የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር ለሚያስገነባው አዲስ ቴአትር ቤት የመሠረት ድንጋይ ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. ተጥሏል፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኰንንና የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሩ አቶ አሚን አብዱልቃድር በቴአትር ቤቱ ቅጥር ግቢ ተገኝተው የመሠረት ድንጋዩን አኑረዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር ዋና ዳይሬክተር አቶ ተስፋዬ ሽመልስ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የቴአትር ቤቱ ግንባታ በጥቅምት 2008 ዓ.ም. የሚጀመር ሲሆን፣ ከሦስት ዓመታት በኋላ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የመሠረተ ድንጋዩ መጣል ቴአትር ቤቱ በኅዳር 2008 ዓ.ም. ለሚያከብረው 60ኛ ዓመት የአልማዝ ኢዮቤልዩ ክብረ በዓል መነሻ እንደሆነም አክለዋል፡፡ የቴአትር ቤቱን 60ኛ ዓመት ክብረ በዓል ምክንያት በማድረግ ከሚካሄዱ መርሐ ግብሮች አንዱ ለቴአትር ቤቱ አንጋፋ ባለሙያዎች ሽልማት መስጠት ነው፡፡
መሠረተ ድንጋዩ በተጣለበት ዕለት ሽልማትና እውቅና መሰጠቱ ተጀምሯል፡፡ ቴአትር ቤቱን ለረዥም ዓመታት ያገለገሉና አሁንም በማገልገል ላይ ላሉ አሥር ባለሙያዎች ሽልማት ተበርክቷል፡፡ ከእነዚህ መካከል መርአዊ ስጦት፣ ጌታቸው ደባልቄና ታደለ ታምራት ይጠቀሳሉ፡፡ በቴአትር ቤቱ የሚሠሩና በአገልግሎታቸው የተመሰገኑ 16 ሠራተኞችም ተሸልመዋል፡፡ ሽልማቱ እስከ 60ኛ ዓመት ክብረ በዓሉ የሚቀጥል ይሆናል፡፡
አቶ ተስፋዬ እንደተናገሩት፣ 500 ሚሊዮን ብር ያወጣል የተባለው የቴአትር ቤቱ ሕንፃ መሠረተ ድንጋይ ሳይጣል የዘገየው በዲዛይኑ መስተካከል ያለባቸው ነገሮች ስለነበሩና በግንባታው ላይ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ውይይት ላይ ስለነበሩ ነው፡፡ የቴአትር ቤቱ የመድረክ ግንባታ፣ የመብራት ሥራና ሌሎችም በአገር ውስጥ የውጭ ባለሙያዎች የሚሠሩ ይሆናል ብለዋል፡፡
ቴአትር ቤቱ ለአዲሱ ሕንፃ ግንባታ ካወዳደራቸው ስምንት ተቋሞች መካከል ያሸነፈውን አዲስ መብራቱ ኮንሰልቲንግ አርክቴክትስ ኤንድ ኢንጂነርስ ጳጉሜ 1 ቀን 2006 ዓ.ም. ማሳወቁ ይታወሳል፡፡