ከአዲስ አበባ እስከ ጂቡቲ ወደብ ድረስ የተዘረጋው የባቡር መስመር ጥቅምት 2008 ዓ.ም. ሥራ የሚጀምር ቢሆንም፣ ለአገሪቱ ኢኮኖሚ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሊያበረክት የሚችለውን ነዳጅ ለማጓጓዝ፣ የሚያስፈልገው የመሠረተ ልማት ቀደም ብሎ አለመጠናቀቁ አለመግባባት ፈጠረ፡፡
ኢትዮጵያ የምትጠቀመው አብዛኛው ነዳጅ የሚገባው በጂቡቲ በኩል ሲሆን የሚጫነውም ከሆራይዘን ተርሚናል ነው፡፡ ነገር ግን የተገነባው የባቡር መስመር ቀጥታ ወደ ጂቡቲ ወደብ የሚያመራ ነው፡፡ የአገሪቱ ነዳጅ ወደሚጫንበት ሆራይዘን ተርሚናል የባቡር ሐዲድ አለመገንባቱ አለመግባባት መፍጠሩን የሪፖርተር ምንጮች ገልጸዋል፡፡
ከሆራይዘን ተርሚናል ባቡሩ ነዳጅ ቢጭን እንኳን የተጫነው ነዳጅ ኢትዮጵያ ከደረሰ በኋላ የሚያራግፍበት ዲፖ አለመገንባቱ ሌላ ችግር እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ ጉዳዩ ላይ የበለጠ አለመግባባት የፈጠረው የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን፣ የትራንስፖርትና የዕቃ ማጓጓዣ ባቡሮችን እንዲያመርት ከቻይናው ኩባንያ ኖሪንኮ ጋር አስቀድሞ ውል መግባቱ ነው፡፡ ኖሪንኮ በበኩሉ ከአገር በቀሉ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ጋር በገባው ውል መሠረት ከ50 በላይ የሚሆኑ የነዳጅ ማመላለሻ ባቡር ፉርጎዎች ተመርተው ለሥራ ዝግጁ መሆናቸውን እየገለጸ ነው፡፡
የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ኢንተርፕራይዝ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ታደሰ ኃይለ ማርያም ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የእሳቸው ኩባንያ ከውጭ ነዳጅ ገዝቶ ጂቡቲ ሆራይዘን ተርሚናል ያራግፋል፡፡ ከዚህ በኋላ የነዳጅ ኩባንያዎች በተሽከርካሪዎች ለአገር ውስጥ ገበያ ያቀርባሉ፡፡ ነገር ግን ነዳጅን በባቡር ለማጓጓዝ ወደ ሆራይዘን ተርሚናል የሚጓዝ የባቡር ሐዲድ አልተገነባም፡፡ በአገር ውስጥም ማጠራቀሚያ ዲፖ አልተገነባም፡፡ ‹‹ጉዳዩ በደንብ መታየት ነበረበት፡፡ ትንሽ ክፍተት አለው፤›› በማለት አቶ ታደሰ የጉዳዩን አሳሳቢነት ገልጸዋል፡፡
ይህ ጉዳይ ክፍተት እንዳለው ዘግይቶ የተገነዘበው ትራንስፖርት ሚኒስቴር አጀንዳ ቀርጾ መሠረተ ልማት ለማሟላት ውይይት ማካሄድ መጀመሩ ታውቋል፡፡
