ከ150 ዓመታት በፊት በጉራጌ ምድር የሴቶችን መብት ለማስከበር በመንቀሳቀስ ዝናን ያተረፈችው የቃቄ ወርድወት የሕይወት ታሪክ ከክልሉ አልፎ የብዙዎችን ቀልብ ከሳበ ሰነባብቷል፡፡ የቃቄ ወርድወት በ1850ዎቹ በጉራጌ ማኅበረሰብ ውስጥ የሴቶችን የበታችነት ተቃውማ በሰባቱ የጉራጌ ወረዳዎች ሴቶችን አስተባብራ ነበር፡፡ በወቅቱ ካነሳቻቸው የጾታ እኩልነት ጥያቄዎች መካከል ሴት ልጅ የፍቺ ጥያቄ ማቅረብ ይፈቀድላት፣ ሴቶች እንደ ወንዶች በአካባቢው ሸንጐ ተሰብስበው ይምከሩ፣ ሴት ልጅ ከቤተሰቦቿ የሚገኝን ውርስ ከቀሪው ቤተሰቧ እኩል ትካፈል የሚሉት ጥቂቶቹ ናቸው፡፡
የቃቄ ወርድወትን ታሪክ የተመረኮዘ ቴአትር ባለፈው ሳምንት በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር ተመርቋል፡፡ ነሐሴ 24 ቀን 2007 ዓ.ም. የተመረቀው ቴአትሩ፣ የቃቄ ወርድወት በአካባቢዋ ታዋቂ ከሆነ ጀግና ጋር ትዳር ከምትመሠርትበት ዕለት አንስቶ ያለውን ሕይወቷን ያሳያል፡፡
ቴአትሩ የቃቄ ወርድወት ባለቤት ከእሷ ውጪ ሁለት ሚስቶች ያሉት መሆኑን ከመቃወም ተነስታ ሌሎችም በሴት ላይ የሚደርሱ ጭቆናዎችን ለማስቆም ስትታገል ያሳያል፡፡ እንደ እሷ የተጨቆኑ ሴቶችን አሰባስባ በአካባቢው ባህላዊ ሥርዓት ሴት ያለባሏ ፈቃድና ምርቃት ባሏን ፈትታ እንዳትሄድ የሚያስራትን እርግማን (በአካባቢው የጉራግኛ አጠራር አንቂት) እንዲነሳላት ጥያቄ ታቀርባለች፡፡
ቴአትሩ በርካታ ተከታይ ሴቶችን አፍርታ በአካባቢው ታይቶ የማይታወቅ ንቅናቄ ስትፈጥርና የሴቶቹን ጥያቄ አንግባ በቤተ ጉራጌ ጠቅላይ ሸንጐ ስትቀርብ ያስቃኛል፡፡ የማኅበረሰቡን ባህላዊ ሥርዓትና አኗኗር በሚገልጹ ግብዓቶች የታጀበው ቴአትሩ፣ አብዛኛውን ጊዜ የሰጠው ለሸንጐው ክርክር ነው፡፡ ከ60 በላይ ተዋንያንን ያሳተፈው ቴአትሩ የማኅበረሰቡ ባህላዊ ሙዚቃና አልባሳት ተካተውበታል፡፡
ከቃቄ ወርድወት የጥናት ቡድን አባላት አንዱ የብሔራዊ ቴአትር የትውፊታዊ ትውን ጥበባት፣ የጥናትና ምርምር ከፍተኛ ባለሙያ አቶ ደስታ ሎሬንሶ፣ ጥናቱ በተጠናቀቀበት ወቅት ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የወርድወት ጥያቄዎች በፌሚኒስት አንትሮፖሎጂ ንድፈ ሐሳብ የሚነሱ ጥያቄዎችን የያዙ ናቸው፡፡ ንድፈ ሐሳቡ የተጀመረው እ.ኤ.አ. 1960ዎቹ ሲሆን፣ ወርድወት ንድፈ ሐሳቡ እውቅና ከማግኘቱ ከ90 ዓመታት በፊት ጥያቄዎቹን አቅርባለች፡፡ አቶ ደስታ በዚህ ማስረጃ ተደግፈው ወርድወት በዓለም ግንባር ቀደም የሴቶች መብት ተከራካሪ እንደሆነች ያስረዳሉ፡፡
የዚህችን ሴት የሕይወት ታሪክ ወደ ቴአትር የቀየረው የብሔራዊ ቴአትር ትውፊታዊ ትውን ጥበባት ክፍል የጥናትና ምርምር ከፍተኛ ኤክስፐርት ጸሐፌ ተውኔት ጫንያለው ወልደጊዮርጊስ ነው፡፡ የቴአትሩ አዘጋጅ ዳግማዊ ፈይሳ ሲሆን፣ የቃቄ ወርድወትን ሆና የምትተውነው ደግሞ መስከረም አበራ ናት፡፡ ከ2፡30 ሰዓት በላይ የሚወስደው ቴአትሩ ዘወትር እሑድ በ8፡00 በቴአትር ቤቱ ይታያል፡፡