‹‹ከአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጋር በምናደርገው ውይይት እንደ አገርም ሆነ እንደ አኅጉር ከግብረ ሰዶማውያን መብት በላይ በጣም የሚያሳስቡን ሌሎች ጉዳዮች አሉን››
የኬንያ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ የፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማን ጉብኝት አስመልክተው ካደረጉት ንግግር የተወሰደ፡፡ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ፕሬዚዳንት ኦባማ አገሪቱን ሲጎበኙ ‹በግብረ ሰዶማውያን መብት ጉዳይ ላይ ትነጋገራላችሁ ወይ?› ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት መልስ፣ ይህ ጉዳይ ፈጽሞ አጀንዳ አይሆንም ብለዋል፡፡ ‹‹ይህ ጉዳይ የኬንያ ሕዝብ አጀንዳ አይደለም፡፡ በመሆኑም ፈጽሞ የመነጋሪያ ርዕስ አይሆንም፡፡ ከግብረ ሰዶማውያን መብት በላይ ሌሎች አሳሳቢ ጉዳዮች አሉ፤›› ብለዋል፡፡ የኢኮኖሚና የፀጥታ ጉዳዮችን በዋናነት ጠቅሰዋል፡፡ ድህነት ቅነሳ፣ የተሻለ የጤናና የትምህርት አገልግሎት፣ የተሻሻሉ መንገዶች፣ አስተማማኝ ፀጥታና ደኅንነት ቅድሚያ የሚሰጣቸው ዋነኛ ጉዳዮች ናቸው ብለዋል፡፡ ፀረ ሽብር ዘመቻንም እንዲሁ፡፡ በምሥሉ ላይ የሚታዩት ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ መግለጫ ሲሰጡ ነው፡፡