‹‹ከዚያ ጦርነት አንዳች ግንኙነት የሌላቸውን ልጆቻችንን፣ የልጅ ልጆቻችንንም ሆነ ወደፊት የሚመጣውን ትውልድ ስላለፈው ጊዜ ይቅርታ እንዲጠይቁ ማድረግ አይገባንም፡፡››
የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ሺንዞ አቤ፣ ሁለተኛው የዓለም ጦርነት ያከተመበት 70ኛ ዓመት አስመልክቶ ነሐሴ 8 ቀን 2007 ዓ.ም. የተናገሩት፡፡ ከ1932 ዓ.ም. እስከ 1937 ዓ.ም. ድረስ በተደረገው ጦርነት የአክሲስ ኃያላት በመባል የሚታወቁት ጀርመን፣ ጃፓንና ጣሊያን በአሜሪካና በቀድሞው ሶቭየት ኅብረት መራሹ ኃይል ድል በተደረጉበት ጦርነት 60 ሚሊዮን ያህል ሕዝብ ማለቁ ተመዝግቧል፡፡ በአውሮፓ፣ በፓስፊክ፣ በአትላንቲክ፣ በደቡብ ምሥራቅ እስያ፣ በቻይና በመካከለኛው ምሥራቅ፣ በሜድትራኒያንና በአፍሪካ በተደረገው ጦርነት ተጠያቂ ከተደረጉት አገሮች አንዷ ጃፓን ነበረች፡፡ አሜሪካ ፕርል ሃርበር በተሰኘው የጦር ሰፈሯ በጃፓን ለተሰነዘረበት ድብደባ የበቀል ምላሽ የሰጠችባቸው የሂሮሺማና ናጋሳኪ ኒውክሌር ጥቃትም ይታወሳል፡፡ ጃፓን በጦርነቱ አጋማሽ ዓመት ላይ ለፈጸመችው ጥቃት አሜሪካ በጦርነቱ ፍጻሜ ብቀላዋን ተወጥታለች፡፡ ጃፓን በቻይናና ደቡብ ምሥራቅ እስያ ውስጥ ለፈጸመችው ድርጊት ጠቅላይ ሚኒስትር አቤ ጦርነቱ ያከተመበትን 70ኛ ዓመት ምክንያት አድርገው፣ በወቅቱ አገራቸው ለፈጸመችው ጥፋት መፀፀቷን የሚገልፅ መግለጫ ለማውጣት ማሰባቸው በየሚዲያው መነገሩ ይታወሳል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የዓርብ ዕለት ንግግር ይፋ የሆነው ለወራት ያህል መንግሥት ባቋቋመው የምሁራን፣ የባለሥልጣኖችና የፖለቲካ አማካሪዎች የተካተቱበት ኮሚቴ ንግግሩን ቃል በቃል ሐረግ በሐረግ ከመረመረውና ካቢኔው ካፀደቀው በኋላ ነበር፡፡ በምስሉ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ሺንዞ አቤ ይታያሉ፡፡