በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኙ የግል የትምህርት ተቋማት በመማር ማስተማር ሒደት የሚያስከፍሉትን ክፍያና የትምህርት ጥራታቸውን የሚቆጣጠር መመርያ ፀደቀ፡፡ መመርያው በአጠቃላይ የግል የትምህርት ተቋማት የሚተዳደሩበት ነው ተብሏል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ዴላሞ ኦቶሬ ነሐሴ 4 ቀን 2007 ዓ.ም. በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ኢኮኖሚያዊ ምክንያት ሳይኖሯቸው ዋጋ የሚጨምሩ የትምህርት ተቋማትን እንዲሁም የትምህርት ጥራትን መቆጣጠር የሚያስችል መመርያ መፅደቁን አስታውቀዋል፡፡
አቶ ዴላሞ እንደገለጹት፣ በ2007 ዓ.ም. ኢኮኖሚያዊ ምክንያት ሳይኖራቸው ዋጋ የጨመሩ 194 ትምህርት ቤቶች ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል፡፡ 60 ትምህርት ቤቶች ደግሞ ክስ ተመሥርቶባቸዋል ብለዋል፡፡
ይህ ዕርምጃ የተወሰደው ከንግድ አሠራርና ከሸማቾች ጥበቃ ባለሥልጣን ጋር በጋራ መሆኑን አቶ ዴላሞ አስረድተዋል፡፡
ነገር ግን የግል ትምህርት ቤቶች ለምን ዋጋ ጨመራችሁ ተብለው እንዳልተጠየቁ፣ ይልቁንም ትምህርት ቤቶቹ ዋጋ የጨመሩት በኢኮኖሚያዊ ምክንያት ነው ወይስ ሆን ብለው ነው የሚለው መሠረታው ጉዳይ ከተጣራ በኋላ፣ ያለ በቂ ምክንያት ዋጋ የጨመረ ተቋም ዕርምጃ እንደሚወስድበት አስታውቀዋል፡፡
ይህንን መመርያ የሚያስፈጽም ራሱን የቻለ ኤጀንሲ እንዲቋቋም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ በቅርቡ ውሳኔ እንደሚያሳልፍ አቶ ዴላሞ ተናግረዋል፡፡
አቶ ዴላሞ እንደሚሉት ኅብረተሰቡ በመንግሥት ትምህርት ቤቶች ላይ ያለው አመለካከት ሊቀየር ይገባል፡፡ ምክንያቱም ተማሪዎች መለካት ያለባቸው በሚያመጡት ውጤት ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት በመንግሥት ትምህርት ቤቶች የሚማሩ ተማሪዎች ከፍተኛ ውጤት በማምጣት ላይ የሚገኙ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ በአዲስ አበባ የሚገኙ ሁሉም መለስተኛና ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ መረብ የተገናኙ መሆናቸውን አስረድተው፣ ትምህርት ቢሮውም በዚህ ቴክኖሎጂ በመጠቀም የመማር ማስተማርን ሒደት በቀጥታ ይከታተላል ብለዋል፡፡
ትምህርት ቢሮው ከነሐሴ 8 እስከ 9 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ በአዲስ አበባ ስብሰባ ማዕከል ከ1,500 ወላጆችና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች ጋር የትምህርት ጉባዔ እንደሚያካሂድ ገልጿል፡፡
በጉባዔው የግል ትምህርት ቤቶች አሠራርና አስተዳደራዊ ጉዳዮች፣ የሥርዓተ ትምህርት አተገባበርና መልካም አስተዳደር የመነጋገሪያ አጀንዳዎች ይሆናሉ ተብሏል፡፡