የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መጋቢት 13 ቀን 2007 ዓ.ም. ዕጣ ያወጣባቸው 35 ሺሕ የጋራ መኖሪያ ቤቶች (ኮንዶሚኒየም) ካርታ ተሠርቶ ባለመጠናቀቁ፣ ቤቶቹ ለደረሳቸው ዕድለኞች ማስረከብ አለመቻሉ ተጠቆመ፡፡
አስተዳደሩ በአራት ኪሎ፣ የካ አባዶ፣ ገላን፣ ቱሉ ዲምቱና በተለያዩ ቦታዎች 41 ሺሕ ቤቶችን አዘጋጅቶ ስድስት ሺሕ ያህሉን ለልማት ተነሺዎች፣ 35,000 የሚሆኑትን ደግሞ ለነባር ተመዝጋቢ ዕድለኞች በዕጣ እንዲደርስ ካደረገ በኋላ፣ እስከ ሰኔ 5 ቀን 2007 ዓ.ም. ከአስተዳደሩ ጋር ውል እንዲፈጽሙ ማድረጉ ይታወሳል፡፡
ውሉን ከአስተዳደሩ የተለያዩ ወረዳ ጽሕፈት ቤቶች በመቅረብ (በየክፍላተ ከተሞቹ) ተዋውለው ከጨረሱ በኋላ 20 በመቶ ቅድሚያ ክፍያ ሲፈጽሙ፣ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለት ወራት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ጠርቶ የብድር ውል እንደሚፈራረሙ ገልጾላቸው እንደነበር፣ በዕጣ ዕድሉ የደረሳቸው ግለሰቦች ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
የቤቶቹ ዕጣ ከወጣ ስድስት ወራት እንደሞላውና 20 በመቶውን ከከፈሉ አራት ወራት እንደሞላቸው የሚናገሩት አቶ በዛብህ ንጉሡ የተባሉ ዕድለኛ፣ ባንኩ በሁለት ወራት ውስጥ እንደሚጠራቸው የነገራቸው ጊዜ ከማለፉም በተጨማሪ፣ 11ኛው ዙር የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ ሊወጣ መሆኑን በመገናኛ ብዙኃን ሲሰሙ ሥጋት እንደገባቸው ገልጸዋል፡፡ ዕጣው እንደወጣላቸው ከታወቀ ጊዜ ጀምሮ አከራዮቻቸው ‹‹ነገ ጥሎት ለሚሄደው›› በማለት የኪራይ ዋጋ በእጥፍ እንደጨመሩባቸው የሚናገሩት አቶ በዛብህ፣ ባንክ በሁለት ወራት ውስጥ ውል ፈጽሞ ቤቱን እንደሚረከቡ ተስፋ በማድረጋቸው የተጨመረባቸውን የቤት ኪራይ በወቅቱ ችላ ቢሉም፣ አሁን ግን ባንኩ ዝም በማለቱ ግራ እንደገባቸው ተናግረዋል፡፡
ለእሳቸውና ለሌሎች ዕድለኞች የደረሰው መኖሪያ ቤት ሳይተላለፍ ስለሌላ ዕጣ ሲወራ ሲሰሙ ግራ በመጋባታቸው ወደ ባንክ ሄደው ሊጠይቁ ቢሞክሩም በቂ ምላሽ እንዳላገኙ የሚናገሩት አቶ በዛብህ፣ አስተዳደሩ ወይም ሌላ የሚመለከተው አካል ችግሩ ምን እንደሆነ እንዲያስረዷቸው ጠይቀዋል፡፡
እንደ አቶ በዛብህ ሁሉ አብዛኛዎቹ የዕድሉ ተጋሪዎች ከባንክ ጋር ውል አለመፈጸሙና ቤቱን አለመረከባቸው ግራ እንዳጋባቸው እየገለጹ መሆኑን የ65 ዓመት ዕድሜ እንዳላቸው የሚናገሩት ወይዘሮ ቀለሟ ተገኝም አስረድተዋል፡፡ ችግር ካለም የሚመለከተው አካል ግልጽ እንዲያደርግላቸው እሳቸውም እንደ አቶ በዛብህ ጠይቀዋል፡፡
በአሥረኛው ዙር የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ የደረሳቸው ዕድለኞች በየክፍለ ከተማው ከሚገኙ ከቤቶች አስተዳደር ጽሕፈት ቤቶች ጋር የመጀመርያውን የቤት ባለቤትነት ውል ከፈጸሙ በኋላ፣ 20 በመቶ ቅድሚያ ክፍያ ለባንክ ከፍለዋል፡፡
