የንብ ኢንሹራንስ ኩባንያን በሥራ አስፈጻሚነት ሲመሩ የቆዩት አቶ ኃይለ ማርያም አሰፋን የሥራ መልቀቂያ ጥያቄ የተቀበለው የንብ ኢንሹራንስ ቦርድ፣ አዲስ ተጠባባቂ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሰየመ፡፡
ምንጮች እንደገለጹት አቶ ኃይለ ማርያም የሥራ መልቀቂያቸውን ያቀረቡት ከሁለት ሳምንታት በፊት ሲሆን፣ ቦርዱ ጥያቄውን ከተቀበለ በኋላ አቶ ኃይለ ማርያምን ተከትለው እንዲሠሩ በኢንሹራንስ ኩባንያው የኦፕሬሽን ምክትል ሥራ አስኪያጅ በመሆን ሲያገለግሉ የቆዩትን አቶ ሽፈራው በንቲን ተጠባባቂ ዋና ሥራ አስፈጻሚ በማድረግ ሰይሟል፡፡ ባለፉት 11 ዓመታት በኩባንያው ውስጥ ማገልገላቸው የሚነገርላቸው አቶ ሽፈራው፣ በኢንሹራንስ ኢንዱስትሪ ውስጥ ለ25 ዓመታት ያገለገሉ ባለሙያ ናቸው ተብሏል፡፡
የአቶ ሽፈራውን ሹመት እንዲፀድቅለትም ቦርዱ ለብሔራዊ ባንክ ማመልከቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በኢንሹራንስ ኩባንያ ውስጥ የረዥም ጊዜ ልምድ አላቸው የተባሉትና ከንብ ኢንሹራንስ ምሥረታ ጀምሮ የነበሩት አቶ ኃይለ ማርያም ከሥራ የለቀቁበት ምክንያት ምን እንደሆነ ለማወቅ ባይቻልም፣ ከጤና ጋር በተያያዘ በፈቃዳቸው የለቀቁ መሆኑ ይነገራል፡፡
ከጥቂት ወራት በፊት ናይል ኢንሹራንስን በዋና ሥራ አስፈጻሚነት ሲያገለግሉ የቆዩት አቶ ዳዊት ወልደ አማኑኤል፣ በተመሳሳይ ሁኔታ ኃላፊነታቸውን መልቀቃቸው ይታወሳል፡፡ ከናይል ኢንሹራንስ ከለቀቁ በኋላ በኅብረት ኢንሹራንስ ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ በመሆን መቀጠራቸው ታውቋል፡፡ ናይል ኢንሹራንስም በአቶ ዳዊት ምትክ አቶ አንዱዓለም ደምሰውን መመደቡ ይታወሳል፡፡ አቶ አንዱዓለም በናይል ኢንሹራንስ ውስጥ በሕግ አገልግሎት ኃላፊነት ሲያገለግሉ ነበር፡፡