የኢትዮጵያ፣ የግብፅና የሱዳን መንግሥታት የታላቁ የህዳሴ ግድብን ለመገምገም የቋቋሙት የቴክኒክ ኮሚቴ ሰኔ 8 ቀን 2007 ዓ.ም. በካይሮ እንደሚገናኙ ተሰማ፡፡
የቴክኒክ ኮሚቴው ከእያንዳንዱ አገር አራት ባለሙያዎች የተወከሉበት ሲሆን፣ ዓላማውም ከዚህ ቀደም ግድቡን የገመገመው ዓለም አቀፍ የባለሙያዎች ቡድን ሦስቱ አገሮች በጋራ እንዲተገብሯቸው ያቀረቧቸውን ሁለት ምክረ ሐሳቦች ዕውን ማድረግ ነው፡፡ ሁለቱን ምክረ ሐሳቦች ተግባራዊ ለማድረግ በወጣው ዓለም አቀፍ ጨረታ ከተወዳደሩት አምስት ኩባንያዎች መካከል፣ ሁለት ኩባንያዎች ማለትም የፈረንሣዩን ቢአርኤል ግሩፕና የኔዘርላንዱ ዴልታሪዝ በመጨረሻ መቅረታቸው ይታወሳል፡፡
በሚያዝያ ወር በአዲስ አበባ የተገናኙት የሦስቱ አገሮች የኮሚቴ አባላት ሁለት ቀናት የፈጀ ውይይት በማድረግ የፈረንሣዩ ቢኤርኤል ግሩፕ አጠቃላይ ጥናቶችን በበላይነት እንዲያከናውን፣ የኔዘርላንዱ ዴልታሪዝ ደግሞ ከፈረንሣዩ ኩባንያ የተወሰኑ ሥራዎች እንዲሰጠው ተስማምተዋል፡፡
በዚህ ውሳኔ መሠረት ሁለቱ ኩባንያዎች ውሳኔውን እንዲያውቁት ከተደረገ በኋላ፣ ረዥም ቀናት ፈጅተው በግንቦት ወር የቴክኒክ ሰነድ ለኮሚቴው አስረክበዋል፡፡
ይኼ ሰነድ ምን እንደሚያትት ባይታወቅም፣ የሦስቱ አገሮች የኮሚቴ አባላት በዚሁ የቴክኒክ ሰነድ ላይ ከሰኞ ጀምሮ እንዲሚወያዩ ታውቋል፡፡
የዓለም አቀፍ አጥኚዎች ቡድን ቀደም ሲል የሰጠው ምክረ ሐሳብ የግድቡ ኃይድሮ ሲሙሌሸን ሞዴል ማለትም ግድቡ ውኃ የሚይዝበትና የሚለቅበት በተለያዩ የዝናብ ወቅቶች ምን መሆን አለበት የሚለው አንዱ ሲሆን፣ የግድቡ ግንባታ በሦስቱ አገሮች ላይ ሊፈጥረው የሚችለውን የአካባቢያዊና የማኅበራዊ ጥናት ተፅዕኖ ግምገማ ደግሞ ሁለተኛው ምክረ ሐሳብ ነው፡፡