[ክቡር ሚኒስትሩ ቢሯቸው እንደገቡ አማካሪያቸውን አስጠሩት]
- እንኳን አደረስዎት ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ለምኑ?
- ለአዲስ ዓመት ነዋ፡፡
- አንተ ሥራ ቀይረሃል እንዴ?
- እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
- ከበዓሉ በፊት እንኳን አደረሰህ አልከኝ፡፡
- ለዋዜማው ነዋ፡፡
- የበዓል ቀን ቴክስት ላክልኝ፡፡
- ምን አጠፋሁ ታዲያ?
- በዓሉም አልፎ እንኳን አደረሰህ ትለኛለህ?
- የመልካም ምኞት መግለጫ ነዋ፡፡
- ምኞት ምን ያደርጋል? ዋናው ተግባር ነው፡፡
- ከእናንተ ተምሬ ነዋ፡፡
- ምኑን?
- ይኼን ባህሪ ነዋ፡፡
- እንዴት?
- እናንተ ሁሌም ትመኛላችሁ እንጂ ተግባር ላይ የት አላችሁበት?
- አልገባኝም እባክህ?
- ያው መልካም አስተዳደር ይሰፍናል፣ ሙስና ይቀረፋል ምናምን እያላችሁ ትመኛላችሁ እንጂ መቼ ትተገብሩታላችሁ?
- እ…
- ለዚያ ነው ከእናንተ ተምሬ ነው ያልኩት፡፡
- ለመሆኑ ሪፖርቶቹ የት አሉ?
- የምን ሪፖርት?
- አዲስ ሥራ የምንጀምርበት ዘመን መሰለኝ፡፡
- እ… እየተሠራ ነው፡፡
- ይህን የቤት ሥራ ከሰጠሁህ እኮ ወር ሆኖታል፡፡
- አዎ ግን ችግር አለ፡፡
- የምን ችግር?
- ሠራተኛው ይከፈለኝ እያለ ነው፡፡
- ደመወዝ መከፈል ቆሟል እንዴ?
- አይ ደመወዝ አይደለም፡፡
- ታዲያ ምንድነው?
- የውሎ አበል፡፡
- የምን የውሎ አበል?
- ክቡር ሚኒስትር የአንዳንድ ዲፓርትመንት ሠራተኞች የውሎ አበል ይከፈላቸዋል፡፡
- በምን ስሌት?
- በርካታ እንግዶችን ስለሚያስተናግዱ ተብሎ፡፡
- ደመወዝ ይከፈላቸዋል አይደል እንዴ?
- እንደውም በወር የሚያገኙት የውሎ አበል ክፍያ ከደመወዛቸው ጋር ሲነፃፀር የትዬለሌ ነው፡፡
- ጭራሽ?
- አዎን ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምን ተሻለ?
- የሚሻለውማ ለሌሎቹም መክፈል ነው፡፡
- ምንድነው የሚከፈለው?
- የውሎ አበሉ ነዋ፡፡
- እሱ ነው የአንተ ምክር?
- ከልጅ ልጅ ቢቆዩ ዓመትም አይቆዩ አይደል የሚባለው፡፡
- ዓመት አትቆይም እያልከኝ ነው?
- ያው ሹም ሽር ደርሷል ብዬ ነው፡፡
- ቢደርስስ?
- ወጥ የሆነ አሠራር ያስፈልጋላ፡፡
- አሁን ለሌላው ሠራተኛ አስበህ ነው ወይስ ለራስህ አስበህ ነው?
- እኔስ ብሆን ልጅዎት አይደለሁም?
- ስለዚህ የሪፖርቱ አለመቅረብ ዋናው ምክንያት ይኼ ነው እያልከኝ ነው?
- አዎን ክቡር ሚኒስትር፡፡
- በል በአፋጣኝ ሠራተኛውን ስብሰባ ጥራልኝ፡፡
[ክቡር ሚኒስትሩ ጸሐፊያቸውን አስጠሯት]
- ሪፖርቱን ምን አደረስሽው?
- የቱን ሪፖርት?
- ባለፈው ሳምንት ያዘዝኩሽን?
- እየሠራሁት ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እስካሁን አላለቀም?
- የሚመለከታቸው ሠራተኞች በሚገባ ስለማይተባበሩኝ ነዋ፡፡
- ለምን?
