በቴክኒክና በንግድ ሥራ የሠለጠኑ 63 ሴቶች ሰኔ 12 ቀን 2007 ዓ.ም. ተመረቁ፡፡ በሥልጠናው በወተትና የሥጋ ምርት አቅርቦት፣ እንዲሁም የቁም ከብት ንግድ ላይ ክህሎት የሚያሳድግ ግንዛቤ ማግኘታቸውን በኢትዮጵያ የአሜሪካ ኤምባሲ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ሥልጠናውን ያዘጋጀው የአሜሪካ መንግሥት በዓለም አቀፍ ልማት ኤጀንሲው (USAID) ሲሆን፣ በ2004 ዓ.ም. በሴቶች ላይ በተደረገ ጥናት በወተት ምርት፣ በእንስሳት ዕርባታ፣ በአመራር ዕውቀት፣ በንግድ ሥራ አገልግሎቶች ተደራሽነት፣ ውሳኔ በመስጠት፣ በስኬታማ የንግድ ሥራ ዕቅድ አዘገጃጀት ረገድ የታዩትን ክፍተቶች ለመሙላት ነው ተብሏል፡፡
የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ኤጀንሲ ‹‹ወደፊትን መመገብ›› በተሰኘ ፕሮግራሙ በግብርና ዕድገት ፕሮግራም የእንስሳት ገበያ ልማትና ዘላቂ ልማትን ማረጋገጥ በሚያስችል አቅም መመረቅ በተሰኙ መርሐ ግብሮች፣ በመጋቢት ወር 2007 ዓ.ም. ሥልጠና ሰጥቷቸዋል፡፡ በሥልጠናው የተካተቱት ሴቶች የሥራ ፈጠራ አቅም እንዳላቸው የታመነባቸው መሆናቸው በመግለጫው ተመልክቷል፡፡ ሴቶቹ በአስተዳደርና በሥራ አመራር ክህሎት ሥልጠና የተሰጣቸው ሲሆን፣ ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያግዝ የንግድ ሥራ ዕቅድ በመንደፍ ረገድም የቴክኒክ ዕውቀት ማግኘታቸው ተገልጿል፡፡
ሠልጣኞቹ ከአማራ፣ ከደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል እንዲሁም ከትግራይ ክልል የተውጣጡ ናቸው፡፡ በቆይታቸው ያገኙትን ክህሎት በአካባቢያቸው ለሚገኙ ሴቶችም እንደሚያካፍሉ ይጠበቃል፡፡
ሴቶች በእንስሳት ዕርባታና በእንስሳት ምርት አያያዝ የሚጫወቱትን ሚና ማሳደግ ለቤተሰብም ሆነ በአገር ደረጃ ከፍ ያለ ጠቀሜታ አለው ያሉት የአሜሪካ ዓለም አቀፍ ልማት ኤጀንሲ ተወካይ ካለን ሒዩስ ናቸው፡፡ እሳቸው እንደሚሉት በንግድ ሥራ አስተዳደርና በአመራር ላይ ያተኮረው ሥልጠና፣ በእንስሳት ዕርባታ ዕምቅ አቅም ያላቸው አርዓያ ሴቶች ላይ ማተኮሩ፣ በዘርፉ የመሪነቱን ሚና እንዲጫወቱ ያግዛቸዋል፡፡ በሥልጠናው ያልተካተቱ ሴቶችም በሠልጣኞቹ አማካይነት ተጠቃሚ ይሆናሉ ብለዋል፡፡