በመጪው ሐምሌ ወር አጋማሽ ወደ ኢትዮጵያ እንደሚመጡ የተረጋገጠው የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ጉብኝት፣ የአገሪቱን ስኬት ከመረዳት የመነጨ ነው ሲሉ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሚኒስቴር አቶ ሬድዋን ሁሴን ገለጹ፡፡
ከዓመታት በፊት በምዕራብ አፍሪካ ጉብኝት ባደረጉበት ወቅት ኢትዮጵያን ሳይጐበኙ መመለሳቸውን ያስታወሱት አቶ ሬድዋን፣ ‹‹በወቅቱ የምፅዓት ቀን የመጣባት መስሏቸው ብዙ ብዙ የተናገሩ የመገናኛ ብዙኃን እንደነበሩ እናውቃለን፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ያለፈውን የፕሬዚዳንቱን የምዕራብ አፍሪካ ጉብኝት አስመልክቶ አስተያየት የሰጡ የመገናኛ ብዙኃን፣ አሁን ደግሞ ጉዳዩ ምንም ዓይነት ጠቀሜታ የለውም እያሉ እንደሆነም እናውቃለን፤›› ብለዋል፡፡
‹‹እንዳይመጡ የሚቀሰቅሱ አሉ፡፡ ባይሄዱ ይሻል ነበር ቡራኬ መስጠት ነው ብለው የሚያስቡ አሉ፡፡ መምጣታቸው ምንም ለውጥ የለውም ስንት መሪ መጥቶ የለም ወይ በማለት ደግሞ ዝቅ ለማድረግ የሚሞክሩም አሉ፤›› በማለት በፕሬዚዳንት ኦባማ የኢትዮጵያ ጉብኝት ላይ እየተሰጡ ያሉ ትርክቶችን አውስተዋል፡፡
‹‹ቤታችን እየተናጋ ቢሄድ እንባችንን ለማበስ የሚመጣ መሪ አይኖርም፡፡ ቤታችንን በልኩ በወጉ መያዝ ስንጀምር የስኬታችን አካል የሚሆን ሰው እየጨመረ እንደሚመጣ ቀድመንም ስንናገር ነበር፤›› በማለት የፕሬዚዳንት ኦባማ ጉብኝት ከአገሪቱ ዕድገት ጋር ግንኙነት እንዳለው አስታውቀዋል፡፡
ሁለተኛው ያነሱት ምክንያት ደግሞ አገሪቱ በዓለም አቀፍ ሰላም ማስከበር ያላት ሚና ከፍተኛ መሆኑን ነው፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ ሰላም ለማረጋጋት ከፍተኛ ሚና ካላቸው አገሮች ውስጥ አራተኛ ደረጃ ያላት ሲሆን፣ ከአፍሪካ የሚስተካከላት የለም፡፡ ይህን የሚያህል ለዓለም ሰላም አስተዋጽኦ የምታደርግ አገርን አለመጐብኘት ቀድሞ ነገርም ፍትሐዊ አልነበረም፤›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያና የአሜሪካ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት 112 ዓመታትን ያህል ያስቆጠረ ሲሆን፣ በሥልጣን ላይ የሚገኝ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ኢትዮጵያን ሲጐበኝ ይህ የባራክ ኦባማ የመጀመሪያው ይሆናል፡፡ ከዚህ ቀደም ከሥልጣናቸው ከወረዱ በኋላ ጂሚ ካርተር፣ ቢል ክሊንተንና ጆርጅ ደብልዩ ቡሽ ኢትዮጵያን መጎብኘታቸው ይታወሳል፡፡