Sunday, October 1, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

ክቡር ሚኒስትር

[ክቡር ሚኒስትሩ የቀላል ባቡር ፕሮጀክት ጅማሬ ሥነ ሥርዓት ላይ ተገኝተው ከተጋባዥ እንግዶች መካከል ከአንደኛው ጋር እያወሩ ናቸው]

  • አንተ ለመሆኑ እዚህ አገር አለህ እንዴ?
  • አለሁ ክቡር ሚኒስትር፣ የት እሄዳለሁ ብለው ነው?
  • እኔማ አይቼህ ስለማላውቅ ከአገር የወጣህ መስሎኝ ነው፡፡
  • አገሬን ጥዬማ የትም አልሄድም፡፡
  • አዎ አገራችን እያደገች ስለሆነ ጥሎ መሄድማ ጥሩ አይደለም፡፡
  • ከአገር ጥፉ ጥፉ የሚያሰኙ በርካታ ችግሮችማ አሉ፡፡ ግን…
  • ግን ምን?
  • እየታየ ባለው የልማት ጅማሬ ባንፅናና ኖሮ መጥፋታችንማ አያስገርምም፡፡
  • ምን ችግር ኖሮ ነው እንዲህ የተመረርከው?
  • ራሳችሁ በግልጽ ያመናችሁዋቸው ችግሮች ምን ሊባሉ ነው?
  • በእርግጥ ችግሮች ቢኖሩም እነሱን በቆራጥነት ለመፍታት ወስነናል፡፡
  • ቆራጥነቱ እኮ ከወሬ አላልፍ እያለ ነው፡፡
  • ይኼው ባቡሩን ሥራ እንዳስጀመርነው ሌላውንም እናቀላጥፈዋለን፡፡
  • የዘገየው ባቡር ሥራ መጀመሩ ደስ ቢልም፣ የእናንተ ቆራጥነት ግን ያሳስበኛል፡፡
  • ለምን ያሳስብሃል?
  •  ከስብሰባ የመግለጫ ጋጋታ በስተቀር ተግባራዊነቱ ላይ ታጠራጥራላችሁ፡፡
  • ስብሰባዎቻችን እኮ የስትራቴጂዎቻችን መቀመሪያ ናቸው፡፡
  • ብዙዎቹ ስብሰባዎቻችሁ ደግሞ ዴሞክራሲና ፍትሕን ማዳፈኛ እየሆኑ ነው፡፡
  • ምሳሌ አቅርብልኝ፡፡
  • ለምሳሌ ከመቐለው ጉባዔ በኋላ ቴሌቪዥኑን ሳየው ወሬው ሁሉ ዴሞክራሲ አይሸትም፡፡
  • ምንድነው የሚሸተው?
  • የተለመደው የጎረና ፕሮፓጋንዳ፡፡
  • የአንተ አፍንጫ ታሞ ቢሆንስ?
  • ይኼ እኮ ነው ችግራችሁ፡፡
  • ምኑ?
  • ተቃውሞ ሲቀርብ ለማረም ከመሞከር ይልቅ ማጣጣል፡፡
  • ስለዚህ?
  • ስለዚህማ ዛሬ በደስታ የተጀመረው የባቡር ትራንስፖርት ዓይነት በሕዝብ ተቀባይነት ያለው ሥራ አሳዩ፡፡
  • ተቃዋሚ ትመስላለህ፡፡
  • መደገፍም መቃወምም መብት መሰለኝ፡፡
  • አንዴ እንኳ ምሥጋና ከአፍህ አይወጣም?
  • ምሥጋና ለሚገባው ይቀርባል፡፡ የሚወቀሰው ደግሞ በደንብ ይቀጠቀጣል፡፡
  • ምን ይሻልሃል?
  • ወቀሳ ማቅረብ፡፡
  • ወቀሳ ምን ያደርግልናል?
  • በአድርባዮች ሽንገላ የሞቀ ልባችሁን ቀዝቀዝ ያደርገዋል፡፡
  • እንዲያው ምን ቢደረግ ይጥማችኋል?
  • ልባችንን ማሸነፍ ከቻላችሁ በቂ ነው፡፡
  • አሁንስ?
  • አሁንማ ሩብ መንገድ አልደረሳችሁም፡፡
  • ተሳስተሃል፡፡
  • አንድ ነገር ልንገርዎት?
  • ምን?
  • ከውዳሴ ይልቅ ለወቀሳ ትኩረት ስጡ፡፡
  • እስቲ ይሁና!

