Monday, October 2, 2023
- ማስታወቂያ -
- ማስታወቂያ -

ኢትዮጵያና ሱዳን ነፃ የንግድ ቀጣና ለመመሥረት ተስማሙ

ተዛማጅ ፅሁፎች

ኢትዮጵያና ሱዳን የሁለቱ አገር ሕዝቦች ያለቀረጥና ታክስ መገበያየት የሚችሉበትን ነፃ የንግድ ቀጣና ለማቋቋም ከስምምነት ላይ ደረሱ፡፡

ሰኔ 7 ቀን 2007 ዓ.ም. የሁለቱ አገሮች የጋራ የቴክኒክ ኮሚቴ ባደረገው ስብሰባ፣ በሁለቱም አገሮች ነፃ የንግድ ቀጣናው እንዲቋቋምና በእነዚህ የንግድ ቀጣናዎች የሁለቱም አገሮች ገንዘብ መገበያያ እንዲሆን መስማማታቸውን ዘገባዎች አመልክተዋል፡፡

የሱዳን የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ አብዱልራህማን ዲራር ለመገናኛ ብዙኃን እንደገለጹት፣ የንግድ ቀጣናዎቹን ከማቋቋም በተጨማሪ የሁለቱ አገሮች የመገበያያ ገንዘቦች ዝውውር መኖሩም ለሁለቱ አገሮች የንግድ ልውውጥ እንደሚጠቅም ተናግረዋል፡፡

በሁለቱ አገሮች የሚቋቋሙትን ነፃ የንግድ ቀጣናዎችን ምቹ ቦታ የሚለይ አማካሪ ኩባንያ እንደሚቀጠር፣ ኩባንያውም በተቀጠረ በ45 ቀናት ውስጥ ውጤቱን ለጋራ የቴክኒክ ኮሚቴው እንደሚያቀርብ መረጃው ያመለክታል፡፡

የጋራ ቴክኒክ ኮሚቴው ከነፃ የንግድ ቀጣናው በተጨማሪ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሱዳን ቅርንጫፉን እንዲከፍት፣ እንዲሁም የሱዳን ባንኮች በኢትዮጵያ ጽሕፈት ቤታቸውን እንዲከፍቱ ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሌሎች አገሮች ቅርንጫፎቹን መመሥረት የሚችል ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅትም በደቡብ ሱዳን ቅርንጫፎች ያሉት መሆኑ ይታወቃል፡፡

በኢትዮጵያ ግን የውጭ አገር ባንኮች የባንክ አገልግሎት መስጠት እንደማይችሉ በሕግ ተከልክሏል፡፡ በመሆኑም ሊከፈት የሚችለው የሱዳን ባንክ ጽሕፈት ቤት የማማከር አገልግሎትና ሌሎች ባንክ ነክ ያልሆኑ አገልግሎቶችን ነው መስጠት የሚችለው፡፡

የሁለቱ አገሮች የቴክኒክ ኮሚቴ ከዚህ ቀደም በተስማማው መሠረት፣ ሁለቱን አገሮች በየብስ የሚያገናኝ ትራንስፖርት ለመጀመር ከወራት በፊት ስምምነት መፈረሙ ይታወሳል፡፡

spot_img
- Advertisement -spot_img

የ ጋዜጠኛው ሌሎች ፅሁፎች

- ማስታወቂያ -

በብዛት ከተነበቡ ፅሁፎች