– ዋጋው በጣም ውድ ነው ተብሏል
ዶ/ር አርከበ ዕቁባይ ‹‹ሜድ ኢን አፍሪካ ኢንዱስትሪያል ፖሊሲ ኢን ኢትዮጵያ›› በሚል ርዕስ ያሳተሙት አዲስ መጽሐፍ፣ በኢትዮጵያ ገበያ ቀረበ፡፡
መጽሐፉ በዓለም ገበያ ግንቦት 19 ቀን 2007 ዓ.ም. የቀረበ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ውስጥ በቡክ ወርልድ አማካይነት ገበያውን ተቀላቅሏል፡፡
ዋቢና ኢንዴክስን ጨምሮ 348 ገጽ ያለው ይህ የዶ/ር አርከበ ዕቁባይ መጽሐፍ፣ ከአፍሪካ አጠቃላይ ሁኔታ በመነሳት የኢትዮጵያን ኢንዱስትሪ በጥልቀት ይተነትናል፡፡
ዶ/ር አርከበ ለዚህ መጽሐፍ መነሻ የሆናቸው በለንደን ስኩል ኦፍ ኦርየንታል ኤንድ አፍሪካን ስተዲስ ለተከታተሉት የዶክትሬት ዲግሪ ማሟያ ያቀረቡት ጽሑፍ ነው፡፡
ዶ/ር አርከበ በአራት ዓመት የሚጠናቀቀውን ትምህርታቸውን በዩኒቨርሲቲው ባልተለመደ ሁኔታ በ23 ወራት ውስጥ በከፍተኛ ማዕረግ በማጠናቀቃቸው፣ በወቅቱ ከፍተኛ አድናቆትን ተችሯቸው እንደነበር ይታወሳል፡፡
የተመረቁበትን ዴቨሎፕመንት ስተዲስ የዶክትሬት ዲግሪ የጥናት ጽሑፍ በማስፋት በመጽሐፍ መልክ ያዘጋጁት ሲሆን፣ የተማሩበት ለንደን ስኩል ኦፍ ኦርየንታል ስተዲስ ይኼንን መጽሐፍ እንዲታተም ለኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ ልኮታል፡፡
ለዶ/ር አርከበ ቅርበት ያላቸው የሪፖርተር ምንጮች እንደገለጹት፣ ዶ/ር አርከበ ይኼንን መጽሐፍ ያዘጋጁት በዘርፉ ጥልቅ ጥናት አካሂደው ነው፡፡
ዶ/ር አርከበ መጽሐፉን ለማዘጋጀት በ150 ኩባንያዎች ላይ ጥልቅ ጥናት ማድረጋቸው፣ ሃምሳ ፋብሪካዎችን በአካል በመገኘት ማጥናታቸው፣ ለዚሁ ጽሑፍ 250 ጥያቄዎችን በማዘጋጀት ከፋብሪካዎች መረጃ እንደሰበሰቡና ከሁለት እስከ አራት ሰዓት የፈጁ 200 ቃለ መጠይቆችን ማድረጋቸው ተሰምቷል፡፡ ለኢንዱስትሪ ልማት ማነቆ ናቸው የተባሉ ችግሮችን ለመለየት በውጭና በአገር ውስጥ የሚገኙ ፋብሪካዎች ላይ ጥናት ማድረጋቸው እንዲሁ ተነግሯል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በሌሎች ጥናቶች መረጃ ሆነው ያልቀረቡ አንድ ሺሕ ሰነዶችን በማገላበጥ የተሟላ ጥናት ማድረጋቸውን ምንጮች ገልጸዋል፡፡ ይህ አጠቃላይ ጥናት አራት ዓመት የፈጀ መሆኑም ተገልጿል፡፡
ይህ የዶ/ር አርከበ መጽሐፍ የተወሳሰቡ የኢንዱስትሪ ፖሊሲ ሐሳቦችን በጥልቅ አረዳድ የተነተነ ነው ሲሉ አስተያየት ሰጪዎች ገልጸዋል፡፡ ይህ ሊሆን የቻለው ‹‹ጸሐፊው በንድፈ ሐሳብ ብቻ ሳይሆን በተግባራዊ ልምዳቸውና በፖሊሲ ቀረፃ የረዥም ጊዜ ልምድ ስላላቸው ነው፤›› በማለት የካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ሀ ጁን ቻንግ ለመጽሐፉ ያላቸውን አድናቆት በመጽሐፉ ላይ ገልጸዋል፡፡
የቀድሞ የዓለም ባንክ ዋና ኢኮኖሚስት ጀስቲን ይፋ ሊን በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ በልማት ተዓምር እየፈጠረች በመሆኑ ለአፍሪካ አገሮች መነቃቃት፣ በራስ መተማመንና መልካም ተሞክሮ ማካፈል ትችላለች ያሉ ሲሆን፣ ዶ/ር አርከበ ይኼን ለውጥ በመጽሐፉ በግሩም ሁኔታ እንደተረኩት መስክረዋል፡፡ ጃፓን ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ለምሥራቅ እስያ አገሮች ምሳሌ እንደሆነችው ሁሉ፣ ኢትዮጵያ ለአፍሪካ አገሮች ተመሳሳይ አስተዋጽኦ ማበርከት ትችላለች ብለዋል፡፡ መጽሐፉ ኢትዮጵያ ዕድገቷን እንዴት እያፋጠነችና ባለሁለት አኃዝ ዕድገት እያስመዘገበች እንደመጣች፣ ጥልቅ ግንዛቤ ይሰጣል በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
መጽሐፉ በእንግሊዝ ገበያ ውስጥ 55 ፓውንድ ሲሸጥ ኢትዮጵያ ውስጥ ደግሞ 1,815 ብር በመሸጥ ላይ ይገኛል፡፡
ከቡክ ወርልድ የተገኘው መረጃ እንደሚያሳየው፣ የመጽሐፉ ዋጋ መወደዱን ከተለያዩ አቅጣጫዎች አስተያየት እየተሰጠበት ነው፡፡ መጽሐፉ ሊወደድ የቻለው ሐርድ ከቨር ያለውና ደረጃውን ጠብቆ በመታተሙ፣ እንዲሁም በጣም የተለፋበት በመሆኑ ነው ተብሏል፡፡
መጽሐፉ በዋነኛነት ትኩረት የሚያደርገው በኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ መዋቅራዊ ለውጥ ለማምጣት መሄድ ባለባቸው አቅጣጫዎች ላይ ነው፡፡ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ዘርፍን ማሳደግ ለግብርና የላቀ ዕድገት ወሳኝ መሆኑም ተተንትኗል፡፡
ዶ/ር አርከበ በመጽሐፉ መግቢያ ላይ እንደጠቀሱት፣ በመጽሐፉ ያንፀባረቋቸው ምልከታዎች የመንግሥትንም ሆነ አብረዋቸው እየሠሩባቸው ወይም የሠሩባቸው ተቋማትን አይወክሉም፡፡ የመጽሐፉ ዋናው ዓላማ የተለያዩ ምልከታዎች፣ ልምዶችና ተግዳሮቶችን ለማቅረብ ለተጨማሪ ጥናትና ውይይት መጋበዝ መሆኑም ተገልጿል፡፡