Friday, September 22, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ለመልካም አስተዳደር ዕጦትና ለሙስና ትኩረት እንዲሰጥ ተጠየቀ

ሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ለመልካም አስተዳደር ዕጦትና ለሙስና ትኩረት እንዲሰጥ ተጠየቀ

ቀን:

ሰሞኑን ለውይይት የቀረበው ሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ በርካታ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ቢያቅፍም፣ ሙስናና የመልካም አስተዳደር እጦት ሥጋት እንደሆነበት ተገለጸ፡፡

ከአብዛኛዎቹ ተሰብሳቢዎች ጐልተው የተነሱ ነጥቦች ይህንን ግዙፍ ብሔራዊ ዕቅድ ለመተግበር፣ ቅድሚያ የመልካም አስተዳደርና የሙስና ጉዳዮች መፍትሔ ሊያገኙ እንደሚገባ የሚገልጹ ናቸው፡፡

አስተያየት ሰጪዎቹ እንደሚሉት፣ በአዲስ አበባና በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች የመልካም አስተዳደር እጦት ተባብሷል፡፡ ሙስና የዕለት ተዕለት ክስተት እየሆነ መምጣቱ በምሬት ተገልጿል፡፡

መንግሥት የቀረፀው የዚህ ግዙፍ ፕሮጀክት ስኬት በቀጥታ ከመልካም አስተዳደር ጋር የሚገናኝ በመሆኑ፣ አገርን በማዳን አስተሳሰብ ላይ የተመሠረተ ዕርምጃ ሊወሰድ ይገባል በማለት አስተያየት የሰጡ በርካታ ናቸው፡፡

ከጥቂት ቀናት በኋላ የሚጠናቀቀው የመጀመሪያው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ይዞ መቅረቡ ይታወሳል፡፡

ከእነዚህ መካከል አሥር የስኳር ፕሮጀክቶች፣ ከሁለት ሺሕ ኪሎ ሜትር በላይ የሚሸፍን አዲስ የባቡር መስመር ግንባታ፣ ታላቁ የህዳሴ ግድብና የማዳበሪያ ፋብሪካዎች ተጠቃሾች ናቸው፡፡

በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ እነዚህ ፕሮጀክቶች ተስፋፍተው እንደሚቀጥሉ፣ ቀደም ባለው ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ውስጥ ያልነበሩ የፔትሮሊየምና የኬሚካል ፋብሪካዎች ይገነባሉ ቢባልም፣ ከመጀመሪያው ዕቅድ ተነጥሎ ሊታሰብ የሚያስችለው ዓይነተኛ መለያ የለውም ተብሏል፡፡

ይህ ሐሳብ ባለፈው ረቡዕና ሐሙስ በአዲስ አበባ ባህልና ቴአትር አዳራሽ በተካሄደው የዕቅድ ሰነድ ውይይት፣ የኢሕአዴግ የውጭ ግንኙነት ኃላፊ የነበሩትና በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ የፖሊሲ ጥናትና ምርምር ኢንስቲትዩት የአንድ ክፍል ኃላፊ የሆኑት አቶ ሴኮቱሬ ጌታቸው በሰጡት አስተያየት፣ የመጀመሪያው ዕቅድ ሜጋ ፕሮጀክቶችን ይዞ በመቅረቡ ብሔራዊ መነሳሳት ፈጥሯል ብለው፣ የአሁኑ ዕቅድ ፕሮጀክቶችን ቢይዝም ከመጀመሪያው ዕቅድ ጋር በግልጽ የተቀመጠ ልዩነት የለውም በማለት አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

‹‹እኛ የምንከተላቸው ልማታዊ መንግሥታት አንድ ዕቅድ አጠናቀው ሌላ ሲያቅዱ ልዩነቱ በግልጽ ይታያል፤›› በማለት የተናገሩት አቶ ሴኮቱሬ፣ ‹‹እኛም ብሔራዊ መነሳሳት ለመፍጠር ልዩነቱን በግልጽ በማውጣት ብሔራዊ ግብ ልናስቀምጥ ይገባል፤›› ብለዋል፡፡

