የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ ሸዋ ዞን ኖኖ ወረዳ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ የአማራ ክልል ተወላጆች፣ ላለፉት 30 እና ከዚያ በላይ ዓመታት ከኖሩበትና ሀብት ንብረት ካፈሩባት ሥፍራ በኃይል እንዲለቁ መደረጉ እንዳሳሰበው አስታወቀ፡፡ መንግሥት በጉዳዩ ላይ የተሳተፉ አካላትን ለፍትሕ እንዲያቀርብ፣ አስፈላጊውን ዕርዳታና ድጋፍ እንዲያደርግ ጠየቀ፡፡
መኢአድ ይህን ያስታወቀው ሐሙስ ነሐሴ 21 ቀን 2007 ዓ.ም. ቴዎድሮስ አደባባይ በሚገኘው ጽሕፈት ቤቱ ‹‹በሰላም አብረው በሚኖሩ ዜጎች መካከል ቅራኔ እንዲፈጠር በካድሬዎችና በመንግሥት አካላት የሚደረገው ሴራ በአስቸኳይ ይቁም›› በሚል ርዕስ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት ነው፡፡ መግለጫውን የሰጡት ደግሞ ፕሬዚዳንቱ አቶ አበባው መሐሪና ዋና ጸሐፊ አቶ ካሳሁን አበባው ናቸው፡፡
‹‹በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 32(1) መሠረት ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በአገሪቱ ውስጥ በመረጠውና በፈቀደው አካባቢ የመዘዋወር፣ የመኖርና ሠርቶ የማደር መብት እንዳለው ቢደነግግም፣ የገዢው ፓርቲ ባለሥልጣናት ዜጎችን በብሔርና በቋንቋ በመከፋፈል እያሳደዷቸውና አካላቸው እንዲጎድል እያደረጓቸው ነው፤›› በማለት መኢአድ ተቃውሞውን አሰምቷል፡፡
ይሁን እንጂ መጤዎች በሚል ሰበብ በተለያዩ ጊዜያት የንብረት መዘረፍና መሰደድ እንደሚደርስ ገልጾ፣ ይኼ አሁን በኦሮሚያ ክልል ተፈጸመ የተባለውም ከዚህ ቀደም ይደርሱ ከነበሩት እንግልቶች ጋር ተመሳሳይ፣ ነገር ግን ከሕገ መንግሥቱ ድንጋጌዎች ጋር የሚጋጭ መሆኑንም አመልክቷል፡፡
በዚህ ምክንያት መኢአድ በኦሮሚያ ክልል በኖኖ ወረዳ የተለያዩ ቀበሌዎች ተፈጸመ ባለው ችግርም 305 ግለሰቦች ከቤት ንብረታቸው መፈናቀላቸውን አቶ አበባው ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም በድርጊቱ አንድ ግለሰብ ሕይወቱ ማለፉን፣ አሥር ግለሰቦች ደግሞ ከፍተኛ ጉዳት እንደረሰባቸውና 99 የሳርና 25 የቆርቆሮ ቤቶች ከነሙሉ ንብረታቸው በእሳት ተቃጥለው መውዳማቸውን አብራርተዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም በመኢአድ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ተወስኖ ተጠቂዎቹ ያሉበትን ሁኔታ ለማጣራት ወደ ሥፍራው የተላኩት አቶ ሙሉጌታ አበበ ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ለአምስት ተከታታይ ቀናት ያህል ታስረው መቆየታቸውን አቶ አበባው የገለጹ ሲሆን፣ ክስተቱም ሕገ መንግሥቱን የጣሰ ስለሆነ መንግሥት ሁኔታውን አጣርቶ በደሉን የፈጸሙት ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ጥያቄያቸውን ለመንግሥት አቅርበዋል፡፡
‹‹የኢትዮጵያ መንግሥት ገለልተኛ አካላትን በመመደብ ሁኔታው ተጣርቶ በደሉን የፈጸሙት ግለሰቦች ለፍርድ እንዲቀርቡ እንዲያደርግ፣ ለተጎጂዎችም ተገቢው የሆነ ዕርዳታና ድጋፍ እንዲደረግ እንጠይቃለን፤›› በማለት መኢአድ በመግለጫው ጠይቋል፡፡