- የውሎ አበል ጉዳዩ ነዋ፡፡
- ወይ ይኼ የውሎ አበል ነገር፤ ደመወዝ ይከፈላችኋል አይደል እንዴ?
- ማን በደመወዙ ይኖራል?
- ታዲያ በምንድነው የሚኖረው?
- በደመ – አበሉ ነዋ፡፡
- ማን ነው የፈቀደላቸው ለመሆኑ?
- የክፍሉ ኃላፊዎች ናቸዋ፡፡
- እኔ ሳላውቅ?
- ክቡር ሚኒስትር የኑሮ ውድነቱ እኮ አይቻልም፡፡
- ስለዚህ መፍትሔው አበል ነው?
- ሌላ መፍትሔም አለ፡፡
- ምንድነው እሱ?
- የኑሮ ውድነቱን መቆጣጠር፡፡
- እኔ እናንተን ራሱ መቆጣጠር አቅቶኛል፡፡
- መጀመሪያ ራስዎትን ይቆጣጠሩ፡፡
- ምን አልሽ?
- አይናደዱ ማለቴ ነው፡፡
[የክቡር ሚኒስትሩ ጓደኛ ሚኒስትር ደወሉ]
- በዓል እንዴት አለፈ ክቡር ሚኒስትር?
- ድግሱ እንዴት አለፈ ማለትህ ነው?
- ለመሆኑ እየተዘጋጁ ነው?
- ለምኑ?
- ለደስታ ወይም ለሐዘን፡፡
- የምን ደስታና ሐዘን ነው?
- ወቅቱን ረሱት እንዴ?
- እኮ ምንድነው?
- ያው በዘመኑ መጀመሪያ ላይ በዓላት አሉ ከዚያም የእኛ ዋናው በዓል አለ፡፡
- የትኛው በዓል?
- ሹም ሽሩ ነዋ፡፡
- እ…
- ለማንኛውም አንድ ኮሚቴ ተቋቁሟል፡፡
- የምን ኮሚቴ?
- ተሿሚዎችን የሚመለምል፡፡
- እኔ የሌለሁበት?
- አዎን ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እ…
- አሁን የደወልኩት ሰው እንዲጠቁሙኝ ነው፡፡
- የምን ሰው?
- ሊሾም ይገባዋል የሚሉትን ነዋ፡፡
- ከየት?
- ከእርስዎ መሥሪያ ቤት፡፡
- አንድ ሰው ነው ልጠቁምህ የምችለው፡፡
- ማን ነው እሱ?
- እኔው ነኝ፡፡
- የእርስዎ አማካሪ እንዴት ነው?
- ስለእሱ ምን እንደማስብ ታውቃለህ?
- ምንድነው የሚያስቡት?
- አህያ ታውቃለህ አህያ ነው፡፡
- አህያ የሚያማክረው እኮ አህያን ብቻ ነው፡፡
- እየሰደብከኝ ነው?
- ራስዎትን እየሰደቡ ነው እንጂ፡፡
- ለመሆኑ ምንድነው መሥፈርቱ?
- ብሔርንና ጾታን ያማከለ መሆን አለበት፡፡
- ሌላስ?
- የትምህርትና የሥራ ብቃቱ እንደተረጋገጠ ሆኖ ማለት ነው፡፡
- በቃ?
- ከዚህ በላይ ምን እንፈልጋለን?
- የፓርቲ ታማኝነትስ?
- ክቡር ሚኒስትር ከፓርቲ በፊት ያለው እኮ አገር ነው፡፡
- እ…
- ፖለቲካና ፓርቲ የሚኖረው ቅድሚያ አገር ስትኖር ነው፡፡
- እሱማ ልክ ነው፡፡
- ስለዚህ ብቃት ያላቸው ሰዎች አገሪቷን ማገልገል ከፈለጉ ቦታ ሊያገኙ ይገባል፡፡
- ለፓርቲው ታማኝ ባይሆኑም?
- ለአገርና ለሕዝብ ታማኝ ከሆኑ ይበቃል፡፡
- እና እኛን አሽቀንጥራችሁ ልትጥሉን ነው ማለት ነው?
- እሱ ወደፊት የሚታይ ጉዳይ ነው፡፡
- ይህ ጉዳይ እኮ እንቅልፍ የሚነሳኝ ነው፡፡
- ለእዚህ ነው እኮ ዕረፍት የሚያስፈልግዎት፡፡
- የምን ዕረፍት?
