– በሞያሌ የተፈጸመውን ጥቃት በመሸሽ በሺዎች የሚቆጠሩ ተሰደዋል
በኦሮሚያ ክልል ቦረና ዞን ሞያሌ ከተማ ቅዳሜ መጋቢት 1 ቀን 2010 ዓ.ም. ‹‹በተሳሳተ መረጃ›› በነዋሪዎች ላይ በተፈጸመ ግድያ ተደናግጠው ወደ ኬንያ የተሰደዱ ኢትዮጵያውያንን ለመመለስና ዕርዳታ የሚያስፈልግ ከሆነም ለማቅረብ፣ መረጃ እየጠበቀ መሆኑን ብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
ኮሚሽነሩ አቶ ምትኩ ካሳ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በአካባቢው የሚገኝ የኮሚሽኑ ቅርንጫፍ መረጃዎችን በራሱ መንገድ እየተከታተለ ነው፡፡ ዝርዝር መረጃ ከኮማንድ ፖስቱ እየጠበቀ መሆኑንም አክለዋል፡፡
‹‹በድንጋጤ የተፈናቀሉ ናቸው፡፡ በቀላሉ መመለስ የሚችሉ ናቸው፡፡ አስቸኳይ የምግብ አቅርቦትና የመሳሰሉትን መረጃው እንደደረሰን ማቅረብ እንችላለን፤›› ብለዋል፡፡
እስከ 50 ሺሕ የሚገመቱ ኢትጵያውያን በድንጋጤ በመሸሽ ወደ ኬንያ የዘለቁ መሆኑ እየተነገረ ቢሆንም፣ በኢትዮጵያ መንግሥት በኩል ትክክለኛው የስደተኞች ቁጥር ይፋ አልሆነም፡፡
ይሁን እንጂ ሰኞ መጋቢት 3 ቀን 2010 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ከ2,000 ሺሕ በላይ ኢትጵያውያን ስደተኞችን ሰሞኑን ተቀብሎ እንደነበር የገለጸው የኬንያ ቀይ መስቀል ማኅበር፣ በማግሥቱ ማክሰኞ ማምሻውን ባወጣው መግለጫ የስደተኞቹ ቁጥር 5,000 መድረሱን ይፋ አድርጓል፡፡ ከእነዚህም መካከል ነፍሰ ጡሮች፣ አራሶች፣ ሕፃናትና በሽተኞች እንደሚገኙበት ገልጿል፡፡ ስደተኞቹ በሰባት ጊዜያዊ መጠለያዎች ተጠልለው የአስቸኳይ ጊዜ ዕርዳታ እየቀረበላቸው መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡
ስደተኞቹ ወደ አገራቸው እንዲመለሱ መንግሥት እያደረገ ስላለው ጥረት መረጃ እንዲሰጥ ለአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አስፈጻሚ ኮማንድ ፖስት ጽሕፈት ቤት በተደጋጋሚ የተደረገው ሙከራ አልተሳካም፡፡ በተጨማሪም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መርማሪ ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ታደሰ ሆርዶፋንም ለማግኘት የተደረገው ሙከራ ስብሰባ ላይ በመሆናቸው አልተሳካም፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኮማንድ ፖስት ጽሕፈት ቤት ተወካይ ሌተና ጄኔራል ሐሰን ኢብራሂም ለመንግሥት መገናኛ ብዙኃን በሰጡት መግለጫ ግድያውን የፈጸሙት በአካባቢው የተሠማራ ሻለቃ ጦርና አባላቱ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የማስፈጸም ግዳጅ ውስጥ እንዳልነበሩ ገልጸው፣ በአካባቢው የሚንቀሳቀስ የኦነግ ኃይልን ለመቆጣጠር ወይም ለመደምሰስ ግዳጅ የተሰጠው እንደነበር ተናግረዋል፡፡
ይሁን እንጂ በተሳሳተ መረጃ ላይ በመመሥረት ዘጠኝ ሰዎችን ሲገድሉ፣ 12 ማቁሰላቸውን ይፋ አድርገዋል፡፡ ግድያውን የፈጸሙት አምስት አባላትና ዋና አዛዥ ትጥቅ ፈትተው በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ተናግረዋል፡፡ በጦር ፍርድ ቤት እንደሚዳኙም አስታውቀዋል፡፡ የመከላከያ ሠራዊት ከፍተኛ አዛዦች ያሉበት አጣሪ ቡድን በሞያሌ በንፁኃን ላይ የደረሰውን ጉዳት ለማጣራት መሄዱን አስረድተዋል፡፡