የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ማስፈጸሚያ መመርያ ቁጥር አንድ ሰኞ የካቲት 26 ቀን 2010 ዓ.ም. በፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ አቶ ጌታቸው አምባዬ ይፋ ተደርጓል። ጠቅላይ ዓቃቤ ሕጉ መመርያው ለሁለት የተከፈለ መሆኑን፣ በመላው አገሪቱ ተግባራዊ እንደሚሆን አስታውቀዋል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ኮማንድ ፖስት በሚለያቸው ቦታዎች ተግባራዊ የሚደረጉ ክልከላዎችን የያዘ ሲሆን፣ በማስፈጸሚያ መመርያ ላይ ግልጽ የሆነ መረጃ እንዲኖራቸው፣ ባለማወቅም አዋጁን እንዳይተላለፉ መመርያውን በተመለከተ ግንዛቤ የመፍጠር ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማስፈጸሚያ መመርያ ቁጥር አንድ የሚከተለው ነው፡፡
- በመላው አገሪቱ የሚተገበሩ ክልከላዎች
1.1 ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን የሚጥስ ተግባር መፈጸም
በመመርያው መሠረት ማንኛውም ሰው በኃይል፣ በዛቻና በየትኛውም መልኩ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን የሚጥስ ተግባር መፈጸም የለበትም፡፡ የጦር መሣሪያ ይዞ ማመፅና የእርስ በርስ ግጭት እንዲኖር መፍጠርም ክልክል ነው።
1.2 የሕዝቡን አንድነትና መቻቻል የሚጎዳ ተግባር መፈጸም፣
1.3 ከአሸባሪ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ማድረግና መደገፍ፣
1.4 የትራንስፖርት እንስቃሴን ማወክ፣
1.5 የሕዝብ አገልግሎት ማስተጓጎል፣ ማቋረጥና መዝጋት፣
1.6 የመሠረት ልማት ተቋማት ላይ ጥቃት ማድረስ፣
1.7 የሕግ አስከባሪዎችን ሥራ ማወክ፣
1.8 ያልተፈቀደ ሠልፍና የአደባባይ ስብሰባ ማድረግ፣
1.9 በትምህርት ተቋማት አድማ ማድረግ፣
1.10 በስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎች አድማ ማድረግ፣
1.11 ሁከትና ብጥብጥ የሚያነሳሳ ቅስቀሳና ግንኙነት መፍጠር፣
1.12 የመሠረታዊ ሸቀጦችን ዝውውር ማወክ፣
1.13. ባህላዊ፣ ሕዝባዊ፣ ሃይማኖታዊና ብሔራዊ በዓላትን ማወክ፣
1.14. በገበያ፣ ሃይማኖታዊ ተቋማት፣ በዓላትና ሕዝብ በተሰበሰበበት ሥፍራ የጦር መሣሪያ ይዞ መግባት፣
1.15. የሕዝብን ሰላምና ፀጥታ ለማደፍረስ የገንዘብ፣ የቁሳቁስና ሌሎች ድጋፎችን ማድረግ፣
1.16. ከኮማንድ ፖስቱ ውጭ በፀጥታ ጉዳይ ላይ መግለጫ መስጠት፣ አዋጁንና አዋጁን ተከትለው የወጡ ደንቦችና መመርያዎችን አስመልክተው የሚከለክሉ ድንጋጌዎች ተቀምጠዋል፡፡
እነዚህን ክልከላዎች በመላ አገሪቱ የሚተገበሩ ክልከላዎች ናቸው።
- በተወሰኑ የአገሪቱ ክፍሎች የሚተገበሩ ክልከላዎች
2.1 የጦር መሣሪያ ይዞ መንቀሳቀስ
የአስቸኳይ ጊዜ ኮማንድ ፖስት ይፋ በሚያደርጋቸው ሥፍራዎች የትኛውንም የጦር መሣሪያ ይዞ መንቀሳቀስ አይፈቀድም፡፡
2.2 የሰዓት ዕላፊ ገደብ
የአስቸኳይ ጊዜ ኮማንድ ፖስት ይፋ በሚያደርጋቸው ሥፍራዎች የሰዓት ዕላፊ ገደብ ያስቀምጣል፡፡
በትላልቅ ፋብሪካዎች፣ በኢንዱስትሪ ማዕከላት በሰፋፊ እርሻዎች የሰዓት ዕላፊ የሚጣልባቸው ሥፍራዎች ናቸው።
2.3 የዜጎችን ደኅንነት በተመለከተ
የዜጎችን ደኅንነት ለመጠበቅ ሲባል ዜጎችን በአንድ በተወሰነ ሥፍራ ማቆየት፣ ከአንድ ሥፍራ ወደ ሌላ ማዘዋወር፡፡
2.4 ለአካባቢ ሥጋት ሲባል ወደ ተዘጋ መንገድ መግባትን መከልከል።
- የመተግበርና የማሳወቅ ግዴታ
3.1 የቤትና የተሽከርካሪ አከራዮች
የተከራይን አካል ማንነት መዝግቦ በግልጽ መያዝ፣ በጽሑፍ የሠፈረውን መረጃ በ24 ሰዓት ውስጥ ለፖሊስ ማሳወቅ፣ ተከራዩ የውጭ አገር ዜጋ ከሆነ የተከራዩን ፓስፖርትና የኪራይ ውል ለፖሊስ የማቅረብ ግዴታ አለባቸው።
3.2 መረጃ የመስጠት ግዴታ
ማንኛውም ተቋም በተጠየቀበት ጊዜ ለሕግ አስከባሪ አካል መረጃ የመስጠት ግዴታ አለበት።
3.3 ማንኛውም ሰው የኮማንድ ፖስቱን ውሳኔ የማክበርና የመተግበር ግዴታ አለበት።
- ዕርምጃዎች
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተላልፎ መገኘት ዕርምጃዎችን ያስወስዳል። የሚወሰዱ ዕምጃዎችም፣
- ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ በቁጥጥር ሥር ማዋል፣
- በቁጥጥር ሥር የሚውሉ ሰዎችን ኮማንድ ፖስቱ በወሰነው ቦታ እንዲቆዩ ይደረጋል፣
- ማንኛውም ሥፍራና አካል ላይ በማንኛውም ሰዓት ብርበራ ማድረግ፣
- የተዘረፉ ንብረቶችን አጣርቶ ለባለቤቶቹ መመለስ፣
- በትምህርት ተቋማት ረብሻ የሚፈጥሩ አካላት ላይ ሕጋዊ ዕርምጃ መውሰድ፣ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ አስተዳደራዊ ዕርምጃ እንዲወሰድ ማዘዝ።
- የኃይል አጠቃቀም
የሕግ አስከባሪ አካላትና የጥበቃ ኃይሎች የራሳቸውን ደኅንነት መጠበቅ ይችላሉ።
የዜጎችን ደኅንነትና የኢንቨስትመንት ተቋማትን የመጠበቅ ግዴታ አለባቸው። ይህንን ግዴታቸውን ለመወጣት ተመጣጣኝ ኃይል መጠቀም እንደሚችሉም በመመርያው ተደንግጓል።