የመረጃ መረብ ደኅንነት ኤጀንሲ ባለፉት 11 ወራት አርባ ያህል ከፍተኛ ኪሳራ ሊያስከትሉ የሚችሉ የሳይበር (ኮምፒዩተርን መሠረት ያደረጉ) ጥቃቶችን ማምከኑን፣ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አስታወቀ፡፡
ኤጀንሲው ከተቋቋመ በርካታ ዓመታት ቢያልፉም፣ እንደ አዲስ በተነደፈው አሠራር መሠረት ለመጀመርያ ጊዜ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርቱን ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ለምክር ቤቱ አቅርቧል፡፡
የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር ሜጄር ጄኔራል ተክለ ብርሃን ወልደ አረጋይ እንደገለጹት፣ የአገሪቱን ቁልፍ መሠረተ ልማቶች ለማጥቃት የተሰነዘሩ የሳይበር ጥቃቶች ነበሩ፡፡
‹‹ወደ አገራችን የሚሰነዘሩ የሳይበር ጥቃቶች በርካታና ብዙ መልክ ያላቸው ናቸው፤›› ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፣ ‹‹አንዳንድ የጥቃት ዓይነቶች አገራችንን በተለየ ሁኔታ ዒላማ ያላደረጉ ነገር ግን ማንኛውም ተጋላጭ መሠረተ ልማትን የሚያጠቁ ሲሆን፣ እንደዚህ ዓይነት ጥቃቶች በየቀኑ ከዚህ አልፎም በየሰዓቱ የሚሠራጩ ናቸው፤›› ብለዋል፡፡
ሌሎች ሆን ተብሎ የኢትዮጵያን የሳይበር መሠረተ ልማት ለማጥቃት የሚለቀቁ ቫይረሶች መኖራቸውን የገለጹት ሜጀር ጄኔራል ተክለ ብርሃን፣ ወደ አርባ የሚጠጉ በአጠቃላይ መሠረተ ልማቱንና የተወሰኑ ቁልፍ ተቋማትን ዒላማ ያደረጉ ከፍተኛ ኪሳራ ሊያደርሱ የነበሩ የሳይበር ጥቃቶችን ለማምከን መቻሉን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ጥቃቱ ቢደርስ ኖሮ ሊያስከትል የነበረው ኪሳራ በጣም ትልቅ ነበር፤›› ብለዋል፡፡
ዋና ዳይሬክተሩ ከዚህ ውጪ የሳይበር ጥቃቶቹ በየትኞቹ ቁልፍ ተቋማት ላይ እንደተሠነዘሩ፣ እንዲሁም ከየት አካባቢ እንደሆነ አልገለጹም፡፡
ከዚህ በተጨማሪ በቴሌኮም ማጭበርበር ተግባር ላይ የተሰማሩ 55 ተጠርጣሪዎች በሕግ ቁጥጥር ሥር መዋላቸውን፣ ለዚህ የወንጀል ተግባር ሲጠቀሙባቸው የነበሩ ወደ 170 የተራቀቁና ዘመናዊ ሕገወጥ የቴሌኮም መሣሪያዎች መያዛቸውን ገልጸዋል፡፡ ግለሰቦቹ በቴሌኮም ወንጀል ተሰማርተው በነበረበት ወቅት 700 ሚሊዮን ብር ኪሣራ በኢትዮ ቴሌኮም ላይ ማድረሳቸውንም ተናግረዋል፡፡
ኤጀንሲው የተሰጠውን ተልዕኮ በተቀናጀና በተጠናከረ መንገድ ለመወጣት እንዲችል ቀደም ሲል የተጀመረውን በዘርፉ ያሉትን የሕግ፣ የፖሊሲና የስታንዳርድ ክፍተቶች በመለየት ክፍተቶችን ለመዝጋት እየሠራ መሆኑን ዋና ዳይሬክተሩ አስረድተዋል፡፡
ከእነዚህም መካከል የሳይበር ወንጀል ሕግ ረቂቅ ማዘጋጀት አንዱ ሲሆን፣ በ2005 ዓ.ም. ለካቢኔ ቀርቦ የነበረ ነው፡፡ ረቂቅ ሕጉ ከፍትሕ ሚኒስቴር ጋር በመሆን እንደገና እንዲታይ በመወሰኑ በድጋሚ በመታየት ላይ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