 

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሾፌራቸው ጋር ወደ ቤት እየተመለሱ ነው]

  • የባቡሩን ሥራ መጀመር እንዴት አገኘኸው?
  • ደስ ይላል… ግን…
  • ግን ምን?
  • በቻይና የሚነዳ ባቡር ማየት ይገርማል፡፡
  • የእኛዎቹ እኮ እስከሚሠለጥኑ ነው፡፡
  • ቻይና ለወራት ሠልጥነው ተመለሱ ተብሎ እኮ በቴሌቪዥን ሲታዩ ነበር፡፡
  • ቢሆንም የሥራ ላይ ልምምድ ማድረግ ይገባቸዋል፡፡
  • የሚገርመው የፌርማታዎቹን ስያሜ አየተንተባተበች የምትጠራው ሴት መንገደኞችን ታሳስታለች፡፡
  • ምን ብላ ጠራች?
  • ስለ ምትኮላተፍ አይሰማም፡፡
  • ለጊዜው መቻል ነው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር በአማርኛ ባይነገረን እኮ ሁላችንም ቃሊቲ ገብተን ነበር፡፡
  • ምን ልትሆኑ?
  • ሳንዘጋጅ እስረኞችን ልንጠይቅ፡፡
  • አሹፈህ ሞተሃል፡፡
  • እውነቴን ነው እኮ?
  • ሌላስ?
  • ለዘመናት አንበሳ አውቶቡስ በኢትዮጵያውያን እንዳልተነዳ ለባቡራችን ቻይና መሆኑ አናዶኛል፡፡
  • ለጊዜው ነው ሲባል አልሰማህም እንዴ?
  • ለጊዜው ነው እየተባለ ስንቱ ዘለዓለማዊ ለመሆን ሲታገል እያየን?
  • ማነው እሱ?
  • እሱን ሆድ ይፍጀው፡፡
  • ከማን ጋር ነው የምትውለው?
  • ከጓደኞቼ ጋር፡፡
  • ስንተዋወቅ?
  • ምኑን?
  • ውሎህን ነዋ፡፡
  • ሆሆሆ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • አይዞህ ለጨዋታ ያህል ነው፡፡
  • አዎ ቻይናም በሰፊው እየተጫወች ነው፡፡
  • ምን ዓይነት ጨዋታ?
  • በባቡር ፌርማታዎች ላይ የተጻፉትን አይተዋል?
  • ምን ተጻፉ?
  • ቻይንኛ ይሁኑ አማርኛ የማይገቡ ነገሮች በሽ ናቸው፡፡
  • ወሬኛ!

[ክቡር ሚኒስትሩ ቤታቸው ገብተው ከባለቤታቸው ጋር ምሣ ለመብላት ገበታ ቀርበዋል]

  • የባቡሩን ሥራ መጀመር በአካል ተገኝተሽ ብታይው ጥሩ ነበር፡፡
  • ሥራ አላጣሁም እባክህ፡፡
  • ምነው?
  • ቴሌቪዥኑ እየደጋገመ ካሳየኝ በቂ ነው፡፡
  • ምን ምን አየሽ?
  • ሕዝቡ ተሳፍሮ ሲጓዝና በየፌርማታው ሲወርድ አየሁ፡፡
  • ምን ተሰማሽ?
  • ከእኔ ይልቅ ወይዘሮ ስርጉት ያሉት ይሻላል፡፡
  • እሳቸው ደግሞ ምን አሉ?
  • ለዚህ ትውልድ ነው እንጂ ለእኛ ብርቅ አይደለም አሉ፡፡
  • ምን አልሻቸው?
  • እኔ ምን እላለሁ? እሳቸው ከአዲስ አበባ ድሬዳዋ የተንፈላሰሱበትን ዘመን እያስታወሱ ብዙ አወሩ፡፡
  • ምንድነው የሚሉት?
  • ለትውልዱ ዘመናዊ ባቡር ሥራ መጀመሩ ጥሩ ነው፡፡ ነገር ግን የበለጠ መሥራት እንጂ  በአንድ ጅምር መኩራራት አይገባም ነው ያሉት፡፡
  • ይኼው ከአዲስ አበባ – አዋሽ – ጂቡቲ፣ ከመቐለ – ወልዲያ – አዋሽ – ጂቡቲ ሥራው ቀጥሏል፡፡ ወደ ደቡብና ምዕራብ ኢትዮጵያም እንዲሁ ይቀጥላል፡፡
  • እሳቸው ይኼንን አላጡትም፡፡
  • ታዲያ ምን እያሉ ነው?
  • አንድ ነገር ከያዘ የማይለቀው ቴሌቪዥን በወሬ እንዳያደነቁረን ነው የሚሉት፡፡
  • ተደጋግሞ ቢወራ ምን ይላል?
  • እጅ እጅ ይላል ነው የሚሉት፡፡
  • ምኑ ነው እጅ እጅ የሚለው?
  • ድግግሞሹ፡፡
  • ወይ ጣጣ?

