- Advertisement -

አውሮፓውያንን ለሁለት የከፈለው የስደተኞች ማዕበል

በየቀኑ በሺዎች የሚቆጠሩ ስደተኞች የአውሮፓ ድንበርን ለማቋረጥ ደጅ ይጠናሉ፡፡ ሆኖም ወደ አውሮፓ አገሮች መዝለቁ ፈተና ነው፡፡ አንዳንዶቹ አገሮች በስደተኛ ካምፕ ሲያስቀምጡና ጥገኝነትን ሲፈቅዱ፣ አንዳንዶቹ ደግሞ በራቸውን ዝግ የሚያደርጉ ጠንካራ የስደተኛ ፖሊሲ አውጥተዋል፡፡ ይህም የአውሮፓ አባል አገሮች መሪዎችን ለውዝግብ ዳርጓል፡፡

በአንድ የጋራ ፖሊሲ የሚተዳደሩት የአውሮፓ ኅብረት አባል አገሮች፣ በየቀኑ የሚጐርፉትን ስደተኞች ጉዳይ ለመዳኘት ወጥ አቅጣጫ ማስቀመጥ ተስኗቸዋል፡፡ ጀርመን ሁሉም አባል አገሮች ስደተኞች በተወሰኑ የአውሮፓ አገሮች ላይ የፈጠሩትን ጫና እንዲካፈሉ ሐሳብ ብታቀርብም፣ በሁሉም አገሮች ተቀባይነት አላገኘችም፡፡ ፈረንሳይና እንግሊዝ ከጀርመን ጐን በመቆም ስደተኞች የሚስተናገዱበትን አኳኃን በተመለከተ አዲስ የጋራ ፖሊሲ እንዲወጣ ግፊት ቢያደርጉምና በተደጋጋሚ ስብሰባ ቢቀመጡም፣ ከሌሎቹ አገሮች በጐ ምላሽ አላገኙም፡፡ በመሆኑም መስከረም 3 ቀን 2008 ዓ.ም. የአውሮፓ ኅብረት አባል አገሮች አስቸኳይ ስብሰባ በብራሰልስ ለማድረግ ወስነዋል፡፡ ስብሰባው ስደተኞች በተወሰኑ አገሮች ላይ የሚፈጥሩትን ጫና ለማቃለል የሚያስችልና ሁሉም አገሮች ችግሩን የሚካፈሉበትን የጋራ ስትራቴጂ ለመንደፍ ያለመ ቢሆንም፣ ሐሳቡ ከወዲሁ እክል እየገጠመው ነው፡፡

ጣሊያን፣ ግሪክና ጀርመን ስደተኞች በተለይ የሚጐርፉባቸው የአውሮፓ አገሮች ናቸው፡፡ ትንሽ በምትባለው የግሪክ ሌስቦስ ደሴት ብቻ 13 ሺሕ ስደተኞች ይገኛሉ፡፡ ከሊቢያ ሜዴትራኒያን ባህርን በማቋረጥ የጣሊያን ወደብን ያጨናነቁና ባህር የበላቸውም በሺዎች የሚቆጠሩ ናቸው፡፡ ከአውሮፓ አገሮች ትልቁን የስደተኞች ቁጥር የምታስተናግደው ጀርመን፣ በተያዘው ዓመት ብቻ ከ800 ሺሕ በላይ የፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂዎችን ልታስተናግድ እንደምትችል አሳውቃለች፡፡ ይህ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር በአራት እጥፍ ጨምሯል፡፡ በጀርመን እ.ኤ.አ. በ2015 የፖለቲካ ጥገኝነት የጠየቁ ስደተኞች ቁጥር በአውሮፓ አባል አገሮች ጥገኝነት ከጠየቁት 43 በመቶውን ይይዛል፡፡

የጀርመኗ መራሂተ መንግሥት አንገላ መርከል፣ በአገራቸውም ሆነ በሌሎች አገሮች ላይ ስደተኞች እያደረሱ የሚገኙትን ጫና ሁሉም እንዲጋሩ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ‹‹አውሮፓውያን እርስ በርሳቸው እንደሚረዳዱ ሁሉ ይህንን ለሌሎችም ማድረግ አለባቸው፡፡ ድጋፋችንን አሁን ማሳየት አለብን፣ በፍጥነት!›› ሲሉም ተናግረዋል፡፡  

