ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ገቢ ማሰባሰቢያ የሚውል የሙዚቃ አልበም ተመርቋል፡፡ ‹‹የሕብር ዜማ ለሕዳሴአችን›› የተሰኘው የሙዚቃ አልበም ከተለያዩ ብሔረሰቦች የተውጣጡ ሙዚቀኞች የተሳተፉበት ነው፡፡ አልበሙ በሲዲ፣ ቪሲዲና ካሴት የተዘጋጀ ሲሆን፣ በ25 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡
በአልበሙ ላይ የተሳተፉ ድምፃውያን ሰብለ መዝሙር፣ ኢሳን አብዱልሰላም (ሐረሪኛ)፣ ሙስጠፋ አብዲ (ሱማሊኛ)፣ አስናቀ አባተ (ጉምዝ)፣ ብርሃኔ ዜና (ኦሮምኛ)፣ ይገረም አሰፋ (ሐዲያ)፣ አማረ ሰሚከ (ጋሞኛ)፣ ዘውዱ በቀለ (ወላይትኛ)፣ ተስፋዬ ታዬ (አማርኛ)፣ ጆን አናንቦ (ጋምቤላ)፣ መሐመድ ሲርጋጋ (ስልጢኛ)፣ ፈለቀ ማሩ (ጉራግኛ)፣ ትርሐስ ታረቀኘ (ትግርኛ) እና ሁሴን ዓሊ (አፋርኛ) ናቸው፡፡
ግጥምና ዜማ በማሰናዳት ከተሳተፉ ባለሙያዎች መካከል ሰለሞን ደነቀ፣ አዳሙ ገመቹና መኰንን ለማ ይጠቀሳሉ፡፡ በሙዚቃ ክሊፖቹ ዝግጅት ደግሞ ስንታየሁ ሲሳይ፣ ታደሰ ማስረሻ፣ ኤልያስ በቀለና ሌሎችም ተሳትፈዋል፡፡
ከ100 በላይ ባለሙያዎች ከክፍያ ነፃ የተሳተፉበት አልበሙ፣ መስከረም 10 ቀን 2007 ዓ.ም. በካፒታል ሆቴል ሲመረቅ፣ በዕለቱ 8100 ኤ ዳግም መጀመሩም ይፋ ሆኗል፡፡
ለግድቡ ግንባታ ገቢ ከሚሰበሰብባቸው መንገዶች አንዱ የሆነውና የአጭር የጽሑፍ መልዕክት ከላኩ ግለሰቦች መካከል እድለኞች የሚሸለሙበት 8100፣ ልዩ ልዩ ዕጣዎች ማካተቱን አዘጋጆቹ አሳውቀዋል፡፡ በመጀመሪያው ዙር በሰባት ወር ውስጥ ከ28 ሚሊዮን በላይ አጭር የጽሑፍ መልዕክቶች ተልከው፣ ከ80 ሚሊዮን ብር በላይ መሰብሰቡ ይታወሳል፡፡ የሁለተኛውን ዙር 8100 መጀመር ያሳወቁት በመጀመሪያው ዙር ቅስቀሳ ላይ የተሳተፉት ኮሜዲያኖች ናቸው፡፡
የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ሕዝባዊ ተሳትፎ ማስተባበሪያ ብሔራዊ ምክር ቤት ዋና ሥራ እስፈጻሚ ወ/ሮ ሮማን ገብረሥላሴ እንደተናገሩት፣ ሕዝቡ ለግድቡ ግንባታ በተለያየ መንገድ በሚያደርገው ተሳትፎ ውስጥ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎችም ይጠቀሳሉ፡፡
የግድቡ ግንባታ ከተጀመረ አንስቶ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ ኅብረተሰቡ ለግድቡ ያለው አስተዋጽኦ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በሁሉም የጥበብ ዘርፍ ያበረከቱት አስተዋፅኦ በታሪክ ልዩ ቦታ እንደሚይዝ ወ/ሮ ሮማን ተናግረዋል፡፡