Tuesday, May 30, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

ክቡር ሚኒስትር

[የክቡር ሚኒስትሩ ልጅ የብሔራዊ ፈተና ተፈትና ቤት ስትገባ አባቷን አገኘቻቸው]

  • ደህና ዋልክ አባዬ?
  • ደህና ነኝ፤ አንቺ እንዴት ዋልሽ?
  • እኔ በጣም ደህና ነኝ፡፡
  • ከትምህርት ቤት እየገባሽ ነው?
  • አዎን፡፡
  • ትምህርት እንዴት ነበር?
  • ሰሞኑን እኮ ፈተና ላይ ነን፡፡
  • እንዴ እና አሁን ተፈትነሽ ነው የምትመጪው?
  • አዎን፡፡
  • በእጅሽ ምንድነው የያዝሽው?
  • ዛሬ የተፈተነው የፈተና ሽት ነው፡፡
  • እስቲ አምጪው፡፡
  • እሺ እንካ፡፡

 

[የክቡር ሚኒስትሩ ልጅ የፈተና ሽቱ ላይ መልሶቿን አክብባ ስለነበር ማረም ጀመሩ] 

  • በጣም ደስ ይላል፡፡
  • ምኑ አባዬ?
  • እስካሁን እኮ ኤክስ አላገኘሁብሽም፡፡
  • የአባቷ ልጅ እኮ ነኝ፡፡
  • ጐበዝ፤ እውነትም በእኔ ነው የወጣሽው፡፡
  • የደፈንኩት ይመስለኛል፡፡
  • መድፈን እኮ ከዘራችን ነው፡፡
  • አንተም ትደፍናለህ እንዴ?
  • መድፈን ቢሉሽ መድፈን ነው?
  • አባዬ ግን አንተ ትማራለህ እንዴ?
  • ኧረ አልማርም፡፡
  • ታዲያ ምንድነው የምትደፍነው?
  • ምን የማልደፍነው ነገር አለ ብለሽ ነው?
  • መንግሥት ጋ ቀዳዳ አለ እንዴ?
  • የምን ቀዳዳ?
  • የሚደፈን ቀዳዳ፡፡
  • አንቺ ልጅ አይደለሽ እንዴ?
  • ብሆንስ ታዲያ?
  • እንዲህ ዓይነት አሽሙር ማነው ያስተማረሽ?
  • ትምህርት ቤት እኮ ብዙ ነገር ሲሉ እሰማለሁ፡፡
  • ምን ይላሉ?
  • እሱን ሌላ ጊዜ እነግርሃለሁ፡፡
  • እንዴ የዚህን ጥያቄ መልስ ምንድነው ያልሽው?
  • ቢ ነዋ፡፡
  • ወይኔ!
  • ምነው አባዬ?
  • መልሱ ኤ ነበራ፡፡
  • ስንተኛው ጥያቄ ላይ ነህ?
  • የመጨረሻው ላይ ነኝ፡፡
  • እኮ ስንት ኤክስ አገኘህብኝ?
  • አንድ ኤክስ፡፡
  • አሪፍ ነዋ አባዬ፡፡
  • አሪፍ አይደለም፡፡
  • ለምን?
  • መድፈን ነበረብሽ?
  • አንድ ኤክስ ስለሆነ እንደ ደፈንኩት ይቆጠራል እኮ፡፡
  • እኔማ በእኔ እንድትወጪ ፈልጌ ነው፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • እኔ ፈተናዬን ደፍኘዋለኋ፡፡
  • አልማርም አላልከኝም እንዴ?
  • ሌላ ፈተና ነበረብኝ፡፡
  • እና ደፈንከው?
  • አዎን ደፈንኩት፡፡
  • በዚህ ዘመን ግን የሚደፍን ሰው ያለ አይመስለኝም ነበር፡፡
  • እኔ አለሁ፡፡

[የክቡር ሚኒስትሩ አማካሪ ቢሯቸው ገባ] 