አውሮፓውያን ግን መርከል እንዳሉት ተባባሪ ሆነው አልተገኙም፡፡ አልጄዚራ እንደዘገበው፣ የተወሰኑ የአባል አገሮቹ ተወላጆች ‹‹ጫናው እኛ በምንከፍለው ታክስ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ያመጣል፤›› ሲሉ፣ ሃንጋሪ ደግሞ ማንኛውም ስደተኛ ወደ አገሯ እንዳይገባ፣ የፖለቲካ ጥገኝነት የሚጠይቁም በጠንካራ መሥፈርቶች እንዲያልፉ አድርጋለች፡፡ ከዚህ ባለፈም ስደተኞች ድንበሯን እንዳያቋርጡ አጥር ለመገንባት በዝግጅት ላይ ነች፡፡ አጥሩ የሚገነባውም ከሰርቢያ በሚያዋስናት ድንበር ሲሆን፣ ይህም ከሰርቢያም ሆነ ሰርቢያን አቋርጠው ወደ ሃንጋሪ የሚገቡ ስደተኞችን ለማገድ ያስችላታል፡፡

የሃንጋሪ መንግሥት ቃል አቀባይ ዞልታን ኮቫስ ‹‹ሕገወጥ ስደተኞችን ለመግታት ደንብና ሥርዓት ማበጀት አለብን፤›› ብለዋል፡፡

- Advertisement -

ፈረንሳይ ግን በሃንጋሪ ዕርምጃ ላይ ተቃውሞዋን ሰንዝራለች፡፡ የፈረንሳይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሎረንት ፋቢዮ፣ ‹‹ጨካኞች ናቸው፡፡ ሃንጋሪ የአውሮፓ አካል ናት፡፡ የራሳችን የሆነ እሴት አለን፡፡ ስደተኞች ላይ አጥር በማጠር ግን እሴቶቻችንን ልናከብር አንችልም፤›› ሲሉ ለኢሮፕ 1 ሬዲዮ ጣቢያ ተናግረዋል፡፡

አውሮፓ በስደተኞች መጥለቅለቋ ምሥራቅና ምዕራብ አውሮፓን በሐሳብ ልዩነት ከፍሏል፡፡ በተለይ ስደተኞችን በኮታ መከፋፈል የሚለው አጀንዳ ላይ ለመስማማት አልቻሉም፡፡ ጀርመንን ጨምሮ አንዳንድ የኅብረቱ አባል አገሮች የኮታ ሥርዓት ለመዘርጋት ሐሳብ ቢያቀርቡም፣ ተቀባይነት አላገኙም፡፡ እንደ ሃንጋሪ ሁሉ ስሎቫኪያም ሐሳቡን ውድቅ አድርጋለች፡፡ የስሎቫኪያ ጠቅላይ ሚኒስትር ሮበርት ፊኮ፣ አገራቸው መቼውንም ቢሆን ኮታ በሚለው ሐሳብ እንማትስማማና ስደተኞችንም እንደማትቀበል አሳውቀዋል፡፡ ‹‹አንድ ቀን ከዓረቡ ዓለም የተሰደዱ 100 ሺሕ ሰዎች በስሎቫኪያ ቢገኙ ለአገራችን ችግር ነው፡፡ ይህን ችግር ስሎቫኪያ እንድትሸከም አልፈልግም፤›› ብለዋል፡፡ ንግግራቸውም በፖላንድ፣ በቼክ ሪፐብሊክና በሃንጋሪ ድጋፍ አግኝቷል፡፡

አውሮፓ በተያዘው የአውሮፓውያን ዓመት ከዚህ ቀደም ከነበረው በተለየ ሁኔታ በስደተኞተ ተጨናንቃለች፡፡ ከዚሁ ጐን ለጐን የጋራ የፖለቲካ ጥገኝነት ጥያቄ ማስተናገጃ ስትራቴጂ አለመኖር ችግሩን በተወሰኑት አገሮች ላይ አባብሶታል፡፡ በመሆኑም ስደተኞቹ ጠንካራ ኢኮኖሚ ወዳላቸውና የፖለቲካ ጥገኝነት ጥያቄያቸው በቀላሉ ተቀባይነት ወደሚያገኝበት ምዕራብና ሰሜን አውሮፓ እንዲጓዙ አስገድዷል፡፡ ይህ ደግሞ በተወሰኑት አገሮች ላይ ጫና ፈጥሯል፡፡

በአገሮቹ ላይ ጫናውን ከመፍጠር ባለፈም፣ ስደተኞች በባህርና በየብስ እንዲሁም በማጓጓዣ መኪኖች ላይ ሕይወታቸው እያለፈ ነው፡፡ ባለፈው ሳምንት ብቻ ከ100 በላይ የስደተኞች አስከሬን ከባህር ማውጣታቸውን የሊቢያ ባለሥልጣናት አሳውቀዋል፡፡ ሟቾቹም አውሮፓ ለመግባት የሚጠባበቁ ነበሩ፡፡ ሊቢያ ይህንን ከማሳወቋ በፊትም በኦስትሪያ በተሳቢ ተሽከርካሪ ውስጥ የተጫኑ 71 ስደተኞች ሞተው ተገኝተዋል፡፡