የቤቱን ካርታ በመያዝ የብድር ውል ከዕድለኞቹ ጋር መፈጸም ያለበት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ ለምን ውሉን እንዳልፈጸመ ከሪፖርተር ለቀረበለት ጥያቄ የባንኩ የኮሙዩኒኬሽን ሥራ አስኪያጅ አቶ ኤፍሬም መኩሪያ ሲመልሱ፣ ‹‹ችግሩ የባንኩ አይደለም፡፡ ባንኩ ካርታ ተሠርቶ ከተሰጠው ትክክለኛነቱን በማረጋገጥ ውል ይፈጽማል፡፡ ነገር ግን በየሳይቱ ተሠርቶ የቀረበለት ካርታ በጣም ትንሽ ነው፡፡ በመሆኑም ካርታው ተሠርቶ ካልተሰጠው ውል መፈጸም አይችልም፤›› ብለዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቤቶች አስተዳደር ኤጀንሲን ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ መስፍን መንግሥቱ በጉዳዩ ላይ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ካርታ የሚያዘጋጀው የመሬት አስተዳደር ነው፡፡ ‹‹እስካሁን ሰባት ሺሕ ካርታዎችን አዘጋጅቷል፡፡ በእርግጥ በተለያዩ ባለድርሻ አካላት የተጠቀሱት ክፍተቶች አሉ፡፡ ክፍተቶቹን ለመሙላት በጋራ እየሠራን ነው፡፡ የመሬት አስተዳደር፣ የቤቶች ግንባታ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት፣ የቤቶች አስተዳደር ኤጀንሲና ሌሎችም ያሉበት ኮሚቴ ተዋቅሮ በመረባረብ እየተሠራ ነው፤›› ሲሉ አቶ መስፍን አስረድተዋል፡፡
ካርታው ሲሠራ ጥንቃቄ የሚፈልግ መሆኑንና አብዛኛው የዕድሉ ባለቤት የሚያቀርበው ሰነድ ደግሞ ከጋብቻ መኖርና መፍረስ፣ ከስም ስህተትና ከመሳሰሉት ጋር የተገናኘ በመሆኑ፣ እሱን ማስተካከሉ ጊዜ የሚወስድ መሆኑንም አቶ መስፍን አክለዋል፡፡ ባንክ አንድ ፊደል ቢጎድል ስለማይረከብ ሥራው ልዩ ጥንቃቄ የሚፈልግ መሆኑን የገለጹት ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ ካርታውን በዋናነት የሚሠራው መሬት አስተዳደር መሥሪያ ቤት ሠራተኞች ወደ ሥልጠና መግባታቸውም ጫና መፍጠሩን ጠቁመዋል፡፡
ሌላው እያንዳንዱ ቤት የማን እንደሆነ የሚያረጋግጠው የዲዛይንና የቴክኒክ ሥራ በተለይ በየካ አባዶ፣ በአቃቂ ቃሊቲ፣ በገላንና ገነት መናፈሻ ሳይቶች ላይ ችግር በመፈጠሩ፣ እንደገና እየተከለሰ እንደነበር አክለዋል፡፡ በአሁኑ ጊዜ ግን የአውቶካድ ኤክስፐርቶች በየሳይቱ በቋሚነት ተመድበው እየሠሩ በመሆናቸው ችግሩ እየተቀረፈ እንደሆነ አቶ መስፍን ተናግረዋል፡፡
ሁሉም ባለድርሻ ተረባርቦ በመሥራት እስከ መስከረም 30 ቀን 2008 ዓ.ም. ድረስ ሁሉም ካርታ ተጠናቆ ለባንክ መሰጠት እንዳለበት አቅጣጫ ተቀምጦ እየተሠራ በመሆኑ፣ ሥራው እንደሚጠናቀቅና ለዕድለኞቹ ቁልፍ ማስረከብ እንደሚከናወን ተናግረዋል፡፡ አዲስ ይወጣል ስለሚባለው 11ኛ ዙር የጋራ መኖሪያ ቤቶች ጉዳይ የተጠየቁት አቶ መስፍን፣ ጎን ለጎን ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑን ጠቁመው የወጡ ዕጣዎች ለዕድለኞች ሳይተላለፉ ሌላ ዕጣ እንደማይወጣ፣ ቀጣዩ ዕጣ መቼና በየትኛው ወር እንደሚወጣ አሁን መናገር እንደማይቻል አስታውቀዋል፡፡