ትራንስፖርት ሚኒስቴር፣ በሥሩ የሚገኘውን ትራንስፖርት ባለሥልጣን፣ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን፣ የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ኢንተርፕራይዝንና አሥሩን ነዳጅ አከፋፋይ ኩባንያዎች በማሰባሰብ በመፍትሔ ሐሳቦች ላይ እየተነጋገረ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በዋናነት የቀረበው መፍትሔ ከጂቡቲ ወደብ ወደ ሆራይዘን ተርሚናል የሚወስድ የባቡር ሐዲድ መዘርጋትና በሆራይዘን ተርሚናል ባቡሮቹ ነዳጅ የሚጭኑባቸውን መሣሪያዎች ማሟላት ነው፡፡
በአገር ውስጥ ደግሞ አዲስ አበባ (ሰበታ) አካባቢ በሚገኘው ግዙፍ የባቡር ተርሚናል ውስጥ የነዳጅ ማራገፊያ ዲፖ መገንባት ዋነኛ ጉዳይ ሆኗል፡፡ በአሁኑ ወቅት እነዚህ ጉዳዮች በውይይት ላይ የሚገኙ ሲሆን፣ ግንባታዎቹን ለማካሄድ የበጀት ጉዳይ ቀጣዩ መነጋገሪያ ይሆናል ተብሏል፡፡
ምንጮች እንደገለጹት፣ በጀት ተወስኖ የግንባታ ቦታ ከተዘጋጀ ግንባታው ከሁለት እስከ ሦስት ዓመት የሚፈጅ በመሆኑ፣ በባቡር መሠረተ ልማት ነዳጅ ለማመላለስ ረዥም ጊዜ ሊወስድ ይችላል፡፡ ይህ ፕሮግራም ቀድሞ ባለመታሰቡ ብቻ የተገነባው የባቡር መሠረተ ልማት ላልተወሰነ ጊዜ ነዳጅ ከማመላለስ ውጪ ይሆናል፡፡
በጂቡቲ ሆራይዘን ተርሚናል ነዳጅ በተሽከርካሪ የሚያቀርቡ ኩባንያዎች አሥር ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ኢንተርፕራይዝ በወር በ250 ሚሊዮን ዶላር ወጪ በሚያቀርበው ነዳጅ ትልቅ ድርሻ ያላቸው ኖክ፣ ቶታል፣ ኦይል ሊቢያና የተባበሩት ናቸው፡፡ እነዚህና ሌሎች ስድስት ኩባንያዎች በመላው አገሪቱ ባላቸው ከ250 በላይ ነዳጅ ማደያዎች አማካይነት ነዳጅ ሲያቀርቡ ቆይተዋል፡፡
ሰበታ አካባቢ የነዳጅ ዲፖ እንደሚገነባ የሚጠበቀው በግል ኩባንያዎቹ ሲሆን፣ የምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ከጂቡቲ ነዳጅ እያጓጓዙ በዲፖው የማራገፍ ኃላፊነት እንዳለበት ይጠበቃል፡፡ ኩባንያዎቹ ደግሞ በተሽከርካሪዎች ወደ ነዳጅ ማደያዎች ያደርሳሉ በሚለው ዕቅድ ላይ ውይይት እየተካሄደ መሆኑም ታውቋል፡፡
ከአዲስ አበባ (ሰበታ) እስከ ጂቡቲ ወደብ ድረስ የተዘረጋው የባቡር መስመር 656 ኪሎ ሜትር ርዝመት አለው፡፡ መስመሩ እስከ አዳማ ድረስ ሁለት ባቡሮች በአንዴ የሚያስተናግድ ሲሆን፣ ከአዳማ እስከ ጂቡቲ ድረስ ደግሞ አንድ መስመር ይኖረዋል፡፡
የባቡር መስመሩ ለመንገደኞችና ለዕቃ አገልግሎት የሚሰጥ በመሆኑ የትራንስፖርት ወጪን በ50 በመቶ ይቀንሳል ተብሏል፡፡ በሁለት የቻይና ኩባንያዎች እየተገነባ ያለው ይህ የባቡር መስመር የሐዲድ ማንጠፍ ሥራው የተጠናቀቀ በመሆኑ፣ በመጪው ጥቅምት አገልግሎት መስጠት ይጀምራል ተብሏል፡፡ ነዳጅ ለማጓጓዝ በተፈጠረው ክፍተት ላይ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር ጌታቸው በኩረ አስተያየት እንዲሰጡ የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