Friday, December 8, 2023
- ማስታወቂያ -
- ማስታወቂያ -

መንግሥት ከሚድሮክ ጎልድ ከ429 ሚሊዮን ብር በላይ የሮያሊቲ ክፍያ ማጣቱ ሪፖርት ተደረገ

ተዛማጅ ፅሁፎች

ማዕድን ሚኒስቴር በአገሪቱ የሕግ አግባብ መሠረት ባለመሥራቱ፣ መንግሥት በከፍተኛ ደረጃ የማዕድን ማምረት ሥራ ላይ ከተሰማራው ሚድሮክ ወርቅ ማዕድን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ማግኘት የሚገባውን ከ429 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ማሳጣቱን የዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት አስታወቀ፡፡

የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት በማዕድን ሚኒስቴር ላይ በ2006 ዓ.ም. አጠቃላይ የሥራ አፈጻጸም ላይ ባደረገው የክዋኔ ኦዲት ነው መንግሥት ከፍተኛ ገንዘብ ማጣቱን ያረጋገጠው፡፡

የማዕድን ሥራ አዋጅን በተመለከተ የወጣው የ1986 ዓ.ም. አዋጅ ከከበሩ ማዕድናት ሽያጭ አምስት በመቶ የሮያሊቲ ክፍያ እንደሚወስን፣ ባልከበሩ ማዕድናት ላይ ምንም የሚለው ነገር እንደሌለ የኦዲተሩ የክዋኔ ኦዲት ሪፖርት ያስረዳል፡፡

ይህ አዋጅ ግን በአዋጅ ቁጥር 678/2002 መሻሻሉን በዚህ መሠረትም የከበሩ ማዕድናት ላይ ስምንት በመቶ የሮያሊቲ ክፍያ መጣሉን፣ ያልከበሩ ማዕድናት ላይ ስድስት በመቶ መጣሉን ሪፖርቱ ያትታል፡፡

ይሁን እንጂ ማዕድን ሚኒስቴር ከሚድሮክ ወርቅ ማዕድን ኩባንያ የከበሩና በከፊል የከበሩ ማዕድናት ላይ አምስት በመቶ ብቻ ሮያሊቲ ክፍያ በመሰብሰቡ፣ ከ2004 ዓ.ም.  እስከ 2006 በጀት ዓመት ከሚድሮክ የወርቅ ሽያጭ መንግሥት ሊያገኝ የሚችለውን 252.9 ሚሊዮን ብር ማጣቱን፣ እንዲሁም ካልከበሩ ማዕድናት በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ ብቻ 413,394 ብር ማጣቱን፣ በድምሩ በሁለት ዓመታት ውስጥ 253.37 ሚሊዮን ብር ለመንግሥት ገቢ መደረግ የነበረበት የሮያሊቲ ገንዘብ አለመሰብሰቡን ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡

በተጨማሪም ሚድሮክ ወርቅ ማዕድን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር በ2000 ዓ.ም. ማምረት የጀመረ ቢሆንም፣ ማዕድን ሚኒስቴር ግን ይህንን ተቋም በየወቅቱ እየተከታተለ ሒሳባቸውን እንዳልመረመረ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ማረጋገጡን ይገልጻል፡፡ ይህም በመሆኑ በሮያሊቲ ሥሌቶች ላይ በሕግ ማሻሻያዎች የሚመጡ ለውጦችን በመከተል የመንግሥትን ገቢ ለማስገባት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ እንዳልቻለ ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም መንግሥት በሚድሮክ የወርቅ ማዕድን አክሲዮን ማኅበር ላይ ያለውን የነፃ ድርሻ በሕግ አግባብ ማስላት ባለመቻሉ፣ እስከ 2005 ዓ.ም. ድረስ 108.7 ሚሊዮን ብር እንዲሁም እስከ መጋቢት 2006 ዓ.ም. ድረስ 67.4 ሚሊዮን ብር በድምሩ 176.2 ሚሊዮን ብር አገሪቱ ማጣቷን ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡

ይህ በመሆኑም የተፈጠረውን ስህተት በማረም መንግሥት ያጣው ገንዘብ እንዲመለስ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ማዕድን ሚኒስቴሩን አሳስቧል፡፡

spot_img
- Advertisement -spot_img

የ ጋዜጠኛው ሌሎች ፅሁፎች

- ማስታወቂያ -

በብዛት ከተነበቡ ፅሁፎች