Thursday, September 21, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊየቅማንት ማኅበረሰብ ተጨማሪ ጥያቄ በክልሉ መንግሥት መፍትሔ ያግኝ ተባለ

የቅማንት ማኅበረሰብ ተጨማሪ ጥያቄ በክልሉ መንግሥት መፍትሔ ያግኝ ተባለ

ቀን:

–  የዛይ ሕዝብ የማንነትና የራስ አስተዳደር ጥያቄ አቅርቧል

የአማራ ክልል ምክር ቤት የቅማንት ሕዝብ ላነሳቸው ተጨማሪ የማንነትና ራስን የማስተዳደር ጥያቄ፣ ከዚህ ቀደም ዋናውን ችግር ለመፍታት በሄደበት መንገድ እንዲፈታ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ውሳኔ አሳለፈ፡፡

የፌዴሬሽን ምክር ቤት የመጨረሻ የሥልጣን ዘመኑን ማጠቃለያ ጉባዔ ሰኔ 17 ቀን 2007 ዓ.ም. ባካሄደበት ወቅት፣ የምክር ቤቱ የሕገ መንግሥትና ክልሎች ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ በቅማንት ሕዝቦች የማንነትና የራስ አስተዳደር ጥያቄ ላይ ያቀረበውን የውሳኔ ሐሳብ መርምሮ ነው ውሳኔውን ያሳለፈው፡፡

በአማራ ክልል የሚኖሩ የቅማንት ሕዝቦች የማንነትና ራስን የማስተዳደር ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄያቸውን በመጀመርያ ያቀረቡት ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ነው፡፡ ምክር ቤቱም ለቀረበው ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት የሕገ መንግሥትና የክልል ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ኃላፊነቱን እንዲወስድ ማድረጉን የቋሚ ኮሚቴው ሪፖርት ያስታውሳል፡፡

ቋሚ ኮሚቴው የጥናት ቡድን አቋቁሞ ከአማራ ክልል፣ ከሰሜን ጎንደርና በየደረጃው ከሚገኙ የወረዳና የቀበሌ አመራሮችና ከአቤቱታ አቅራቢ ኮሚቴ ጋር በመተባበር ጥናት ማካሄዱን ይገልጻል፡፡ በዚሁ ጥናት በላይ አርማጭሆ፣ በጭልጋና በመተማ ወረዳዎች የወረዳ አመራሮችና የጥያቄ አቅራቢው ሕዝብ አስተባባሪ ኮሚቴ በመስማማት በመረጧቸው ናሙና ቀበሌዎች ባደረገው ጥናት ዕድሜ ጠገብ አዛውንቶች፣ አልፎ አልፎም ወጣቶች ቋንቋውን እንደሚናገሩና ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ ሕፃናት ቋንቋውን ለመማር ከፍተኛ ጉጉት እንዳላቸው የጥናት ቡድኑ ማረጋገጡን የኮሚቴው ሪፖርት ይገልጻል፡፡

በጥናቱ ያልተሸፈነ ነው ያለውን ማኅበረሰቡ በተያያዘ መልከዓ ምድር መኖር ያለመኖራቸውን ያካተተ ጥናት ተጠንቶ እንዲቀርብለት ቋሚ ኮሚቴው ለጥናት ቡድኑ ውሳኔ ማሳለፉን አስታውሷል፡፡

የጥናት ቡድኑ ከላይ በተገለጸው መሠረት ጥናቱን ለመቀጠል በተንቀሳቀሰበት ወቅት፣ የክልሉ መንግሥት በራሱ ተነሳሽነት ለጥያቄው ምላሽ ለመስጠት ኮሚቴ አቋቁሞ ሥራ መጀመሩን ገልጿል፡፡ በቋሚ ኮሚቴው የተላኩ አጥኚዎች ተልዕኮ ለጊዜው እንዲቆይና የክልሉ መንግሥት በራሱ ጥያቄውን ለመመለስ የጀመረው እንቅስቃሴ ውጤት እንዲጠበቅ ባቀረበው ጥያቄ መሠረት፣ ጥያቄውን ቋሚ ኮሚቴው እንደተቀበለው ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡

ክልሉ ባካሄደው ጥናት የራስ አስተዳደር ጥያቄውን ዕውቅና ሰጥቶ የቅማንት ሕዝብ ራሱን ችሎ በኩታ ገጠም በሚኖርባቸው የጭልጋና የላይ አርማጭሆ ወረዳዎችን ማዕከል በማድረግ፣ ከሐምሌ 1 ቀን 2007 ጀምሮ የአስተዳደር በጀት ለመመደብና ሌሎች አስፈላጊ ሥራዎችን ለመሥራት የአማራ ክልል ምክር ቤት በ14ኛ መደበኛ ጉባዔው ውሳኔ ማሳለፉን በመግለጽ፣ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ሪፖርት ማድረጉን ቋሚ ኮሚቴው ገልጿል፡፡ የክልሉ መንግሥት ችግሩን ለመፍታት በተነሳሽነት ያሳየው ትብብርና ቁርጠኝነትን የፌዴሬሽን ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ አድንቆታል፡፡

