Tuesday, November 28, 2023
- ማስታወቂያ -
- ማስታወቂያ -

የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ያቀረበው የጋራ ገቢ ድርሻ ጥያቄ ውድቅ ተደረገ

ተዛማጅ ፅሁፎች

የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር የፌዴራልና የክልል የጋራ ገቢ ተብሎ ከሚሰበሰበው ገቢ ውስጥ ድርሻው እንዲከፈለው ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ያቀረበው ጥያቄ፣ የክልል መንግሥትነት ዕውቅና የሌለው በመሆኑ ውድቅ ተደረገ፡፡

የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 98 የፌዴራሉ መንግሥትንና የክልሎችን የጋራ ታክስና የግብር ሥልጣንን ይደነግጋል፡፡

በዚህም መሠረት የፌዴራል መንግሥትና ክልሎች በጋራ በሚያቋቁሟቸው የልማት ድርጅቶች ላይ የንግድ ትርፍ ግብር፣ የሥራ ግብር፣ የሽያጭና የኤክሳይስ ታክስ በጋራ እንደሚጥሉና እንደሚሰበስቡ ይገልጻል፡፡ በተጨማሪም በድርጅቶች የንግድ ትርፍ ላይና በባለአክሲዮኖች የትርፍ ድርሻ ላይ የግብርና የሽያጭ ታክስ በጋራ እንደሚጥሉና እንደሚሰበስቡ፣ በመጨረሻም በከፍተኛ የማዕድን ሥራዎች፣ በማናቸውም የፔትሮሊየምና የጋዝ ሥራዎች ላይ የገቢ ግብርና የሮያሊቲ ክፍያዎች በጋራ እንደሚጥሉና እንደሚሰበሰቡ ይደነግጋል፡፡

ይህንኑ ድንጋጌ መሠረት በማድረግ ከሚሰበሰበው የጋራ ገቢ ክልሎች ድርሻቸውን በመውሰድ ለልማት እያዋሉ የሚገኙ መሆኑን፣ በዚሁ አግባብም የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር የጋራ ገቢ ክፍፍል ድርሻውን እየወሰደ እስከ 2001 ዓ.ም. ድረስ ለልማት ሲያውል መቆየቱን፣ አስተዳደሩ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት በደብዳቤ አሳውቋል፡፡ ከ2001 ዓ.ም. በኋላ ግን የገቢ ድርሻው መቋረጡን በመጥቀስ እንዲለቀቅለት ጥያቄውን ለፌዴሬሽን ምክር ቤት አቅርቧል፡፡ የአስተዳደሩን ጥያቄ ለበጀት ድጐማና የጋራ ገቢዎች ድልድል ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የመራው የፌዴሬሽን ምክር ቤት፣ ቋሚ ኮሚቴው ያቀረበለትን የውሳኔ ሐሳብ ሰኔ 17 ቀን 2007 ዓ.ም. አዳምጧል፡፡

የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ የትምህርት ሚኒስትሩና የደቡብ ክልል ምክር ቤት ተወካዩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት ሪፖርት፣ ቋሚ ኮሚቴው በድሬዳዋ አስተዳደር ጥያቄ ላይ በጥልቀት ከተወያየ በኋላ ሕገ መንግሥታዊ ትርጉም የሚያስፈልገው መሆኑ ስለታመነበት፣ ለሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ እንዲመራ በማድረግ ምላሽ ማግኘቱን አስታውቀዋል፡፡

የሕገ መንግሥት አጣሪ ጉባዔው ባደረገው ምርመራ ‹‹የኢፌዴሪ መንግሥት በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 46(1) መሠረት በክልል መንግሥትነት ዕውቀና የተሰጣቸው ዘጠኙ ክልሎች መሆናቸውን፣ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 49(1) የፌዴራል መንግሥቱ አካል ተደርጐ የሚወሰደው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ነው፤›› በማለት መግለጹን አቶ ሽፈራው ገልጸዋል፡፡

የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር በፌዴራል መንግሥት በወጣ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ቻርተር አዋጅ ቁጥር 416/1996 መሠረት ለጊዜው የፌዴራል መንግሥት አስተዳደራዊ አካል ቢሆንም፣ በሕገ መንግሥቱ በክልልነትም ሆነ በፌዴራል መንግሥት የአስተዳደር መዋቅር ውስጥ የሌለ በመሆኑ የሕገ መንግሥት ትርጉም የሚያስፈልገው ጥያቄ አይደለም በማለት ጉባዔው እንደወሰነ ተናግረዋል፡፡

በዚሁ መሠረትም የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ውሳኔውን እንዲያውቀው መደረጉን አቶ ሽፈራው ለምክር ቤቱ አስረድተዋል፡፡

‹‹በሌላ በኩል ግን ከኅብረተሰቡ የልማት ተሳትፎና ተጠቃሚነት አንፃር የከተማ አስተዳደሩ ያቀረበው ጥያቄ አግባብነት ያለው መሆኑን ቋሚ ኮሚቴው ያምናል፤›› ሲሉ አቶ ሽፈራው ተናግረዋል፡፡

ጉዳዩን በተመለከተ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የድሬዳዋ ከተማ የኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ፈቃዱ በየነ የከተማው አስተዳደር በውሳኔው ደስተኛ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡ ‹‹የድሬዳዋ ከተማ በሕገ መንግሥቱ የክልል መንግሥትነት ዕውቅና እንደሌላት የታወቀ ነው፡፡ ነገር ግን የፌዴራል መንግሥት ከከተማው የሚሰበሰበው ገቢ ተቋዳሽ መሆን አለበት፡፡ ከተማዋ ወደ ኢንዱስትሪ መንደርነት እየተቀየረች ነው፡፡ መሠረተ ልማት ማሟላት ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ደግሞ ተጨማሪ ገቢ የከተማው አስተዳደር ሊያገኝ ይገባል፤›› ብለዋል፡፡

ከከተማው የሚሰበሰውን ገቢ የፌዴራል መንግሥት ብቻ እየወሰደ የከተማዋ ነዋሪዎች፣ በሲሚንቶ ፋብሪካዎች ወይም አሁን በሚፈጠሩት ኢንዱስትሪዎች የሚለቀቅ ጢስና የአካባቢ ጉዳት ገፈት ቀማሽ ብቻ መሆን የለባቸውም ብለዋል፡፡ አስተዳደሩ በካቢኔ ደረጃ ተነጋግሮ ምላሽ የሚሰጥ መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡

የኦሮሚያ ክልልና የሶማሌ ክልል በድሬዳዋ ላይ ባነሱት የይገባኛል ጥያቄ የፌዴራሉ መንግሥት ባወጣው አዋጅ፣ ድሬዳዋ በጊዜያዊነት የፌዴራሉ መንግሥት መዋቅር አካል እንድትሆን መደረጉ ይታወሳል፡፡  

spot_img
- Advertisement -spot_img

የ ጋዜጠኛው ሌሎች ፅሁፎች

- ማስታወቂያ -

በብዛት ከተነበቡ ፅሁፎች