Friday, September 29, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊበሁለቱ የጡረታ አዋጆች ላይ የተካተተው ማሻሻያ ከፕሬዚዳንቱ ሥልጣን ጋር ይጋጫል የሚል ክርክር...

በሁለቱ የጡረታ አዋጆች ላይ የተካተተው ማሻሻያ ከፕሬዚዳንቱ ሥልጣን ጋር ይጋጫል የሚል ክርክር አስነሳ

ቀን:

በግል ድርጅት ሠራተኞች የጡረታ አዋጅና በመንግሥት ሠራተኞች የጡረታ አዋጅ ላይ የተደረጉ ማሻሻያዎችን እንዲያፀድቅ ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. የቀረበለት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማሻሻያዎቹን ቢቀበላቸውም፣ ተፈጻሚ የሚሆኑበት ጊዜ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ከመፈረማቸውና በነጋሪት ጋዜጣ ከመታወጃቸው በፊት ሊሆን አይገባም የሚል ክርክር ተነሳ፡፡

ምክር ቤቱ ሰኔ 29 ቀን ባደረገው ጉባዔ ካፀደቋቸው ረቂቅ አዋጆች መካከል፣ የመንግሥት ሠራተኞች ጡረታ አዋጅና የግል ድርጅት ሠራተኞች ጡረታ አዋጅ ላይ የተደረጉት ማሻሻያዎች ይገኙበታል፡፡ ከሁለቱ አዋጆች መካከል የግል ድርጅቶች ጡረታ አዋጅ ማሻሻያ ቀደም ሲል አማራጭ አድርጎ ያቀረበውን የፕሮቪደንት ፈንድ ሥርዓት የሚያነሳ አንቀጽ በማካተቱ፣ በርካታ ድርጅቶች ተቃውሟቸውን ሲገልጹ ቆይተዋል፡፡ ከዚህም ውጪ ይህ አዋጅ በመንግሥት ድርጅቶች የተጠራቀሙ በፕሮቪደንት ፈንድ የሚተዳደር ገንዘብ ወደ ግል ጡረታ እንዲዘዋወር የሚል አንቀጽ በማስገባቱ፣ ከፍተኛ ሥጋትን በግል ሠራተኞች ላይ ፈጥሮ ነበር፡፡

ይህንን ሥጋት የቀረፈ ማሻሻያ ፓርላማው አንቀጹን በመሠረዝ ያደረገ ቢሆንም፣ በፕሮቪደንት ፈንድ የታቀፉ ድርጅቶች አሁንም በምርጫው ይቀጥሉ የሚለውን ጥያቄ ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡ ሁለቱ አዋጆች ላይ ማሻሻያ ያቀረቡት የመንግሥት ድርጅቶች ጡረታ ኤጀንሲና የግል ድርጅቶች ሠራተኞች ጡረታ ኤጀንሲ አዋጆቹ የሚፀኑበትን ጊዜ በነጋሪት ጋዜጣ ታትመው ከወጡ በኋላ በሚል አስቀምጠው የነበረ ቢሆንም፣ የፓርላማው የማኅበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴና የሕግ፣ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሁለቱም አዋጆች ከሐምሌ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ የፀኑ ይሆናል በሚል አሻሽለውታል፡፡

ጉዳዩን በተመለከተ አንድ የፓርላማ አባል፣ ‹‹አዋጆች ተፈጻሚ መሆን የሚጀምሩት በሕገ መንግሥቱ መሠረት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ፈርመውበት በነጋሪት ጋዜጣ ታውጆ ነው፡፡ ይህ ማሻሻያ አዋጅ የተለየ አሠራር ያመጣው ለምንድነው?›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ ማሻሻያ አዋጁ እንዲፀድቅ ለፓርላማው የውሳኔ ሐሳብ ያቀረቡት የማኅበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወይዘሮ አበባ ዮሴፍ፣ ከበጀት ዓመቱ ጋር የተጣጣመ ለማድረግ እንዲሆን ጠቁመው፣ የበለጠ ግን በምክር ቤቱ የሚገኙ የሕግ ባለሙያዎች አስተያየት እንዲሰጡበት ጠይቀዋል፡፡