  • አነበቡት እንዴ ክቡር ሚኒስትር?
  • ምኑን?
  • ጋዜጣው ይዞ የወጣውን፡፡
  • ምን ይዞ ወጣ?
  • ኦባማ እኮ ኢትዮጵያ ሊመጣ ነው፡፡
  • አታውቅም ነበር እንዴ?
  • እርስዎ ያውቁ ነበር እንዴ?
  • ባለፈው እንግዳ ይመጣል አላልኩህም ነበር እንዴ?
  • እኮ እንግዳ ይመጣል ነው ያሉኝ እንጂ መቼ ኦባማ አሉኝ?
  • ለሴኩዩሪቲ ጉዳይ ብዬ ነዋ፡፡
  • ለምን ይዋሻል?
  • ምን አልከኝ?
  • በጣም ደስ ይላል፡፡
  • ምኑ ነው ደስ የሚለው?
  • ኦባማ መምጣቱ፡፡
  • ገና ብዙዎች ወደ ኢትዮጵያ ይጐርፋሉ፡፡
  • ምን ሊያደርጉ?
  • ሊማሩ ነዋ፡፡
  • ከእኛ?
  • አዎና፡፡
  • ከእኛ ደግሞ ምን ይማራሉ?
  • አንተ ኢትዮጵያ እኮ ትልቅ አገር ናት፡፡
  • እንዴት?
  • የሰው ልጅ መገኛ ናት፡፡
  • እሱን አውቃለሁ፡፡
  • የሥልጣኔ መገኛ ናት፡፡
  • እሱማ ትክክል ነው፡፡
  • የቡናም መገኛ ናት፡፡
  • እሱንም አውቃለሁ፡፡
  • አሁን ደግሞ የአንድ አዲስ ነገር መገኛ ሆናለች፡፡
  • የምን?
  • የዲሞክራሲ፡፡
  • ምን አሉኝ?
  • የዲሞክራሲ መገኛ አልኩህ፡፡
  • እኛን ነው አሜሪካንን ነው የሚሉኝ?
  • እኛ ነን እንጂ፡፡
  • እኮ እንዴት ሆኖ?
  • ዲሞክራሲያዊ ምርጫ አካሂደን መቶ በመቶ ማሸነፍ ችለናል፡፡
  • ምን አሉኝ?
  • ስለዚህ ቻይና ያሉ ወንድሞቻችን ከዚህ መማር ይፈልጋሉ፡፡
  • ምንድነው የሚማሩት?
  • እነሱ እኮ ምርጫ ሳያካሂዱ ነው ማሸነፍ የቻሉት፡፡
  • እሱማ ይታወቃል፡፡
  • እኛ ደግሞ ምርጫ አካሂደን መቶ በመቶ ማሸነፍ ችለናል፡፡
  • አሃሃ…
  • ስለዚህ ገና ሌሎች በርካቶች እኛን ይጐበኙናል፡፡
  • እነማን ናቸው?
  • እነ ሳዑዲ ዓረቢያና ሰሜን ኮሪያ የመሳሰሉ፡፡
  • እነዚህ አገሮች እኮ ምርጫ አካሂደው አያውቁም፡፡
  • ለዛ እኮ ነው የምልህ?
  • እንዴት?
  • ምርጫ ባለማካሄዳቸው ስለሚወቀሱ፣ ምርጫ አድርገው ማሸነፍ እንደሚችሉ እናስተምራቸዋለን፡፡
  • በጣም የሚገርም ሐሳብ ነው፡፡
  • ከዚህ በኋላ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ላይ ማተኮር አለብን፡፡
  • ለምን?
  • ዓለም ሁሉ ወደ እኛ ይጐርፋላ፡፡
  • እኮ ለምን?
  • ከእኛ ለመማር፡፡
  • እና ኦባማም የሚመጡት ለዚህ ነው?
  • እንዴታ?
  • ከእኛ ሊማሩ?
  • አሜሪካ እኮ በቅርቡ ምርጫ ታካሂዳለች፡፡
  • እውነትም የእኛ ዕድገት የኢኮኖሚ ብቻ አይደለም ማለት ነው?
  • ምን ነካህ? በኢኮኖሚ ብቻ አድገህ በዲሞክራሲ ካላደግህ እኮ ዋጋ የለውም፡፡
  • እና በዲሞክራሲውም ልክ እንደ ኢኮኖሚው 11 ፐርሰንት አድገናል ማለት ነው?
  • የዲሞክራሲው ከዛም ከፍ ይላል፡፡
  • ስንት ፐርሰንት?
  • መቶ ፐርሰንት፡፡

[የክቡር ሚኒስትሩ ወዳጅ ከውጭ ደወለ] 

