሥራት አልተቻለም፡፡
  • ምን ሆንክ ደግሞ?
  • አንዴ መንገድ ተዘግቶ አገር ይታመሳል፡፡
  • ምን ይኼ አዲስ ነገር ነው?
  • ሰላም ነው ብለን ደግሞ ሥራ ስንጀምር በድጋሚ ይታመሳል፡፡
  • ታዲያ ምን ይጠበስ?
  • መንግሥት ምን እየሠራ ነው?
  • ሥራውን እየሠራ ነዋ፡፡
  • ይኸው ንግዱም ቆሟል፣ ሁሉም እንቅስቃሴ ቆሟል፡፡
  • ስማ እኔም ንግዱ ውስጥ ስላለሁ ሁሉን ነገር ጠንቅቄ አውቀዋለሁ፡፡
  • ታዲያ ትንሽ አይቆጭዎትም?
  • ለዚያ አይደል እንዴ መፍትሔ ለማምጣት ጠብ እርግፍ እያልን ያለነው፡፡
  • ግን ምንም ዓይነት መሻሻል እያየን አይደለም፡፡
  • እንቅልፍ አጥተን ነው እየሠራን ያለነው፡፡
  • የሚመስለው ግን አውቃችሁ የተኛችሁ ነው፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • ብትቀሰቀሱ አልሰማም አላችኋ?
  • ሰውዬ ልትጨቀጭቀኝ ነው የደወልከው?
  • እሱማ አንድ ጉዳይ ነበረኝ፡፡
  • የምን ጉዳይ?
  • በአካል ተገናኝተን ነው ማውራት ያለብን፡፡
  • ጫፉን ንገረኛ?
  • መሬት የሚፈልጉ ሰዎች ነበሩ፡፡
  • በዚህ ጊዜም መሬት እየደለልክልኝ ነው?
  • እንዲያውም ማጧጧፍ ያለብን በዚህ ወቅት ነው፡፡
  • ለምን?
  • ነገ ምን እንደሚፈጠር አይታወቅማ፡፡
  • በቃ ይኸው ነው ጉዳይህ?
  • በዚያውም እንኳን አደረሰዎት ለማለት ነው?
  • ፋሲካ ገና አይደል እንዴ?
  • ኧረ ለዓመታዊው በዓላችን ነው፡፡
  • ለምኑ?
  • ለአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ!

[ክቡር ሚኒስትሩ የፓርቲ ስብሰባ ውስጥ ናቸው]

  • ክቡር ሚኒስትር በጠቅላይ ሚኒስትሩ መልቀቅ ምን ያስባሉ?
  • የጠቅላይ ሚኒስትሩ ውሳኔ ትክክል ነው ባይ ነኝ፡፡
  • እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
  • ሌሎቻችንም እንደ አርዓያ ልንከተለው የሚገባ ነዋ፡፡
  • ይኼ ነው ሐሳብዎ?
  • ሊታሰብበት የሚገባው ጉዳይ ሌላ ነው፡፡
  • ምንድነው እሱ?
  • የሚተካቸው ሰው ማን መሆን አለበት የሚለው ነዋ፡፡
  • እርስዎ ማን ይተካቸው ይላሉ?
  • ሕዝቡ እውነተኛ ለውጥ ነው የሚፈልገው፡፡
  • እሱማ ትክክል ነው፡፡
  • ስለዚህ በእኔ አስተያየት ቀጣዩ ጠቅላይ ሚኒስትር ከእሳቸው የሚያጥር መሆን አለበት፡፡
  • ምን?
  • ከዚያም ባለፈ መነጽር የማያደርግ ቢሆን ይሻላል፡፡
  • አበዱ ማለት ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ሕዝቡ እውነተኛ ለውጥ ነው የሚፈልገው ስላችሁ?
  • እና ይኼ ነው እውነተኛ ለውጥ ለእርስዎ?
  • ከቁመናው ባሻገር ራሰ በረሃ ሆኖ የደም ግባት ቢኖረው ይሻላል ባይ ነኝ፡፡
  • ቀጥለው እኔን ምረጡኝ እንዳይሉ?
  • ኧረ በፍጹም፡፡
  • የሚመረጠው ሰው እኮ ለቁንጅና ውድድር አይደለም የሚፈለገው?
  • እሱንማ አውቃለሁ፡፡
  • የሚመረጠው ሰው አገሪቷን ከገባችበት ቀውስ ሊያወጣት የሚችል መሪ መሆን አለበት፡፡
  • ለዚያ ነው እኮ ሰውየው እነዚህን ነገሮች ማሟላት ያለበት፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ስለጤነኝነትዎ እየተጠራጠርን ነው፡፡
  • እንግዲህ መስማማት ካልቻልን አንድ አስታራቂ ሐሳብ ላቅርብ፡፡
  • ምንድነው እሱ?
  • የሚፈለገው መሪ ኢትዮጵያን ወደ አንድነት የሚያመጣ መሆን አለበት፡፡
  • ለዚያ አይደል እንዴ እየተወያየን ያለነው፡፡
  • ስለዚህ በጋዜጣ ማውጣት ነዋ፡፡
  • ምንድነው የምናወጣው
  • የሥራ ማስታወቂያ!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