በዚሁ መሠረት የሕግ ባለሙያዎች አስተያየት እንዲሰጡ አፈ ጉባዔው በጋበዙት መሠረት፣ የምክር ቤቱ የመከላከያና የውጭ ግንኙነት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ተስፋዬ ዳባ የተነሳውን የሕገ መንግሥት ጥያቄ በመደገፍ መስተካከል እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ ‹‹ሕገ መንግሥት የመሸርሸር ጉዳይ እንዳይሆን ፍርኃት አለኝ፡፡ በሕገ መንግሥቱ ለፕሬዚዳንቱ ከተሰጡ ሥልጣኖች ውስጥ አንዱ ይኼ ነው፤›› በማለት ሐሳባቸውን ገልጸዋል፡፡

በማከልም ሕግ ሲወጣ በተቻለ መጠን ምንም ዓይነት ውዥንብር መፍጠር እንደሌለበት የተናገሩት አቶ ተስፋዬ፣ ‹‹አዋጁ ተፈጻሚ መሆን ያለበት በፕሬዚዳንቱ ተፈርሞ በነጋሪት ጋዜጣ ከወጣ በኋላ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹ከሐምሌ 1 ቀን ጀምሮ ተፈጻሚ ቢሆን ዓላማው ገንዘብ የመሰብሰብ ያስመስለዋል፡፡ ስለዚህ አሠራራችንን ባንጥስ የሚል አስተያየት አለኝ፤›› ብለዋል፡፡ ሌላኛው የሕግ ባለሙያ የፓርላማው፣ የሕግ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢና የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ አቶ አስመላሽ ወልደ ሥላሴ፣ ‹‹የሕግ ክርክር ለማንሳት አይደለም፡፡ በዚህ ምክር ቤት ሥልጣንና ኃላፊነት መሠረት አዋጆች የሚፀኑበትን ቀን ማስቀመጥ ይቻላል፡፡ ሳያስቀምጥም ዝም ሊል ይችላል፡፡ ከአንድ ዓመት በኋላ ተፈጻሚ ሊሆን ይችላል ብሎ ሊወስንም ይችላል፤›› በማለት ተቃርነዋል፡፡

ሕገ መንግሥቱ የሚለው ፕሬዚዳንቱ በ15 ቀናት ውስጥ ይፈርማሉ እንጂ፣ ከአሥራ አምስተኛው ቀን በኋላ እንደማይል የተናገሩት አቶ አስመላሽ፣ ከሐምሌ 1 ቀን ጀምሮ የፀና ይሆናል መባሉ ፕሬዚዳንቱን ከመፈረም እንደማያግዳቸው ተናግረዋል፡፡ ‹‹ጉዳዩ የፕሮሲጀር ጉዳይ ስለሆነ ምክር ቤቱ በቀረበው መልኩ ቢቀበለው ችግር የለውም፡፡ ከሕገ መንግሥቱም ሆነ ከሌሎች ሕጎች ጋር አይጋጭም፤›› ብለዋል፡፡ በዚሁ የአቶ አስመላሽ ማብራሪያ መሠረት የመንግሥት ጡረታ አዋጅ ላይ የተደነገገው ማሻሻያ ላይ ተቃውሞ አቅርበው የነበሩትን አቶ ተስፋዬ ዳባን ጨምሮ፣ በሰጡት ድምፅ ያለ ተቃውሞ በሙሉ ድምፅ ፀድቋል፡፡

ቀጥሎ የቀረበው የግል ድርጅቶች ማሻሻያ የውሳኔ ሐሳብም በተመሳሳይ አዋጁ ከሐምሌ 1 ቀን ጀምሮ እንዲፀና የሚጠይቅ ነው፡፡ ይህ የውሳኔ ሐሳብ በቀረበበት ወቅት በድጋሚ ዕድል ያገኙት አቶ ተስፋዬ ዳባ፣ ‹‹አቶ አስመላሽ ያነሱትን መከራከሪያ አከብራለሁ፤›› ብለዋል፡፡ አክለውም እርሳቸው የተለከቱት ከመብት አንፃር መሆኑን፣ አቶ አስመላሽ ደግሞ ከሥነ ሥርዓት (Procedure) አንፃር መሆኑን በዚህም መሠረት፣ ‹‹ሁለታችንም ኤ ነው ያገኘነው›› በማለት ምክር ቤቱን ፈገግ አሰኝተዋል፡፡

