Sunday, March 26, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊአብነታዊው ሥራ

አብነታዊው ሥራ

ቀን:

ከሃያ ይበልጣሉ፡፡ በአገሪቱ ዕድገት ላይ አዎንታዊ ተፅዕኖ መፍጠር የሚችሉ የሶፍትዌር ምርቶችን ሠርተዋል፡፡ ሥራዎቻቸውንም ነሐሴ 28 ቀን 2007 ዓ.ም. በጁፒተር ሆቴል ለዕይታ አቅርበዋል፡፡ ፕሮግራሙን ያዘጋጀው የአይሲቲ የልቀት ማዕከል ሲሆን ለዕይታ የቀረቡት ሥራዎች ከጥቂት ሳምንታት በፊት አዘጋጅቶት በነበረው ውድድር ላይ የቀረቡ ሥራዎች ናቸው፡፡ በውድድሩ ከአንድ እስከ ሦስት የወጡ አሸናፊዎች የገንዘብ ሽልማት ተበርክቶላቸው ነበር፡፡ በዐውደ ርዕዩ የመሳተፍ ዕድሉን ያገኙት ግን በውድድሩ ተሳታፊ የነበሩት ሁሉ ናቸው፡፡

በአዳማ ዩኒቨርሲቲ የአምስተኛ ዓመት የሶፍትዌር ኢንጂነሪንግ ተማሪ የሆነችው አብነት ደሴ አንዷ የዐውደ ርዕዩ ተሳታፊ ነች፡፡ በውድድሩ ለመሳተፍ ያደረገችውን ጥረትና ከተሳትፎዋ በኋላ ያገኘችውን ውጤት ለሪፖርተር አብራርታለች፡፡ አብነት የውድድሩን መኖር እንደሰማች በዙሪያዋ ካስተዋለቻቸው ችግሮች መካከል ለአንዱ ቁልፍ ይሆናል ብላ ያሰበችው ላይ ለመሥራት አቀደች፡፡ “ለሕዝቡ አገልግሎት የሚውል ሶፍትዌር መሥራት የክላስ ፕሮጀክት መሥራት እንኳን ከባድ ነው” የምትለው ወጣቷ፣ ሥራውን ከጓደኞቿ ጋር ለመሥራት አነጋግራቸው እንደነበር ትናገራለች፡፡ ነገር ግን ሥራው ከባድ እንደሆነ በመግለጽ አብረዋት እንደማይሰሩ አስረዷት፡፡

በዚህ ተስፋ ቆርጣ አልቀረችም፡፡ ሥራ ፈላጊዎችንና ቀጣሪዎችን የሚያገናኝ ዌብሳይት ፈጠረች፡፡ ግማሽ ዓመትም ፈጅቶባታል፡፡ “ብቻዬን በመሥራቴ ትንሽ ከብዶኝ ነበር፡፡ ቢያንስ ሐሳብ የሚያካፍለኝ ሰው አልነበረም” የምትለው አብነት ሶፍትዌሩ የተመራቂ ተማሪዎችን ሥራ ለማግኘት የሚገጥማቸውን ፈተና እንደሚቀንስ ትገልጻለች፡፡

በውድድሩ ሰባተኛ የወጣች ሲሆን፣ እንዲህ ባሉ መድረኮች ስትሳተፍ የመጀመሪያዋ ነው፡፡ አጋጣሚው ራሷን የምታስተዋውቅበትና ለሙያዋ ዕድገት ትልቅ ሚና እንደሚጫወት ግምቷን ትናገራለች፡፡ ከዚህ ባሻገር ግን ሙያውን ችግር ላይ የሚጥሉ አጋጣሚዎች መኖራቸውን ትገልጻለች፡፡

“ብዙ ጊዜ የሶፍትዌር ሥራዎችን ከመግዛት ይልቅ አባዝቶ መጠቀም ተለምዷል” የምትለው ተማሪዋ፣ ሁኔታው የፈጠራ ሥራዎችን ዋጋ የሚያሳጣ እንደሆነና የባለሙያዎችን ሞራል የሚነካ መሆኑን ትናገራለች፡፡ ፈጠራዋ እንዲህ ባሉ አጋጣሚዎች ከመፈተኑ አስቀድሞ ለአንድ ኩባንያ በመሸጥ ተገቢውን ጥቅም ማግኘት ምኞቷ መሆኑን አልሸሸገችም፡፡