አቶ ሴኮቱሬ ቢካተቱ ያሏቸውን ሐሳቦችም ሰንዝረዋል፡፡ ከሰነዘሯው ሐሳቦች ብሔራዊ አገልግሎት አንዱ ነው፡፡ ‹‹በወታደራዊው መንግሥት የሥልጣን ዘመን ብሔራዊ ውትድርና መጥፎ ጠባሳ ጥሎ ቢያልፍም፣ በአሁኑ ወቅት በሩቁ ከምንሸሸው በበጐ ጐኑ ልንጠቀምበት ይገባል፤›› ካሉ በኋላ፣ በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የሚገኙ ተማሪዎች ከመመረቃቸው በፊት ለተወሰኑ ጊዜያት ወደመጡበት ኅብረተሰብ ተመልሰው እንዲያገለግሉ ቢደረግ ጥቅሙ የጐላ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ ‹‹ይህ ሁኔታ ኅብረተሰቡን ከመጥቀሙ ባሻገር ተማሪዎቹ ከፍተኛ ዕውቀት የሚያገኙበት ይሆናል፡፡ በአገራቸው እንዲኮሩም ያደርጋል፤›› ብለዋል፡፡

ስብሰባውን ይመሩ የነበሩት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ድሪባ ኩማ ለአቶ ሴኮቱሬ አስተያየት ምላሽ ሲሰጡ፣ የብሔራዊ አገልግሎት ጉዳይ እንደ ስትራቴጂ ሊወሰድ ይችላል ብለዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ ይበልጥ በመነጋገር የሚያዋጣውን ማየት ይቻላል ካሉ በኋላ፣ በኢትዮጵያ ይህንን ጉዳይ መተግበር አዋጭ ስለመሆኑ ከባህልና ከታሪክ አንፃር መርመር ያስፈልጋል በማለት አክለዋል፡፡ አቶ ድሪባ ጉዳዩ ከኢሕአዴግ መስመር ጋር ያለውን ልዩነትም አስረድተዋል፡፡

‹‹ኢትዮጵያ የምትከተላቸው ሌሎች አገሮች ልማታዊ መንግሥት ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ ግን ልማታዊ ዴሞክራሲን የምትከተል በመሆኑ ጉዳዩን በጥልቀት ማየት ያስፈልጋል፤›› በማለት አቶ ድሪባ ተናግረዋል፡፡

በዕለቱ በተካሄደው ስብሰባ አብዛኛዎቹ ተሰብሳቢዎች በትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ ጥልቅ ሐሳቦች ላይ አስተያየት ከመሰንዘር ይልቅ፣ ብዙም ግንኙነት በሌላቸው የዕለት ተዕለት ጉዳዮች ላይ አስተያየት ሲሰጡ ተስተውለዋል፡፡

በዚህ ጉባዔ የአምስት ዓመቱን ዕቅድ ያቀረቡት በሚኒስትር ዴኤታ ማዕረግ የብሔራዊ ፕላን ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ጌታቸው አዳም ሲሆኑ፣ ከአቶ ድሪባ ጋር መድረኩን የመሩት የግብርና ሚኒስትሩ አቶ ተፈራ ደርበው ናቸው፡፡ የትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ 192 ገጽ ያለው ሲሆን፣ ለውይይት የቀረበው በ65 ገጽ ተጨምቆ መሆኑን አቶ ጌታቸው ተናግረዋል፡፡    

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ባለሙያዎች ኮሚሽን ሪፖርት ምን ይዟል?

ለአሜሪካ ድምፅ አማርኛ ዝግጅት የስልክ አስተያየት የሰጡ አንድ የደንበጫ...

መንግሥት በአማራ ክልል ለወደሙ የአበባ እርሻዎች ድጋፍ እንዲያደርግ ተጠየቀ

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአማራ ክልል የተፈጠረው ግጭትና አለመረጋጋት በቢዝነስ...

አምናና ዘንድሮ!

እነሆ መስከረም ጠብቶ በአዲስ መንፈስ ተሞልተን መንገድ ጀምረናል። ‹‹አዲስ...