ጉዳዩን በተመለከተ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የሕግ ባለሙያዎች ግን አዋጆች ተፈጻሚ መሆን ያለባቸው በነጋሪት ጋዜጣ ከታተሙ በኋላ መሆን እንዳለበት ይከራከራሉ፡፡ ፓርላማው ራሱ ያወጣው የፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ ማቋቋሚያ አዋጅ 3/1995 አንቀጽ 2(2) ማናቸውም የፌዴራል መንግሥት ሕግ የሚወጣው በፌዴራሉ ነጋሪት ጋዜጣ ይሆናል እንደሚል፣ በነጋሪት ጋዜጣ የወጣን ሕግ ማንኛውም ኅብረተሰብ የማወቅና የመቀበል ኃላፊነት እንዳለበት ይገልጻሉ፡፡

በዚሁ ማቋቋሚያ አዋጅ አንቀጽ 2(3) ላይ፣ ‹‹ማናቸውም የፌዴራል ወይም የክልል ሕግ አውጪ፣ አስፈጻሚና ተርጓሚ እንዲሁም ማንኛውም የተፈጥሮ ሰው ወይም በሕግ የሰውነት መብት የተሰጠው አካል በፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ የሚወጣ ሕግን የመቀበል ግዴታ ይኖርበታል፤›› እንደሚል የሚጠቅሱት የሕግ ባለሙያዎች፣ ፓርላማው ያፀደቀውን ሕግ ኅብረተሰቡ አውቆታል ተብሎ የሚገመተው በነጋሪት ጋዜጣ ከወጣ በኋላ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡

በመሆኑም በነጋሪት ጋዜጣ ያልወጣን ሕግ ከሐምሌ 1 ቀን ጀምሮ ተፈጻሚ ይሆናል ብሎ አንቀጽ ማስገባት፣ አዋጁ ተፈጻሚ በሚሆንባቸው ዜጎች ወይም ድርጅቶች ላይ ጉዳት ሊያመጣ ይችላል ሲሉ ይከራከራሉ፡፡

በተለይ የፀደቁት አዋጆች ጡረታ ሰብስበው በማያስገቡ ቀጣሪዎች ላይ ወለድና ቅጣት የሚጥሉ በመሆናቸው፣ አዋጁ ከሐምሌ 1 ቀን ጀምሮ መፅደቁን የማያውቁ ድርጅቶች ወይም ቀጣሪዎች ላይ የሕግ ተጠያቂነትን መጣል አግባብ አይሆንም ብለዋል፡፡ አቶ ተስፋዬ ዳባ በፓርላማው ስላነሱት ክርክር ተጨማሪ አስተያየት ይኖራቸው እንደሆነ ለማጣራት የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡

የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 57 ፕሬዚዳንቱ በአሥራ አምስት ቀናት ውስጥ ባይፈርም፣ ሕጉን በሥራ ላይ ከማዋል የሚያግድ እንደማይሆን ይደነግጋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የአማራ ክልል ወቅታዊ ሁኔታ

እሑድ ጠዋት መስከረም 13 ቀን 2016 ዓ.ም. የፋኖ ታጣቂዎች...

ብሔራዊ ባንክ ለተመረጡ አልሚዎች የውጭ አካውንት እንዲከፍቱ ለመጀመሪያ ጊዜ የፈቀደበት መመርያና ዝርዝሮቹ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የውጭ ምንዛሪ አጠቃቀምንና ተያያዥነት ያላቸው ጉዳዮችን...

እነ ሰበብ ደርዳሪዎች!

ከሜክሲኮ ወደ ዓለም ባንክ ልንጓዝ ነው። ሾፌርና ወያላ ጎማ...