ለአንድ ቀን በቆየው በአውደ ርዕዩ ሌሎች በርካታ የፈጠራ ሥራዎች ለዕይታ የቀረቡ ሲሆን፣ በፈጠራ ሥራዎቹ መጠቀም እንደሚችሉ የተገመቱ ኩባንያዎች እንዲጎበኙት ተደርጓል፡፡ አብዛኛዎቹ ፈጠራዎችም ማንኛውም ሰው በዕለት ከዕለት እንቅስቃሴው ሊገለገልባቸው የሚችሉ ናቸው፡፡ የአገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ ከግምት ያስገቡ፣ የኢንተርኔት ኮኔክሽን በሌለባቸው አጋጣሚዎችም አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ ተደርገው የተሠሩም አሉ፡፡

ርብቃ ይልማ ትባላለች፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሁለተኛ ዓመት ሶፍትዌር ኢንጂነሪንግ ተማሪ ነች፡፡ ኢትዮፒዲያ ኢንሣይክሎፒዲያ የተሰኘ ሶፍትዌር ሠርታለች፡፡ እንደእሷ ገለፃ የፈጠረችው ሶፍትዌር ማንኛውንም አገር ተኮር የሆኑ መረጃዎች በጽሑፍ ያቀርባል፡፡ በዌብ ሳይትና በዲስክቶፕ አፕልኬሽንም ተዘጋጅቷል፡፡ ሥራውን ሠርቶ ለመጨረስ ዓመት ያህል ቢፈጅባትም፣ አገልግሎት መሥጠት የሚያስችለውን የመጨረሻ ሥራ ገና አላጠናቀቅችም፡፡ ጥቂት ማስተካከያዎች ይቀሯታል፡፡

በዌብሳይትና በዲስክቶፕ አፕልኬሽን የተዘጋጀው ሶፍትዌሩ፣ ማንኛውንም የአገር ውስጥ መረጃዎች በየትኛውም አካባቢ ለማግኘት ያስችላል፡፡ “ኔትወርክ በሌለበት አጋጣሚ እንኳን በዲስክቶፕ የሚጫነው ሶፍትዌር መረጃዎች ለማግኘት ያስችላል” ትላለች፡፡ አገሪቱን አስመልክቶ የሚገኙ እውነታዎች፣ ታሪክና ሌሎችም መረጃዎች በሶፍትዌሩ በመታገዝ ማግኘት እንደሚቻል ትናገራለች፡፡ በተጨማሪም እንደዊኪፒዲያ ሁሉ መረጃዎች በተጠቃሚዎች ወደ ድረገጹ ማስገባት የሚቻል ሲሆን፣ ይህም ዩዘር በሚል እንደሚያዝ ትናገራለች፡፡

የአይሲቲ የልቀት ማዕከል ዳይሬክተር አቶ ቴዎድሮስ መብራቱ እንደገለፁት፣ በአይሲቲ ሙያ በርካታ የአገሪቱን ችግሮች መቅረፍ ይቻላል፡፡ በአውደ ርዕዩ የቀረቡ ሥራዎችም ይህንኑ የሚያረጋግጡ ሲሆን የወጣቶቹ የፈጠራ ሥራ ሊበረታታ ይገባል፡፡ ይህንን ለማድረግም ማዕከሉ ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር አብሮ የሚሠራ ሲሆን መንግሥትም ለዘርፉ ልዩ ትኩረት በማድረግ ሙያው እንዲበለጽግ የበኩሉን እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

በዐውደ ርዕዩ ተሻሽሎ የቀረበ የልብ ምት መለኪያ መሣሪያ፣ የአለቃን ቦታ ተክቶ የሚሠራ አለቃ የተሰኘ ሶፍትዌር፣ አስኳላ የተባለ ወላጆች ልጆቻቸው በትምህርት ቤት የሚኖራቸውን እንቅስቃሴ የሚከታተሉበት ሶፍትዌር በአውደ ርዕዩ ለዕይታ ከቀረቡት መካከል ናቸው፡፡

spot_img
Previous article
Next article
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ለፋይናንስ ዘርፉ ብቃት ያለው የሰው ኃይል የማፍራት የቤት ሥራን የማቃለል ጅማሮ

የአገሪቱ የፋይናንስ ዘርፍ እያደገ ለመሆኑ ከሚቀርቡ ማስረጃዎች ውስጥ  የግል...

የምድር ባቡርን የሚያነቃቃው የመንግሥት ውሳኔ

በኢትዮጵያ ወደብ አልባነት ላይ የተደመረውን የሎጀስቲክስ ችግር ለመፍታት ግዙፍ...

የፓርላማ አባላት ስለሰላም ስምምነቱ አፈጻጸም ግልጽ መረጃ የለንም አሉ

‹‹ሕወሓትን ለፍረጃ አብቅተውት የነበሩ ጉዳዮች በአብዛኛው መልክ ይዘዋል›› ሬድዋን...