- መተኛት አለብዎት፤ በቂ ዕረፍት ማግኘት አለብዎት፡፡
- የዓመት ዕረፍት ልውሰድ ታዲያ?
- ሌላ ዕረፍት ቢወስዱ አይሻልም?
- ሌላ ምን ዕረፍት?
- ከሥልጣን ዕረፍት ቢወስዱስ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ከሾፌራቸው ጋር ወደ ቤት እየሄዱ ነው]
- ክቡር ሚኒስትር በጣም ነው የገረመኝ፡፡
- ምኑ ነው የገረመህ?
- በኤርትራ ያሉት ተቃዋሚዎች ጉዳይ፡፡
- እኮ ምኑ ገረመህ?
- መጣላታቸው ነዋ፡፡
- መቼ ተስማምተው ያውቃሉ?
- ደግሞ ከመንግሥት ጋር ለዓመት ያህል ይገናኙ ነበር፡፡
- መረጃ ያቀብሉን ነበር፡፡
- መንግሥት ግን የሚገርም የስለላ አቅም ነው ያለው፡፡
- ይህ እኮ የተካንበት ነው፡፡
- ሌላ ግን ያሳዘነኝ ነገር አለ፡፡
- ምንድነው ያሳዘነህ?
- ከኤርትራ ተገንጥለው የመጡት ተቃዋሚዎች በአንዴ ጀግና ሆኑ፡፡
- ታዲያ ምኑ ነው የሚያሳዝንህ?
- እነሱ ጀግና መሆናቸው ነዋ፡፡
- ምን ችግር አለው?
- ስንቱ እዚህ ለአገሩ እየለፋ ዞር ብሎ የሚያየው የለም፣ እነሱ አገር ሲወጉ ቆይተው ሲመለሱ በአንዴ ጀግና ሆኑ፡፡
- ከጥፋታቸው ስለተመለሱ ነው ጀግና የሆኑት፡፡
- አጥፍተው የማያውቁ ጀግና አይባሉም እንዴ?
- መጽሐፍ ቅዱስ የምታነብ መስሎኝ?
- እንዴት?
- ጌታ እኮ ዘጠና ዘጠኙ በጐቹን ትቶ የጠፋበትን አንድ በግ ሊፈልግ እንደሄደ እንዳትረሳ፡፡
- ስለዚህ?
- እኛም 99 ሚሊዮኑን ሕዝብ ትተን የጠፉትን ልንፈልግ ሄድና፡፡
- ስለዚህ የጠፋው ልጅ ታሪክ ሊደገም ነዋ፡፡
- የትኛው?
- ጠፍቶ የነበረው ልጅ ሲገኝ እኮ ታላቅ ድግስ ተደርጎለታል፡፡
- እናስ?
- ስለዚህ እኛ ተስፋ የለንማ?
- ለምኑ?
- ለ40/60 ነዋ፡፡
- የምን 40/60 አመጣህ?
- ያው የጠፉት በጐች ስለተመለሱ ለእነሱ ማበረታቻ ይሰጣቸዋል ብዬ ነዋ፡፡
- ጥሩ ሐሳብ አመጣህልኝ፡፡
- እና እኔ ጀግና ለመባል ምን ላድርግ?
- ጀግንነት የሚጠይቀውን ማድረግ ነዋ፡፡
- ኤርትራ ደርሶ መምጣት ነው?
- ሞክረው እስቲ?
- ባለፈው እንዲሁ ስታስገርሙኝ ነበር፡፡
- በምኑ?
- ለዳያስፖራው እንደዚያ ስታሸረግዱ፡፡
- እንዴት?
- አገር ውስጥ ያሉ ጀግኖች ይወደሱ፡፡
- እነሱም ይወሰዳሉ፡፡
- ለመሆኑ ክቡር ሚኒስትር…
- ለመሆኑ ምን?
- ኤርትራ የቀሩት በአሥር ሺሕ የሚቆጠሩ ናቸው ይባላል፡፡
- ይህ የፕሮፓጋንዳ ሥራ ነው፡፡
- እንዴት?
- የቀሩት ጥቂቶች ናቸው፡፡
- ማናቸው የቀሩት?
- በሽተኞች፣ አቅመ ደካሞችና የኪነት አባላት ናቸው፡፡
- ስለዚህ ከኪነት አባላቱ እንጠብቃ፡፡
- ምን?
- ነጠላ ዜማ!