– ‹‹ምርመራ ዘመናት የሚያስቆጥር የአርኪዮሎጂ ቁፋሮ አይደለም›› የተጠርጣሪው አቶ ወንድሙ ቢራቱ ጠበቃ
በከባድ የሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ነሐሴ 3 ቀን 2007 ዓ.ም. በቁጥጥር ሥር ውለው በእስር ላይ የሚገኙት የኦሮሚያ ክልል ባለሥልጣን አቶ ወንድሙ ቢራቱ፣ የአውሮፕላን ትኬት በመግዛት በግብዣ መልክ ለባለሥልጣናት ጉቦ መስጠታቸው ተገለጸ፡፡
አቶ ወንደሙ የተጠረጠሩባቸውን የሙስና ወንጀሎች እየመረመረ የሚገኘው የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ ቡድን ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ተረኛ ችሎት እንዳስረዳው፣ ተጠርጣሪው በሥልጣን ዘመናቸው ወደ ውጭ አገር በመሄድ ምን ያህል ገንዘብ እንዳወጡና ለባለሥልጣናት የአውሮፕላን ትኬት በመቁረጥ በግብዣ መልክ ጉቦ የሰጡበትን ሰነድ ከሚመለከተው ተቋም መጠየቁን አስረድቷል፡፡
መርማሪ ቡድኑ ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዳው፣ ተጠርጣሪው የተጭበረበረ ሰነድ ሕጋዊ በማስመሰል መሬት የሸጡበትና ከባንክ ገንዘብ የተቀበሉበት ሰነድ ተሰብስቧል፡፡ ጉቦ በቼክ የተቀበሉበት ሰነድ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተሰብስቧል፡፡ ከሁለት ሰዎች ሦስት ሚሊዮን ብር ጉቦ መቀበላቸውን ከሚያረጋግጡ ሰዎች የምስክርነት ቃል መቀበሉንም ቡድኑ ገልጿል፡፡ ከጉምሩክ ከጠየቀው የማስረጃ ሰነድ ከፊሉን መሰብሰቡን፣ በኦሮሚያ ልዩ ዞኖች ለሚደረገው ምርመራ ደጋፊ ሰነድ በማቅረብ እየተከታተለ እንደሆነና አንድ ተጨማሪ ተጠርጣሪ በቁጥጥር ሥር አውሎ ቃሉን መቀበሉን መርማሪ ቡድኑ አስረድቷል፡፡
የኮሚሽኑ መርማሪ ቡድን ለተጨማሪ ምርመራ 14 ቀናት እንዲፈቀድለት የጠየቀ ሲሆን፣ ምክንያቱንም አስረድቷል፡፡ ተጠርጣሪው ብዙ ቤቶችና ቦታዎች እንዳሏቸው ጥቆማዎች በመምጣታቸው ከአራት ከተሞች ማኅደሮችን መሰብሰብ እንደሚቀረው፣ ከገቢዎችና ጉምሩክ ያልተሰበሰቡ ማስረጃዎችን መሰብሰብ፣ ተጨማሪ ሰነዶችን ለፎረንሲክ ምርመራ በመላከ ትክክለኛነቱን አረጋግጦ መሰብሰብ፣ ሌሎች ያልተያዙ ተጠርጣሪዎችን አድኖ መያዝና የምስክሮችን ቃል መቀበል ስለሚቀረው መሆኑን አስረድቷል፡፡
አቶ ወንድሙ ቀደም ባሉት ቀጠሮዎች እሳቸው የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት አባል ከመሆናቸውም በተጨማሪ፣ በእሳቸው ላይ የሚቀርብ ማንኛውንም ተጠያቂነት የመጠየቅ ሥልጣን ያለው የክልሉ መንግሥት መሆኑን በመናገር ሲከራከሩ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ተጠርጣሪው አሁንም በጠበቃቸው አማካይነት እንደገለጹት፣ የተጠረጠሩበትን የሙስና ወንጀል የማየት ሥልጣን ያለው የኦሮሚያ መንግሥት ብቻ ነው፡፡ የመመርመርና የመክሰስ ሥልጣን ያለው የኦሮሚያ የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ብቻ ነው፡፡ ይሄም በፌዴራል የፀረ ሙስና አዋጅ 433/97 አንቀጽ 7(4) እና በአዋጅ ቁጥር 434/97 አንቀጽ 7(2/4) ተደንግጓል ብለዋል፡፡ ፌዴራል የክልሉን ሥልጣን