  • ሰላም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እንዴት ነህ ወዳጄ?
  • እንኳን ደስ አለዎት፡፡
  • ለምኑ?
  • ያው ውጤቱ መቶ ፐርሰንት መሆኑን ሰምቼ ነው፡፡
  • የሥራችን ውጤት ነው፡፡
  • የእስራችን ውጤት ነው ያሉኝ?
  • የለም የለም፤ የሥራችን ውጤት ነው፡፡
  • ለነገሩ ልክ ብለዋል፡፡
  • ከለፋህ ሁሌም ያልፍልሃል፡፡
  • ካለፉ ግን ሊያልፍብዎት ይችላል፡፡
  • ሥራህ በግልጽ ከታየ ዓለምም ያደንቅሃል፡፡
  • ዓለም መቼ አደነቀን ታዲያ?
  • ከዚህ በላይ መደነቅን በምን እንለካው?
  • ዓለም መደነቁን በምን አወቁ?
  • ይኸው ሊጐበኘን እኮ ነው፡፡
  • ማን ነው የሚጐበኘን?
  • የዓለም መሪው ኦባማ ሊጐበኘን ነው እኮ፡፡
  • ታዲያ እንዳደነቀን በምን አወቁ?
  • ስለሚጐበኘን ነዋ፡፡
  • የሚጐበኘን በሌላ ምክንያት ቢሆንስ?
  • ተደንቆብን ካልሆነ ምን ሊሆን ይችላል?
  • ታዝቦን፡፡
  • ምን?
  • ምርጫውን እንዲታዘቡ መንግሥት ስላልጋበዛቸው ከውጤቱ በኋላ ራሱ ሊታዘበን እየመጣ ቢሆንስ?
  • ተቃዋሚ ሆንክ እንዴ?
  • ክቡር ሚኒስትር ችግርዎት እኮ ይኼ ነው፡፡
  • ምንድነው ችግሬ?
  • ከእርስዎ አመለካከት ውጪ የሆነ ሁሉ ተቃዋሚ ይመስልዎታል፡፡
  • ታዲያ ይህ የተቃዋሚ እንጂ የደጋፊ ሐሳብ ነው?
  • ድጋፋችን ጭፍን መሆን የለበትም፡፡
  • ዓይንህን ካልጨፈንክ እኛን መደገፍ እንዴት ትችላለህ?
  • ለነገሩ እውነትዎትን ነው፡፡
  • እና አሁን ዓይንህን ገልጠሃል?
  • ሁለቱንም ባይሆን አንዱን ገልጫለሁ፡፡
  • እየተጣቀስክ ነዋ?
  • ሁለቱንም ከመግለጤ በፊት መስተካከል ያለበትን አስተካክሉ፡፡
  • እሺ፡፡

 [ክቡር ሚኒስትሩ ቤታቸው ሲገቡ ሚስታቸውን አገኟቸው]

  • መቼም ሰሞኑን ጉራህ አይቻልም?
  • ለምኑ?
  • ኦባማ ሊመጣ መሆኑን ሰምቼ ነዋ፡፡
  • ሥራችን ገና ብዙዎችን ያስመጣል፡፡
  • ጀመረህ ጉራህ፡፡
  • ጠንክረን እየሠራን ስለሆነ በርካታ መሪዎች ገና ይመጣሉ፡፡
  • የመጀመሪያ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት መሆኑ ነው ኢትዮጵያን ሲጐበኝ?
  • የለም የለም፤ ከዚህ በፊት ሌሎችም ጐብኝተውናል፡፡
  • እነማን?
  • ቡሽ ብትይ፣ ክሊንተን ብትይ፣ ካርተር ብትይ፡፡
  • ይኼ እኮ ነው ችግርህ፡፡
  • እንዴት?
  • እነሱ እኮ የመጡት ከሥልጣን ከወረዱ በኋላ ነው፡፡
  • ቢወርዱስ?
  • እንደ እናንተ ከወረዱም በኋላ አገሪቱን የሚገዙ ይመስልሃል አይደል?
  • ምነው ወሬ አበዛሽ?
  • ለመሆኑ ለምንድነው የሚመጣው?
  • ለሁለት ነገር ነው፡፡
  • ለምንና ለምንድነው?
  • በመጀመሪያ ከእኛ ለመማር ነው፡፡
  • እንዴት?
  • በዴሞክራሲያዊ ምርጫ መቶ ፐርሰንት እንዴት ማሸነፍ እንደሚቻል ለመማር ነው፡፡
  • ሁለተኛውስ?
  • በዓለም መሪዎች ፊት ለዚህ የምርጫ ውጤት ሽልማት ሊሰጠን ነው፡፡
  • ለምን ይሸልማችኋል?
  • ስለደፈነው፡፡
  • ሙገሳ ስትጠብቅ ሌላ እንዳይገጥምህ፡፡
  • ሌላ ምን?
  • ሙለጫ!  

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

ዩኒቨርሲቲዎችን ራስ ገዝ ያደረገው አዋጅ የፍትሐዊነት ጥያቄ አስነሳ

በቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት ስምንት ዩኒቨርሲቲዎችን ራስ ገዝ በማድረግ ተቋማዊና...

