አንድ ሰው አንዲት በጣም ቆንጆ ወፍ በመዳፉ ውስጥ ይዞ ጨምቆ ሊገድላት ሲል ከመሞቷ በፊት አንድ ወይም ሁለት ቃላት ትናገር ዘንድ እንዲፈቅድላት ጠየቀችው፡፡
እንዲህም አለች “እባክህ አትግደለኝ፡፡ ሦስት ጠቃሚ ምክሮችን እሰጥሃለሁ፡፡ የመጀመሪያው ምክር፤ በእጅህ ያለውን ነገር አትልቀቅ፡፡ ሁለተኛው ምክር፤ ስለሆነው ነገር ሁሉ አትቆጭ፤” ካለችው በኋላ ዝም አለች፡፡
ሦስተኛውንም ምክር ትነግረው ዘንድ ሲጠይቃት “ሦስተኛው ምክር ለልጆችህና ለልጅ ልጆችህ በጣም ጠቃሚ ስለሆነ ካለቀከኝ አልነግርህም፤” አለችው፡፡
በዚህ ጊዜ ሰውየው ሦስተኛውን ምክር ለመስማት በጣም ጓጉቶ ስለነበረ ወፏን ሲለቃት ከአንድ ዛፍ ላይ በርራ ወጥታ “ምንድን ነበር ያልኩህ? ታስታውሳለህ?” ብላ ጠየቀችው፡፡ እርሱም “በእጅህ ያለውን ነገር አትልቀቅ ነው ያልሺኝ፡፡” አላት፡፡
“ሁለተኛውስ?”
“ስላለፈው ነገር ሁሉ አትቆጭ፡፡”
“አዎ፡፡ ነገር ግን የነገርኩህን ነገር አልተቀበልክም፡፡ ባትለቀኝ ኖሮ ከሆዴ ውስጥ ለልጅ ልጆችህ የሚሆን ወርቅ ታገኝ ነበር፡፡ ይኸው ነው፤” አለችው፡፡
ሰውየው “ሦስተኛውስ ታዲያ?” አላት፡፡
እሷም “ሦስተኛው የሁለተኛው ምክር ድጋሚ ነው፡፡ ስላጣኸው ነገር አትቆጭ፡፡ ይኸው ነው፡፡ ደህና ሁን፡፡ ምክሬንም ባለመቀበልህ በድህነት ትኖራለህ፤” አለችው፡፡
- የካፋ ወግ