Monday, March 27, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊኢሠማኮ የድጎማ ጥያቄውን ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ሊያቀርብ ነው

ኢሠማኮ የድጎማ ጥያቄውን ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ሊያቀርብ ነው

ቀን:

የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን (ኢሠማኮ) መንግሥት ድጎማ  እንዲያደርግለት ያዘጋጀውን ፕሮፖዛል፣ ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ሊያቀርብ ነው፡፡

ታኅሳስ 26 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ሚኒስትሩና በኢሠማኮ አመራሮች መካከል በተደረገ የምክክር መድረክ ላይ፣ ኢሠማኮ ለመንግሥት ይደረግልኝ ብሎ ያቀረበውን ጥያቄ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቃል አወንታዊ ምላሽ ሰጥተው እንደነበር ይታወሳል፡፡

በዚሁ ምላሽ መሠረት ኢሠማኮ የመንግሥትን ድጎማ እሻባቸዋለሁ ያላቸውን ጉዳዮች በዝርዝርና በፕሮፖዛል መልክ አዘጋጅቷል፡፡ ያስፈልገኛል ያለውንም የገንዘብ መጠን በመጥቀስ  ለገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር አቅርቦ ነበር፡፡

ይህንን ፕሮፖዛል ያቀረበው ባለፈው ዓመት መጨረሻ ላይ ቢሆንም፣ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ምንም ዓይነት ምላሽ ሳይሰጠው ቆይቶ ነበር፡፡ ቆይቶም ግን ኢሠማኮ ለሚኒስቴሩ ያቀረበው ጥያቄ መቅረብ ያለበት ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ነው የሚል ምላሽ ስለተሰጠው፣ ‹‹ድጎማ ይሰጠኝ›› የሚለውን ጥያቄውን በድጋሚ ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ለማቅረብ እየተዘጋጀ መሆኑን፣ የኢሠማኮ ፕሬዚዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

‹‹መንግሥት ድጎማ እንዲያደርግልን የፈለግነው ለግንዛቤ ማስጨበጫና ለአቅም ግንባታ ፕሮግራሞች ማስፈጸሚያ የሚውል ነው፤›› ያሉት አቶ ካሳሁን፣ ይህንንም በፕሮፖዛላቸው ላይ ማስፈራቸውን ተናግረዋል፡፡

በተከታታይ በየዓመቱ የአሠሪና ሠራተኞችን ግንኙነት በሚመለከት የኢንዱስትሪ ሰላምን ለመፍጠር በሚያስችሉ የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት፣ ሁሉም ወገን መብትና ግዴታውን እንዲወጣ ለማድረግ ለሚያስፈልገው ወጪ መንግሥት ድጎማ እንዲያደርግ በኢሠማኮ ተጠይቋል፡፡ ሥልጠናዎቹና የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራሞቹ በአሠሪና በሠራተኛ ዘንድ አሉ የሚባሉትን ችግሮች ለመፍታት፣ ሠራተኛውና አሠሪውን የሚመለከቱ ሕጎች ምን እንደሚመስሉ ለማሳየትና በዚሁ መሠረት ተፈጻሚ እንዲሆን ለማስቻል ጭምር ነው፡፡ ድጎማው ለተፈለገው ዓላማ ብቻ የሚውል ነው ያሉት አቶ ካሳሁን፣ ከመንግሥት የሚገኘው የገንዘብ ድጎማ ለኢሠማኮ ውስጣዊ በጀት ወይም ለአስተዳደር ሥራ እንደማይውልና ደመወዝን ለመሰሉ ወጪዎች ማስፈጸሚያም እንደማይጠቀምበት ገልጸዋል፡፡

ኢሠማኮ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተመራው ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ጋር አድርጎት በነበረው የምክክር መድረክ ላይ፣ ሊፈጸሙልኝ ይገባሉ ብሎ ካቀረባቸው ከ30 በላይ ጥያቄዎች ውስጥ አንዱ ‹‹መንግሥት ኢሠማኮን ይደጉም›› የሚል ሲሆን፣ መንግሥትም ኢሠማኮን ለመደገፍ ፈቃደኝነቱን አሳይቷል፡፡

በወቅቱም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ‹‹ድጎማ የሚለው ቃል ጸያፍ ነው…በድጎማ ያደገ አገርና ድርጅት የለም፡፡ ሥራ ለመሥራት የገበያ ክፍተት ስላለ እንደ ልማታዊ መንግሥት ለዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ አጋር ይሆናል ተብሎ እስከታመነ ድረስ በኢሠማኮ የተጠየቀውን እንሰጣለን፤›› ብለው፣ ‹‹ይህ ድጎማ ግን ለሽርሽር የምትጠቀሙበት አይደለም፤›› የሚል ምላሽ ሰጥተዋቸው እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ይህ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ምላሽ ሠራተኞችን ማስጨብጨቡ ይታወሳል፡፡

በወቅቱ ሊፈቱልን ይገባል ተብለው ከኢሠማኮ ከቀረቡት ጥያቄዎች ውስጥ አብዛኞዎቹ አዎንታዊ ምላሽ እንዳገኙ የተነገረ ሲሆን፣ ከቀረጥ ነፃ ተሽከርካሪዎችም እንዲገቡ ተፈቅዶላቸዋል፡፡ አሠሪዎች ለሠራተኞቻቸው የሚያቀርቡት ምግብ ታክስ እንዳይደረግ የሚለውም ጥያቄያቸው አወንታዊ ምላሽ እንዳገኘም ለማወቅ ተችሏል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ለፋይናንስ ዘርፉ ብቃት ያለው የሰው ኃይል የማፍራት የቤት ሥራን የማቃለል ጅማሮ

የአገሪቱ የፋይናንስ ዘርፍ እያደገ ለመሆኑ ከሚቀርቡ ማስረጃዎች ውስጥ  የግል...

የምድር ባቡርን የሚያነቃቃው የመንግሥት ውሳኔ

በኢትዮጵያ ወደብ አልባነት ላይ የተደመረውን የሎጀስቲክስ ችግር ለመፍታት ግዙፍ...

የፓርላማ አባላት ስለሰላም ስምምነቱ አፈጻጸም ግልጽ መረጃ የለንም አሉ

‹‹ሕወሓትን ለፍረጃ አብቅተውት የነበሩ ጉዳዮች በአብዛኛው መልክ ይዘዋል›› ሬድዋን...