ይሁን እንጂ የማኅበረሰቡ ተወካዮች የክልሉ ምክር ቤት የሰጠው ውሳኔ ሁሉንም ቀበሌዎች ያላካተተና የተሸራረፈ ውሳኔ ነው በማለት ተቃውሟቸውን በድጋሚ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ማቅረባቸውን፣ የሕገ መንግሥትና የክልል ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሪፖርት ይገልጻል፡፡ ቋሚ ኮሚቴው በጥያቄው ላይ ውይይት በማድረግ የቀረበውን ተጨማሪ ጥያቄ ክልሉ ከዚህ በፊት ከፈታው ችግር በላይ ሊሆን እንደማይችል ግንዛቤ በመውሰድ፣ የክልሉ መንግሥት በጀመረው አግባብ ተጨማሪ ጥያቄውን እንዲፈታ የሚል አቋም በመያዙ የፌዴሬሽን ምክር ቤትም ይህንን ውሳኔ በመቀበል ለክልሉ ኃላፊነቱን በመስጠት እንዲወስን ሲል ጠይቋል፡፡ በቀረበው የውሳኔ ሐሳብ ላይ በመወያየትም ምክር ቤቱ ውሳኔውን ተቀብሎ አፅድቆታል፡፡

የቅማንት ሕዝብ በአማራ ክልል በስምንት ወረዳዎች በሚገኙ 126 ቀበሌዎች ውስጥ የራስ አስተዳደር ጥያቄ ያነሰ ቢሆንም፣ የአማራ ክልል ምክር ቤት ግን ባካሄደው ጥናት ላይ ተመሥርቶ መጋቢት 2 ቀን 2007 ዓ.ም. የሰጠው ውሳኔ በሁለት ወረዳዎች በሚገኙ 42 ቀበሌዎች ላይ ነው፡፡ የቅማንት ሕዝብ ተወካዮች ለሪፖርተር በጽሑፍ እንደገለጹት፣ የክልሉ መንግሥት ጥያቄያቸውን እየሸራረፈና ተጨማሪ ጥያቄዎችን እያነሱ ባሉት ተወካዮች ላይ ጉዳት እያደረሰ ነው፡፡

‹‹ከዚህ ሁሉ የችግር ጫና ውስጥ የቅማንት ሕዝብ እየገባ ያለው ጥያቄው በይግባኙ መሠረት በፌዴሬሽን ምክር ቤት መመለስ ባለመቻሉ ነው፡፡ ይግባኝ የቀረበለት የፌዴሬሽን ምክር ቤት በአዋጅ ቁጥር 251/1993 በተሰጠው ሥልጣንና ኃላፊነት መሠረት የማያዳግም ውሳኔ ቢያስተላልፍ ይህ ሁሉ ችግር ውስጥ አይገባም ነበር፡፡ አሁንም በቀረበለት ይግባኝ መሠረት ውሳኔ እንዲያስተላለፍ አቤቱታችንን እናሰማለን፤›› ሲሉ ሰኔ 9 ቀን 2007 በጻፉት ደብዳቤ ፌዴሬሽን ምክር ቤትን ጠይቀዋል፡፡

የፌዴሬሽን ምክር ቤት የሕገ መንግሥትና የክልል ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ግን በአዋጁ መሠረት ኃላፊነት ቢኖረውም፣ ለክልል መንግሥታት ቀርበው ውሳኔ በተሰጠባቸው የማንነት ጥያቄዎች ቅር በመሰኘት ለፌዴሬሽን ምክር ቤት የሚቀርቡ አቤቱታዎችን በመመርመር፣ በምክር ቤቱ የውሳኔ ሐሳብ እንደሚያቀርብ በተሻሻለው የምክር ቤቱ የአሠራርና የአባላት ሥነ ምግባር ደንብ ቁጥር 1/1999 ኃላፊነት የተሰጠው በመሆኑ የክልሉን ውሳኔ በመመርመር እንደተቀበለው ገልጿል፡፡

ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ኃላፊነት በመውሰድ ጥናት ጀምሮ የነበረው አጥኚ ቡድንና የክልሉ ምክር ቤት ባካሄደው ጥናት ላይ በመመሥረት ያሳለፈው ውሳኔ ተመሳሳይነት ያላቸው በመሆኑ፣ ተጨማሪ ጥያቄውን የክልሉ መንግሥት በቀደመው አግባብ ቢመልሰው ችግር እንደማይኖረውም ቋሚ ኮሚቴው እምነቱ እንደሆነ ገልጿል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ በኦሮሚያ ክልል ዝዋይ ሐይቅ ደሴት ላይ የሚኖሩት የዛይ ማኅበረሰብ የማንነትና ራስን የማስተዳደር ጥያቄ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት አቅርበዋል፡፡ የምክር ቤቱ የሕገ መንግሥትና የክልሎች ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ አባል የሆኑት የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባዔ፣ የክልሉ መንግሥትና ምክር ቤት የዛይ ማኅበረሰብ ጥያቄን በተመለከተ ውይይት እያደረጉ መሆኑን በመጥቀሳቸው ጉዳዩ ለክልሉ ተትቷል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ባለሙያዎች ኮሚሽን ሪፖርት ምን ይዟል?

ለአሜሪካ ድምፅ አማርኛ ዝግጅት የስልክ አስተያየት የሰጡ አንድ የደንበጫ...

መንግሥት በአማራ ክልል ለወደሙ የአበባ እርሻዎች ድጋፍ እንዲያደርግ ተጠየቀ

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአማራ ክልል የተፈጠረው ግጭትና አለመረጋጋት በቢዝነስ...

አምናና ዘንድሮ!

እነሆ መስከረም ጠብቶ በአዲስ መንፈስ ተሞልተን መንገድ ጀምረናል። ‹‹አዲስ...