ኢትዮጵያ የፓን አፍሪካ ከፍተኛ ትምህርት ጉባኤ 2015ን ሐምሌ 10 እና 11 ቀን 2007 ዓ.ም. በአፍሪካ ኅብረት አዳራሽ አስተናግዳለች፡፡ ‹‹የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ትብብር ጥራት ያለው ትምህርትን በአፍሪካ ዩኒቨርሲቲዎች ለማስረፅ›› በሚል መሪ ቃል በተዘጋጀው መድረክ አብዛኞቹ የአፍሪካ ዩኒቨርሲቲዎች ከተማሪዎች ቅበላ፣ ከትምህርት ጥራት፣ ከመምህራን ፍልሰት፣ ከአካዴሚክ ፍሪደም፣ ከላቦራቶሪ፣ ከትምህርት ግብዓትና ከተያያዥ ጉዳዮች ጋር ተያይዞ ክፍተት እንዳለባቸው ተነግሯል፡፡ ለክፍተቶቹ ደግሞ በፍጥነትና በብዛት እየተከፈቱ የሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ከቀደሙት በተለየ መልኩ ተጋላጭ ናቸው፡፡ ለዚህም ኢትዮጵያ እንደምሳሌ ልትነሳ ትችላለች፡፡
በኢትዮጵያ 90 የሚደርሱ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እንዲሁም ከ33 በላይ የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ይገኛሉ፡፡ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱ ወጣቱን ትውልድ በብዛት በመቀበል የከፍተኛ ትምህርት ተደራሽነትን እያስፋፉ ቢሆንም ከዚሁ ጎን ለጎን የጥራት ችግር ይነሳል፡፡ ይህንን በተመለከተም ትምህርት ሚኒስቴር ፊቴን ወደ ጥራት አዙሬያለሁ ካለ ሰነባብቷል፡፡
በመድረኩ ትምህርት ሚኒስትሩን አቶ ሽፈራው ሽጉጤን ጨምሮ የተለያዩ የሚመለከታቸው አካላት ተካፍለዋል፡፡ ከዩኒቨርሲቲዎች የተወከሉ ኃላፊዎችም የመድረኩ ተሳታፊ ነበሩ፡፡ ከአውሮፓና ከአፍሪካ የትምህርት ኤክስፐርቶችም ተሳትፈውበታል፡፡
በመድረኩ ላይ በተደረጉ የፓናል ውይይቶች በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የአካዴሚክ ነፃነት መጓደል፣ የመምህራን ፍልሰት፣ ልምድ የሌላቸው ታዳጊ ወጣት መምህራን መብዛት፣ በዩኒቨርሲቲ አስተዳደር ጉዳዮች ላይ የመንግሥት ጣልቃ ገብነት ለትምህርት ጥራት ጉድለት ምክንያት መሆናቸው ተነስቷል፡፡ በኢትዮጵያ ግማሽ ሚሊዮን የሚደርሱ ተማሪዎች በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በመማር ላይ ቢሆኑም፣ የ21ኛው ክፍለ ዘመን ዓለም አቀፍ ገበያ በሚፈልገው ደረጃ መጠን እየተማሩ ነው ወይ? ለሚለው ጥያቄ በእርግጠኝነት አዎ ለማለት በሚቻልበት ደረጃ ላይ አገሪቷ አልደረሰችም፡፡ በመሆኑም በመንግሥት በከፍተኛ ትምህርት ዘርፍ እያደረገ ካለው መስፋፋት ጎን ለጎን በጥራቱ ጉዳይ አብሮ ለመሥራትና ችግሮችን ለመቅረፍ መቀመጫውን በአሜሪካ ያደረገውና በኢትዮጵያውያን የሕክምና ባለሙያዎች የተሠረተው ፒፕል ቱ ፒፕል በትምህርት ጥራት ላይ የበኩሉን እያደረገ ነው፡፡ የድርጅቱ መሥራችና ፕሬዚዳንት ዶ/ር እናውጋው መሐሪ እንዳሉት፣ ድርጅቱ በጤናውና በትምህርቱ ዘርፍ መሥራት ከጀመረ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ በተለይ በጤናውና በጤናው ትምህርት ዘርፍ ጥራት ላይ ከዩኒቨርሲቲዎችና ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር እየሠራ ይገኛል፡፡
እንደ ዶ/ር እናውጋው፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የጤናውንም ጨምሮ 21ኛው ክፍለ ዘመን የሚፈልገውን የተማረ ኃይል ማፍራት አለባቸው፡፡ ለዚህም ደግሞ ዳያስፖራው የበኩሉን አስተዋጽኦ ሊያደርግ ይችላል፡፡ የፓን አፍሪካ የከፍተኛ ትምህርት ጉባኤ በኢትዮጵያ እንዲካሄድ መድረክ መመቻቸቱም፣ ከውይይቶች ክፍተቶችን ለመለየትና ጉድለቶችን ለመሙላት ዕድል ይፈጥራል፡፡ የጉባኤው ዋና ዓላማም አፍሪከ ውስጥ ዩኒቨርሲቲዎች እየተስፋፉ መሆኑና ከዚህ ጎን ለጎን ጥራት ለማስጠበቅ የሚቻልበት ላይ ለመምከር ነው፡፡
ዶ/ር እናውጋው እንዳሉት፣ ከክፍተቶቹ በመነሳት በመፍትሔዎች ላይ አብረው የሚሠሩ ይሆናል፡፡ በተለይ የጤናውን የትምህርት ዘርፍ ጥራት ለማስጠበቅ የጀመሩትን አጠናክረው ይቀጥላሉ፡፡
የፒፕል ቱ ፒፕል የቦርድ ሰብሳቢ ዶ/ር አንተነህ ሀብቴ በበኩላቸው፣ የሕክምና ትምህርት ቤቶች በየቦታው በሚከፈቱበት ጊዜ አንዳቸው ካንዳቸው የሚማሩበትን፣ ለትምህርቱ የሚያስፈልጉ መስፈርቶች የሚጠናከሩበትን፣ ትምህርት ከጨረሱ በኋላ በሙያም በትምህርትም ክትትል እያደረጉ የሚቆዩበትን ለማገዝ እየሠሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
መድረኩ የተዘጋጀበት አንዱ ምክንያትም አገር ውስጥ ያሉ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የአገር ውስጥ ዕውቀት ይዘው ዓለም አቀፋዊ ይዘት እንዲኖራቸው ማስቻል ነው፡፡