የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ድሪባ ኩማ አዲሱን ዓመት በማስመልከት ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጠተዋል፡፡ ከንቲባው ባለፈው ጳጉሜን 4 ቀን 2007 ዓ.ም. በሰጡት መግለጫ፣ በአዲስ ዓመት የሚከናወኑ ዋና ዋና የሚባሉ ጉዳዮችን አብራርተዋል፡፡ ከእነዚህ ዋና ዋና ጉዳዮች መካከል የአከራይ ተከራይ ሕግ በአዲሱ ዓመት እንደሚፀድቅ፣ አቅም ለሌላቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች መንግሥት መኖሪያ ቤት ገንብቶ በኪራይ እንደሚሰጥ ገልጸዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በተለያዩ ምክንያቶች የመኖሪያ ቤት ለማግኘት ከተመዘገቡ 968 ሺሕ ነዋሪዎች መካከል ከግማሽ በላይ የሚሆኑ ተመዝጋቢዎች በአግባብ እየቆጠቡ ባለመሆናቸው ምክንያት ዳግም ምዝገባ እንደሚኖር ከንቲባው ተናግረዋል፡፡
የፖለቲካ ጉዳዮችን በተመለከተ ከተናገሩት መካከል፣ በአዲስ አበባ ከተማ ስለተደረጉ ግምገማዎችና ስለሚወሰዱ ዕርምጃዎች፣ ስለአዳዲስ የሰው ኃይልና አመራር አመዳደብ፣ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታትና የሕዝቡን ተሳትፎ ስለማጠናከር፣ የአዲስ አበባና የኦሮሚያ ልዩ ዞን የጋራ ማስተር ፕላን በአዲሱ ዓመት ሥራ ላይ እንደሚውልና በአገር አቀፍ ደረጃ ኦሮሚያና አዲስ አበባ ከተማ አስተዳድር በጋራ መድረክ ውይይት እንደሚያደርጉ ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ጋር በማስተር ፕላኑ ላይ ውይይት በሚደረግበት ወቅት፣ በተለይ በኦሮሚያ ክልል ተወላጆችና ካድሬዎች ‹‹በማስተር ፕላኑ በጀት ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ማግኘት ያለበት ልዩ ጥቅም ሊከበር ይገባል›› የሚል አቋም ይንፀባረቅ ስለነበር፣ ከንቲባ ድሪባ ለዚህ ጥያቄ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ የመግለጫውን ዋና ጉዳዮችና ቃለ ምልልሱን ለመመልከት እዚህ ላይ ይጫኑ፡፡