የኦስትሪያ የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ጆሃና ማይክሊትነር፣ ‹‹በኦስትሪያ ሞተው የተገኙ 71 ስደተኞች ጉዳይ ለአውሮፓ አገሮች ማንቂያ ደወል ነው፡፡ አውሮፓውያን የስደተኞችን ችግር ለመቅረፍ እጅ ለእጅ መያያዝ አለባቸው፤›› ብለዋል፡፡

በተያዘው ዓመት በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ስደተኞች ለችግር ተጋልጠዋል፡፡ በአውሮፓ የተሻለ ኑሮ ፍለጋ ተሰደዋል ተብለው ከሚገመቱት ውስጥም 2,500 ያህሉ ባህር ውስጥ ሰጥመው ሞተዋል፡፡

አብዛኞቹ ስደተኞች በየአገራቸው ከሚገኝ ጦርነት፣ ብጥብጥና እስር በመሸሽ ወደ አውሮፓ የሚሰደዱ ናቸው፡፡ ሶሪያና አፍጋኒስታንን ጨምሮ ከ300 ሺሕ በላይ ስደተኞችም ጉዞዋቸውን ወደ አውሮፓ አድርገዋል፡፡ የሜዲትራኒያንን ባህር ካቋረጡት ውስጥ 2,636 ሞት መመዝገቡንና ብዙዎችም ጠፍተው መቅረታቸውን የስደተኞች ዓለም አቀፍ ቢሮ አሳውቋል፡፡

ከምሥራቅ አፍሪካ እንዲሁም ብጥብጥ ከነገሠባቸው የዓረብ አገሮች ወደ አውሮፓ የሚጐርፉ ስደተኞች ቁጥር ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ ነው፡፡ ጣሊያንና ግሪክ አብዛኛው የስደተኛ መዳረሻ አገሮች ቢሆኑም፣ የስደተኞች ጉዳይ በአጠቃላይ ለአውሮፓ ራስ ምታት ሆኗል፡፡ የአባል አገሮቹ መሪዎችም በስደተኞች አቀባበል ዙሪያ ከስምምነት መድረስ አልቻሉም፡፡ በመሆኑም መስከረም 3 ቀን 2008 ዓ.ም. በብራሰልስ ለመምከር ቀጠሮ ይዘዋል፡፡ የስደተኞች ማዕበል በአውሮፓ የፈጠረውን ቀውስ በኮታ ሲስተም ለመፍታት የአውሮፓ አባል አገሮች መሪዎች ከስምምነት ይደርሱ ይሆን? በአውሮፓ በሻንገን ቪዛ መጠቀምን ማገድ ወደተወሰኑ አገሮች የሚደረግን እንቅስቃሴስ ይገታው ይሆን? የብዙዎች ጥያቄ ነው፡፡

- Advertisement -

በማህበራዊ ሚዲያዎች ይከታተሉን

ከ ተመሳሳይ አምዶች

ትራምፕና የመጀመሪያዎቹ 100 ቀናት

ተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ጄ ትራምፕ በኅዳር ወር (November) የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች ጎራዎችን አደረጃጀቶችንና አሠላለፎችን እንዲሁም መላውን መራጩን ሕዝብ አሳምነው ማሸነፋቸውን የአገሪቱ የሕዝብ ተወካዮችና...

ከዓመት ዓመት የዘለቁ ግጭቶች

ያለፈው የጎርጎርዮሳውያን ዓመት (እ.ኤ.አ. 2024) በታሪክ በሰው ሠራሽም፣ በተፈጥሮም የሰው ልጅን መከራዎች ያባባሱ፣ በርካታ ክስተቶች ከተስተዋሉባቸው ወቅቶች ሁሉ የከፋ ተብለው ከተመዘገቡት ውስጥ ተካቷል፡፡ በበርካታ...

እስራኤል የመጨረሻ ያለችው ረዥሙ የኢራን እጅ

ባለፈው ሳምንት ሐሙስ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የዓለም የጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ቴድሮስ አድሃኖም በየመን ዋና ከተማ ሰንዓ አውሮፕላን ማረፊያ ከተሰነዘረ የእስራኤል ጥቃት ‹‹ለጥቂት››...