ማክበር እንዳለበት በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 50(8) መደንገጉንም አስረድተዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ በጉዳዩ ላይ የዳኝነት ሥልጣን ስለሌለውና ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮ መስጠት ስለማይችል፣ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 50(8) እና በወ/መ/ሥ/ሥ/ቁ 110 መሠረት ክሱን ዘግቶ ተጠርጣሪው እንዲያሰናብታቸው ጠይቀዋል፡፡
የፖሊስ ምርመራ ተጠናቆ ቀዳሚ ምርመራ ውስጥ መግባቱን የጠቆሙት የአቶ ወንድሙ ጠበቃ፣ የምርመራ ሥራ ዘመናት የሚያስቆጥር የአርኪዬሎጂ ቁፋሮ አለመሆኑንና በፍጥነት መፈጸም ያለበት የሕግ ሥራ በመሆኑን በመጠቆም ተጨማሪ ቀጠሮ መሰጠት እንደሌለበት አመልክተዋል፡፡
የወንጀሉ መፈጸም አጠራጣሪ መሆኑንና ተጠርጣሪውን ዋስትና ሊያስከለክላቸው እንደማይችል የገለጹት ጠበቃው፣ ወንጀሎቹ መፈጸማቸውን የሚያስረዳ ምንም ዓይነት ማስረጃ ካለመገኘቱም በተጨማሪ ተጠርጣሪው ወንጀሉን መፈጸማቸውም አጠራጣሪ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አጠራጣሪ ወንጀል የቅጣት ጣሪያው ምንም ያህል ቢሆንም የዋስትና መብት እንደማያስከለክል ጠቁመው፣ መርማሪ ቡድኑ የጠየቀው ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ታልፎና መዝገቡ ተዘግቶ ከእስር እንዲፈቱ ወይም የመንቀሳቀስ መብታቸው ተገድቦ በዋስ እንዲፈቱ ጠይቀዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኋላ በሰጠው ትዕዛዝ፣ የተጠርጣሪው ጠበቃ ቀደም ባለው ቀጠሮ መርማሪ ቡድኑ በጠየቀው ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ምንም እንዳልሠራ መግለጻቸውን በሚመለከት መዝገቡን ተመልክቶ፣ ጠበቃው እንዳሉት ሳይሆን ቡድኑ ምርመራ ማድረጉን ማረጋገጡን አስታውቋል፡፡ የተጠርጣሪ ጠበቃ የደንበኛቸውን ጉዳይ የፌዴራል መንግሥት ወይም ፍርድ ቤቶች ማየት እንደማይችሉና ሥልጣኑ የክልሉ መሆኑን በመጥቀስ መዝገቡ ተዘግቶ አቶ ወንድሙ በነፃ እንዲሰናበቱ ያቀረቡትን አቤቱታ እንዳልተቀበለው አስረድቷል፡፡ ያልተቀበለበት ምክንያት ቀደም ባሉ ቀጠሮዎች ተመሳሳይ ጥያቄ ቀርቦ ችሎቱ ብይን የሰጠበት መሆኑን በመግለጽ፣ ለመርማሪ ቡድኑ ተጨማሪ ዘጠኝ ቀናትን በመፍቀድ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
አቶ ወንድሙ ሥልጣናቸውን በመጠቀምና ከፌዴራል ባለሥልጣናት ጋር በመመሳጠር አገራዊ ጠቀሜታ ላላቸው የተለየ ክህሎት ለሚጠይቁ የኢንቨስትመንት ዘርፎች የተፈቀደውን ከቀረጥ ነፃ መኪና ማስገባት መብት በመጠቀማቸው፣ በአገር ውስጥና በውጭ አገር ሀብት በማከማቸት፣ በሕገወጥ መንገድ ያካበቱትን ሀብት ሕጋዊ በማስመሰል፣ በዘመዶቻቸው ስም ሀብት በማስቀመጥ፣ ለመንግሥት መግባት የነበረበትን ታክስና ቀረጥ ለግል መጠቀሚያ በማድረግ፣ ጉቦ በመቀበልና በማቀባበል ወንጀሎች መጠርጠራቸውን የኮሚሽኑ መርማሪ ቡድን ቀደም ባሉት ችሎቶች ለፍርድ ቤቱ ማስረዳቱን መዘገባችን ይታወሳል፡፡