የብረታ ብረትና ኢንጂነሪግ ኮርፖሬሽን የነፋስ ኃይል ኤሌክትሪክ ለማመንጨት የሚያገለግሉ የተለያዩ መሣሪያዎችንና ተያያዥ ግብዓቶችን (አክሰሰሪዎች) በአገር ውስጥ ለማምረት እየተዘጋጀ መሆኑ ተገለጸ፡፡
በኮርፖሬሽኑ የኢትዮጵያ ፓወር ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ የሥራ ኃላፊዎች እንደገለጹት፣ ለነፋስ ኃይል ማመንጫ የሚሆኑ መሣሪያዎችን የሚያመርተውን ፋብሪካም በወላይታ ሰዶ የሚገነባ ነው፡፡
ለፋብሪካው መገንቢያ የሚሆነውን ቦታ የተረከበ መሆኑን የገለጹት የሥራ ኃላፊዎቹ፣ በቀጣዩ የበጀት ዓመት የፋብሪካው የኮንስትራክሽን ግንባታ ሥራ ይጀመራል፡፡ ግንባታው ሊፈጅ የሚችለው ወጪ ባይገልጹም ግንባታውን ኮርፖሬሽኑ ራሱ የሚያካሂደው ይሆናል ተብሏል፡፡
ኮርፖሬሽኑ በነፋስ ኤሌክትሪክ ኃይል ለማመንጨት የሚያስችሉ መሣሪያዎችን በአገር ውስጥ ለማምረት ያቀደው በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በነፋስ ኃይል ኤሌክትሪክ ለማመንጨት የሚያስችሉ ተጨማሪ ፕሮጀክቶች የሚካሄዱ በመሆኑ ነው ተብሏል፡፡ ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተውም፣ በአሁኑ ወቅት ወደ ሥራ ከገቡት የአዳማና የአሽጉዳ ነፋስ ኃይል የሠሩ የኤሌክትሪክ ማመንጫ ፕሮጀክቶች ሌላ በአሰላ፣ በደብረ ብርሃንና በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች ተመሳሳይ የኃይል ማመንጫ ለመገንባት ታቅዷል፡፡ የኢትዮጵያ ፓወር ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ለወላይታ ሶዳው ኢንዱስትሪው የሚያስፈልጉትን ጥሬ ዕቃዎች ከውጭ በማስገባት የሚሠራ መሆኑም ታውቋል፡፡ እንዲህ ያሉ ምርቶች በአገር ውስጥ መመረታቸው ከውጭ የሚገባውን ተመሳሳይ ምርት በማስቀረት ለመሣሪያዎቹ ግዥ የሚወጣውን የውጭ ምንዛሪ እንዲቀንስ ያስችላል ተብሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በመቐለ በመገንባት ላይ ያለው የጀነሬተርና የተሽከርካሪዎች ኢንጂንና ሞተር መገጣጠሚያ ፋብሪካ በሚቀጥለው ዓመት ወደ ሥራ ይገባል ተብሏል፡፡ በአሁኑ ወቅት የፋብሪካው ግንባታ የተጠናቀቀ ሲሆን፣ የመገጣሚያ ማሽኖች እየተተከሉ ነው፡፡ ይህ መገጣጠሚያ ፋብሪካ የተለያዩ መጠን ያላቸው ጀነሬተሮችንና ለተለያዩ ተሽከርካሪዎች የሚሆኑ ሞተሮችን ጭምር የሚያመርት ነው፡፡
በኮርፖሬሽኑ ሥር ካሉ የተለያዩ የኢንዱስትሪ ክፍሎች መካከል አንዱ በሆነው የኢትዮጵያ ፓወር ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ እስካሁን ሰባት የተለያዩ ኢንዱስትሪዎችን በሥሩ እያስተዳደረ ሲሆን፣ ከሰባቱ ኢንዱስትሪዎች መካከል የትራንስፎርመር ማምረቻው በፀሐይ ኃይል ማመንጨት የሚችሉ ፓናልና በፀሐይ ኃይል የሚሠሩ መሣሪያዎች የሚያመርተው ፋብሪካ ይጠቀሳል፡፡ ይህ ማምረቻ በሙሉ ኃይሉ በቅርቡ ምርት ይጀምራል ተብሏል፡፡
በሞጆ የሚገኘው የዋየርና ኬብል ማምረቻም ወደ ሰባት ዓይነት ምርቶችን በማምረት ላይ የሚገኘው ፋብሪካም በፓወር ኢንጂነሪንግ ሥር የሚተዳደር ነው፡፡