የእስራኤልና የየመን ሁቲ ታጣቂዎች ግጭት

መቀመጫቸውን የመን ያደረጉ የሁቲ ተዋጊዎች ከእስራኤል ጋር ግንኙነት አላቸው የሚባሉና በቀይ ባህርና በኤደን ባህረ ሰላጤ የሚንቀሳቀሱ መርከቦችን ዒላማ ማድረግ የጀመሩት ከዓመት በፊት ነው፡፡ ሃማስ...

የሶሪያ ሽግግርና የውጭ እጆች

የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን ቅዳሜ በሰጡት መግለጫ፣ አገራቸው ከሶሪያ ልዩ ልዩ ኃይሎች ቀጥተኛ ግንኙነት ማድረጓን ተናግረዋል፡፡ እ.ኤ.አ. ዲሴምበር 7 በሃያት ታህሪር አል...

የበሽር አል አሳድ መገርሰስና የሶሪያውያን ሥጋቶች

የሶሪያው ፈላጭ ቆራጭ በሽር አል አሳድ ከ24 ዓመታት አገዛዝ በኋላ በተቀናቃኝ ታጣቂዎች አሥራ አንድ ቀናት በፈጀ ምት ተሸንፈው እሑድ ኅዳር 29 ቀን 2017 ዓ.ም....

አዳዲስ ጽሁፎች

መንግሥት ገቢ ከመሰብሰብ ባሻገር ለሕዝብ ኑሮ ትኩረት ይስጥ!

የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ማደግ ያለበት በተገኘው ቀዳዳ ሁሉ ከሚሰበሰብ ታክስ ብቻ ሳይሆን ከግብርና፣ ከኢንዱስትሪ፣ ከማዕድን፣ ከአገልግሎትና ከሌሎች ሀብት አመንጪ ዘርፎች ጭምር ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ቁጥራቸው...

የኢትዮጵያን ትንሳዔ ለማብሰርና ለመከወን ምን እናድርግ?

በጌታነህ አማረ ኢትዮጵያ ማለት ታላቅ አገር ቀደምት የሰው ዘር መገኛና የሥልጣኔ ባለቤት የሆነች አገር እንደነበረች ታሪክ ሲያወሳን ይኖራል። በዚያውም ልክ ይህች ታላቅ ነበረች የምትባል አገር...

የምድራችን (የሰው ልጆች) ተማፅኖ — አረንጓዴ ፖለቲካ!

(ወጥመዶችና ማምለጫችን) በታደሰ ሻንቆ የወጥመዶች ዓለም በአፍሪካ ቀንድ አገሮች ዘንድ ያሉ ውዝግቦችና ግጭቶች ምንም ተቀባቡ ምን፣ መሬትን ውኃን አፈርን ማዕድናትን ንግድንና መሰል ጥቅሞችን የተመለከቱ ናቸው፡፡ በእነዚህ...

‹‹መንግሥት ከሁሉም ነገር በላይ ቅድሚያ ሰጥቶ የኢኮኖሚ ጫናውን ለመቀነስ የነዳጅ ድጎማውን መቀጠል ይኖርበታል›› ሰርካለም ገብረ ክርስቶስ (ዶ/ር)፣  የነዳጅ ዘርፍ ከፍተኛ ባለሙያ

የነዳጅ ግብይት ሥርዓትን ለመዘርጋትና ለመቆጣጠር ያስችላል የተባለ አዲስ አዋጅ ባለፈው ሳምንት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ፀድቋል፡፡ በኢትዮጵያ በነዳጅ ሥርጭት ግብይትና በአጠቃላይ በዘርፉ ያሉትን ማነቆዎች...

ስለካፒታል ገበያ ምንነትና ፋይዳ ያልተቋረጠና የተብራራ መረጃ ማድረስ ያሻል!

የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ በይፋ ሥራ ጀምሯል፡፡ አገራዊ ኢኮኖሚውን ከመደገፍና ለተለያዩ ኢንቨስትመንቶች የሚውል ካፒታል ለማሰባሰብ እንደ አንድ አማራጭ የሚወሰድና ለኢትዮጵያ እንደ አዲስ ምዕራፍ የሚታይ ዕርምጃ...

ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ በጀት የተያዘለት የሥነ ተዋልዶ ጤና ፕሮጀክት ይፋ ሆነ

በኢትዮጵያ በተለይ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በተከሰቱ ጦርነቶችና ግጭቶች ምክንያት እየተስተጓጎለ የመጣውን የሥነ ተዋልዶ ጤና አገልግሎት መልሶ ለማጠናከር ያስችላል የተባለ የ1.28 ቢሊዮን ብር ፕሮጀክት ይፋ...
[the_ad id="124766"]

በማህበራዊ ሚዲያዎች ይከታተሉን