Monday, December 4, 2023
- ማስታወቂያ -
- ማስታወቂያ -

የግሉን ዘርፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ግዙፍ የመሠረተ ልማት ባለቤት የሚያደርገው ዕቅድ ተዘጋጀ

ተዛማጅ ፅሁፎች

መንግሥት በታሪኩ ለመጀመርያ ጊዜ የግል ኩባንያዎች በግዙፍ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች እንዲሳተፉ ሊፈቅድ ነው፡፡ ከሚቀጥለው ዓመት ጀምሮ ተግባራዊ የሚደረገው ሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ የግል ኩባንያዎች የፍጥነት መንገድ መገንባት፣ ኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጨትና ለመስኖ አገልግሎት የሚውሉ ግድቦች መገንባት እንዲችሉ ፈቅዷል፡፡

የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ሕግ ዲፓርትመንት ኃላፊ አቶ ዋሲሁን አባተ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ የመንግሥትና የግሉ ዘርፍ ትብብር ትልቅ ቦታ ተሰጥቶታል፡፡

በዚህ መሠረት የግል ኩባንያዎች በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ውስጥ ትልቅ ድርሻ እንዲኖራቸው ከማድረጉ ባሻገር፣ ከዚህ ቀደም ተሳታፊ ባልሆኑባቸው የመሠረተ ልማት ዘርፎች ውስጥ ተዋናይ እንዲሆኑ እየተመቻቸ መሆኑን አቶ ዋሲሁን ገልጸዋል፡፡

መንግሥት በቅርቡ ይፋ በሚያደርገው የአምስት ዓመት ዕቅድ ሰነድ በተዘረዘረው መሠረት፣ የግል ባለሀብቶች የመሠረተ ልማት ግንባታዎችን አካሂደው አገልግሎት በመስጠት የንግድ ሥራ ማካሄድ ያስችላቸዋል፡፡

ይህንን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል የሕግ ማዕቀፍ እየተዘጋጀ ነው፡፡ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር የሕግ ዲፓርትመንት ባዘጋጀው የሕግ ማዕቀፍ ላይ የተቀጠሩ አማካሪ ድርጅቶች አስተያየት እየሰጡ መሆኑ ታውቋል፡፡

ረቂቅ ሕጉ ከፀደቀ በኋላ የግል ኩባንያዎቹ በሚፈልጓቸው የመሠረተ ልማት ዘርፎች የሚሰማሩ ሲሆን፣ ከአዋጁ ባሻገር አሠራሩን የሚደግፍ ደንብ እንደሚዘጋጅም ታውቋል፡፡

በኢትዮጵያ የመንገድና የኃይል ማመንጫ ባለቤት የሆነ የግል ኩባንያ የለም፡፡ ለመስኖ አገልግሎት የሚውል ግድብም ቢሆን ከራስ ፍጆታ አልፎ ለኪራይ አገልግሎት ያዋለ የግል ኩባንያ እንደሌለ ይታወቃል፡፡ እየተዘጋጀ ባለው ዕቅድ ግን አንድ ኩባንያ በራሱ ወጪ የፍጥነት መንገድ ገንብቶ ለተጠቃሚዎች ክፍት በማድረግ መንገድ እንደሚችል ተቀምጧል ተብሏል፡፡

በኢትዮጵያ ብቸኛው የፍጥነት መንገድ ከአዲስ አበባ አዳማ ድረስ የተዘረጋው 80 ኪሎ ሜትር ባለ ስድስት ረድፍ መንገድ ብቻ ነው፡፡ በቻይናው ሲሲሲሲ ኩባንያ የተሠራው ይህ መንገድ የሚተዳደረው መንግሥት ባቋቋመው የልማት ድርጅት ሲሆን፣ መንገዱ የአገልግሎት ክፍያ እየተከፈለበት አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡

‹‹ከእነዚህ ግንባታዎች የግሉ ዘርፍ ልምድ በመውሰድ የራሱን ግንባታ ሊያካሂድ ይችላል፤›› በማለት አቶ ዋሲሁን ገልጸዋል፡፡

በኢትዮጵያ በብቸኝነት የኤሌክትሪክ ኃይል የማመንጨት ሥልጣን ያለው መንግሥታዊው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ነው፡፡ የገጠሩን የአገሪቱ ክፍል የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ለማሻሻል ብሔራዊ ኃይል ማስተላለፊያ ከተዘረጋበት መስመር 15 ኪሎ ሜትር ርቀው የሚገኙ የኅብረተሰብ ክፍሎች፣ ከተለያዩ አማራጭ የኃይል አቅርቦቶች የኤሌክትሪክ ኃይል እንዲያመነጩ ሲደረግ ቆይቷል፡፡ የመነጨውን ኃይል የሚያስተዳድሩትም ያመነጩት የኅብረተሰብ ክፍሎች ናቸው፡፡

በአሁኑ ዕቅድ ግን የታሰበው የግሉ ዘርፍ የኤሌክትሪክ ኃይል በማመንጨት በሚኒስትሮች ምክር ቤት በሚወሰን ታሪፍ ለኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲያቀርብ ይደረጋል ተብሏል፡፡

መንግሥት በሁለተኛው የዕቅድ ዘመን ራሱን የቻለ 12 ሺሕ ሜጋ ዋት ኤሌክትሪክ ለማመንጨት አቅዷል፡፡ ይህ ዕቅድ ይተገበራል ተብሎ የሚጠበቀው የግሉ ዘርፍ ተዋናዮች ከተሳተፉ ብቻ ነው ተብሎ በመታመኑ፣ በተለይ በአሁኑ ወቅት በግድብ ግንባታ የተሰማሩ ኩባንያዎች ተስፋ እንደተጣለባቸው ተመልክቷል፡፡

በሌላ በኩል ለመስኖ ልማት አመቺ በሆኑ ወንዞች ላይ የግሉ ዘርፍ ግድብ እንዲገነባ ሁኔታዎች ይመቻቻሉ ተብሏል፡፡ በግድቡ ዙርያ በእርሻ ሥራ የተሰማሩ ኩባንያዎች ውኃውን እንዲጠቀሙ እየተደረገ የአገልግሎት ክፍያ ይፈጽማሉ ተብሏል፡፡

በአሁኑ ወቅት ይህንን ሥራ እየሠራ የሚገኘው የአዋሽ ተፋሰስ ባለሥልጣን ብቻ ነው፡፡ ባለሥልጣኑ በአዋሽ ወንዝ ላይ ሥልጣን የተሰጠው በመሆኑ ከአዋሽ ወንዝ ጠልፈው የሚጠቀሙ አልሚዎች ኪራይ እንዲከፍሉ ሲደረግ ቆይቷል፡፡

አሁን በተያዘው ዕቅድ፣ የግል ኩባንያዎች የግድብ ግንባታ በማካሄድ የውኃው አገልግሎት ኪራይ ማስከፈል እንዲችሉ ይደረጋል፡፡

መረጃዎች እንደሚጠቁሙት መንግሥት በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ በዋናነት ለማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ትኩረት ሰጥቷል፡፡ ይህንን ዕቅድ ለማሳካት በዋናነት የግሉን ዘርፍ በማሳተፍ፣ አገሪቱን ከአላስፈላጊ ብድር ለመታደግ ተስፋ እንደተደረገ ተመልክቷል፡፡ የልማታዊ መንግሥት ሞዴል በሚከተሉ አገሮች የግሉ ዘርፍ መንግሥት በሚያስቀምጠው አቅጣጫ መሠረት በኢኮኖሚው ውስጥ ጉልህ ሚና እንዲጫወቱ ማድረግ የተለመደ ነው፡፡     

spot_img
- Advertisement -spot_img

የ ጋዜጠኛው ሌሎች ፅሁፎች

- ማስታወቂያ -

በብዛት ከተነበቡ ፅሁፎች