የሁለተኛው አብዮታዊ ሠራዊት ዋና አዛዥ ሜጀር ጄኔራል ሁሴን አህመድ (1930-2015)

ኢትዮጵያ የሁለተኛውን የፋሺስት ጣሊያን ወረራ (1928-1933) በድል ከተወጣች በኋላ...

ከወለድ ነፃ ባንክ የተሰበሰበውን በመቶ ቢሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ ለምን ሥራ ላይ ማዋል አልተቻለም?

  ባንኮች ከወለድ ነፃ የሚሰበስቡት ተቀማጭ ገንዘብ መጠን ዕድገት እያሳየ...

መንግሥት ባለፈው ዓመት ለማዳበሪያ የደጎመው 15 ቢሊዮን ብር ለአርሶ አደሮች አለመድረሱ ጥያቄ አስነሳ

መንግሥት ለ2014/15 በጀት ዓመት እርሻ በአፈር ማዳበሪያ ላይ ያለውን...
- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

የመስቀል አደባባይ የመግቢያ ክፍያ ለምን?

ወጣቶች፣ ሕፃናትና አረጋውያን ሳይቀሩ መንፈሳቸውን የሚያድሱበት እንዲሁም ሐሳባቸውን በነፃነት...

በሕገ መንግሥቱ የተዋቀረው ‹‹የብሔር ፖለቲካ›› እና ‹‹ሥርዓቱ›› ያስከተለው መዘዝና መፍትሔው

(ክፍል አራት) በዓቢዩ ብርሌ (ጌራ) ባለፈው ጽሑፌ (በክፍል ሦስት) አሁን ያለው...

የኢትዮጵያ ኅብረተሰብና የመንግሥት መሪ ምሥል

በበቀለ ሹሜ በ2015 ዓ.ም. መጋቢት ወር ውስጥ ይመስለኛል በ‹ሸገር ካፌ›...

ዩኒቨርሲቲዎችን ራስ ገዝ ያደረገው አዋጅ የፍትሐዊነት ጥያቄ አስነሳ

በቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት ስምንት ዩኒቨርሲቲዎችን ራስ ገዝ በማድረግ ተቋማዊና...

ለመጪው ዓመት የሚያስፈልገው 4.3 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ነዳጅ 4.4 ቢሊዮን ዶላር ወጪ ይጠይቃል

ለመጪው 2016 ዓ.ም. ወደ አገር ውስጥ ለማስገባት ለታቀደው 4.3...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ የቢሮ ስልካቸው ጠራ። ደዋዩ የጊዜያዊ አስተዳደሩ ኃላፊ እንደሆኑ ሲነገራቸው የስልኩን መነጋገሪያ ተቀበሉ]

ሃሎ፡፡ እንዴት አሉ ክቡር ሚኒስትር። ደህና ነኝ። አንተስ? አስተዳደሩስ? ሕጋዊ ሰውነታችን ተነጥቆ እንዴት ማስተዳደር እንችላለን ክቡር ሚኒስትር? ለዚህ ጉዳይ እንደደወልክ ገምቻለሁ። ደብዳቤም እኮ ልከናል ክቡር ሚኒስትር፡፡ አዎ። ሁለት ደብዳቤዎች ደርሰውኛል።...

[ክቡር ሚኒስትሩ አየር መንገዱ ወጪ ቆጣቢ የሥራ እንቅስቃሴ በማድረግ የውጭ ምንዛሪ ግኝቱን በሚያሳድግበት ሁኔታ ላይ ከተቋሙ ኃላፊ ጋር እየተወያዩ ነው]

ቀደም ብዬ እንደገለጽኩት ትልቁ ወጪያችን ለነዳጅ ግዥ የሚውለው ነው። ክቡርነትዎ እንደሚገነዘቡት የዩክሬን ጦርነት የዓለም የነዳጅ ዋጋ በእጅጉ አሻቅቧል። ቢሆንም አገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ችግር ውስጥ...

[ክቡር ሚኒስትሩ የነዳጅ ግብይት በዲጂታል ክፍያ መንገድ ብቻ እንዲፈጸም የተላለፈውን ውሳኔ አተገባበር ላይ ስለተነሱ ቅሬታዎች ከባልደረባቸው ጋር እየተወያዩ ነው]

ክቡር ሚኒስትር አተገባበሩ ጥሩ ቢሆንም፣ ከፍተኛ ወቀሳ እየደረሰብን ነው። ዲጂታል የግብይት ሥርዓቱን ለማስፋፋት በመጣራችን መመስገን ሲገባን እንዴት እንወቀሳለን? የሚገርመው በዲጂታል ክፍያ ላይ የተሰማሩ ኩባንያዎች ናቸው በዋነኛነት...