በዓለም አቀፍ ደረጃ ሕይወታቸውን በኤድስ ምክንያት ላጡ ሰዎች 35ኛ ዓመት መታሰቢያ

ያለፍንበትን እያስታወስን በቁርጠኝነት ወደፊት እንጓዝ - በኧርቪን ጄ ማሲንጋ (አምባሳደር) በየዓመቱ...

እዚያ ድሮን… እዚህ ድሮን…

በዳንኤል ካሳሁን (ዶ/ር) ተዓምራዊው የማዕበል ቅልበሳ “በሕግ ማስከበር” ዘመቻው “በቃ የተበተነ...

ለፈርጀ ብዙ የማንነት ንቃተ ህሊናችን የሚጠቅሙ ጥቂት ፍሬ ነገሮች

በበቀለ ሹሜ ከጨቅላነት ጅምሮ ያለ የእያንዳንዳችን የሰብዕና አገነባብ ከቤተሰብ እስከ...

በሲሚንቶ ፋብሪካ ላይ የታየው ተሞክሮ በሌሎች ምርቶች ላይም ይስፋፋ!

ሰሞኑን በኢትዮጵም ሆነ በአፍሪካ ደረጃ ግዙፍ ስለመሆኑ የተነገረለትን የለሚ...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ የሩብ ዓመት የሥራ አፈጻጸማቸውን ለተከበረው ምክር ቤት ካቀረቡ በኋላ ከምክር ቤቱ አባላት የሚነሱ ጥያቄዎችን እየተቀበሉ ማብራሪያ በመስጠት ላይ ናቸው]

ክቡር ሚኒስትር መንግሥት ለሕዝብ ይፋ ያደረገው ነገር ከምን እንደደረሰ ቢያብራሩልን? ምንድነው ይፋ ያደረገው? ጥያቄውን ትንሽ ቢያብራሩት? ከአራት ዓመት በፊት በኦጋዴን አካባቢ ነዳጅ መገኘቱን ለሕዝብ በቴሌቪዥን አብስሮ...

[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ የካቢኔና የማክሮ ኢኮኖሚ ኮሚቴ አባል የሆኑ ከፍተኛ አመራር የሚያቀርቡትን ቅሬታ እያደመጡ ነው] 

ክቡር ሚኒስትር እየሆነ ያለው ነገር በእጅጉ ስላሳሰበኝ ነው በአካል አግኝቼ ላነጋግርዎት የፈለግኩት። ጥሩ አደረግህ፣ ምን አሳሳቢ ነገር ገጥሞህ ነው? ክቡር ሚኒስትር ተወያይተንና ተግባብተን ያስቀመጥናቸው አቅጣጫዎች፣ በተለይም...

[ጉባዔው በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ክቡር ሚኒስትሩን ለመጠየቅና ምላሽና ማብራሪያቸውን ለማድመጥ ተሰብስቧል። የጉባዔው አባላትም ማብራሪያ የሚሹ ጥያቄዎቻቸውን ለክቡር ሚኒስትሩ እያቀረቡ ነው]

ክቡር ሚኒስትር፣ ይህ ጉባዔ ለሚያነሳቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ለመስጠት በመካከላችን ስለተገኙ አመሰግናለሁ። ክቡር ሚኒስትር፣ ኢትዮጵያ ባለፈው ዓመት የብሪክስ አባል እንድትሆን የሰጡት በሳል አመራር የሚደነቅ ነው። አገራችን...