‹‹ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር ለፊርማ የተዘጋጀው የሰላም ስምምነት ሰነድ ለውጥ ካልተደረገበት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንደሚፈርሙ አረጋግጥላችኋለሁ፡፡››
የደቡብ ሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ባርናባ ማሪያ ቤንጃሚን ከሮይተርስ ጋር በስልክ ካደረጉት ቃለ ምልልስ የተወሰደ፡፡ ረቡዕ ነሐሴ 20 ቀን 2007 ዓ.ም. በደቡብ ሱዳን ዋና ከተማ ጁባ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ፣ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታና ዮዌሪ ሙሲቬኒ ሊገኙበት ይችላሉ በተባለ ሥነ ሥርዓት ላይ ፕሬዚዳንቱ በሰላም ስምምነቱ ሰነድ ላይ ፊርማቸውን እንደሚያኖሩ ሮይተርስ ዘግቧል፡፡ ባለፈው ሳምንት በአዲስ አበባ በተካሄደው ድርድር ተቀናቃኛቸው ዶ/ር ሪክ ማቻር ፊርማቸውን ቢያኖሩም፣ ፕሬዚዳንት ኪር ግን በአለቀ ሰዓት የምክር ጊዜ ያስፈለገኛል ብለው ሳይፈርሙ መቅረታቸው ይታወሳል፡፡ አሜሪካ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጦር ማሣሪያ ማዕቀብና ተጨማሪ ሌሎች ማዕቀብ እንዲጥል ጠንካራ ሐሳብ ማቅረቧ፣ ፕሬዚዳንቱን ወደ ስምምነቱ እንደመለሳቸው እየተነገረ ነው፡፡ ተቀናቃኛቸው ዶ/ር ማቻር ደግሞ ሥልጣን መጋራት በተለይ ነዳጅ በሚወጣባቸው ግዛቶች እንዲኖር እየወተወቱ ነው፡፡ በደቡብ ሱዳን የእርስ በርስ ጦርነት ከአሥር ሺሕ በላይ ሰዎች ሲሞቱ፣ ከሁለት ሚሊዮን በላይ የሚሆኑት ደግሞ መሰደዳቸው ይነገራል፡፡ በምሥሉ ላይ ፕሬዚዳንት ኪር ይታያሉ፡፡