[ክቡር ሚኒስትሩ በጠዋት ቢሮአቸው ገብተው ጸሐፊያቸው አማካሪያቸውን እንድትጠራ ባዘዙዋት መሠረት መጣ]

  • እንዴት አደሩ ክቡር ሚኒስትር?
  • ምን ሰላም አለ ብለህ ነው?
  • ምን ሆኑ?
  • ትናንት ባቡሩ ሥራ ከጀመረ ጊዜ ጀምሮ ጨቅጫቂዎች በዝተውብኝ ስናደድ ነው ያደርኩት፡፡
  • አይ ክቡር ሚኒስትር ምድረ ኪራይ ሰብሳቢ የፈለገውን ቢያወራ ለምን ይናደዳሉ?
  • እንደሱ ነው ብለህ ነው?
  • አልገባኝም?
  • ዙሪያችንን ያሉ ሰዎች እኮ ናቸው በነገር የሚሸነቁጡን፡፡
  • እነሱ ያውሩ እኛ ሥራ ላይ ነን፡፡
  • ይኼም አባባል እያስተቸን ነው፡፡
  • ለምን?
  • ተቃውሞ መስማት አትፈልጉም እየተባለ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ምድረ ኪራይ ሰብሳቢን ዝም በሉዋቸው፡፡
  • ሥራ ላይ ነን እያላችሁ አበዛችሁት እያሉን ነው እኮ?
  • ምን እንበል ታዲያ ክቡር ሚኒስትር?
  • እኔም ግራ ገብቶኛል እባክህ፡፡
  • ምኑ?
  • ይህ ሕዝብ ምን እንደሚፈልግ?
  • መንጌም ያለው ይኸንን ነበር እኮ?
  • የእሱን ስም አታንሳብኝ፡፡
  • ለምን ክቡር ሚኒስትር?
  • ያቅለሸልሸኛል፡፡
  • እውነት ነው ክቡር ሚኒስትር ወደ ጉዳያችን እንግባ፡፡
  • የእነዚያን ሰዎች ፕሮፖዛል አየኸው?
  • ክቡር ሚኒስትር የየትኞቹን?
  • የአርቲስቶቻችንን ነዋ?
  • የሚገርሙ ፕሮፖዛሎችን ነው ያቀረቡት፡፡
  • ጠቅለል አድርገህ ንገረኝ እስቲ፡፡
  • ሲጀምሩ “እኛ ልማታዊ አርቲስቶች …” ነው ያሉት፡፡
  • እሺ?
  • የፕሮጀክቶቹ ጨረታዎች “ውስን ይሁኑልን” ብለዋል፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • ግልጽ ጨረታ እንዳይሆን፡፡
  • በጄ?
  • በ“ውስን” ጨረታዎች መሳተፍ ያለባቸውን የልማታዊ አርቲስቶችን ስም ዝርዝሮችም አቅርበዋል፡፡
  • እነ ማንን?
  • “ልማታዊ” የሚባሉትን ዋነኞቹን ነዋ፡፡
  • ከዚያስ?
  • እንደየፍላጎታቸው ፕሮጀክቱ ከተሰጣቸው በኋላ የድጋፍ ደብዳቤ እንዲጻፍላቸው፡፡
  • ለማን?
  • የድጋፍ ደብዳቤው ለየመንግሥታዊ መሥሪያ ቤቶች ተልኮ ስፖንሰርሺፕ እንዲጠይቅላቸውም ይፈልጋሉ፡፡
  • ይህንን ሁሉ ትብብር ምን ስለሆኑ ነው የሚጠይቁት?
  • “ልማታዊ አርቲስቶች በመሆናችን ነው” ብለዋል፡፡
  • የእኛ ጥቅም ምንድነው?
  • ክቡር ሚኒስትር መደራደር ነዋ፡፡
  • እኛው የራሳችንን ፕሮጀክትና የድጋፍ ደብዳቤ እየሰጠን እንደራደር?
  • ክቡር ሚኒስትር ዘመኑ እኮ የጥበብ ነው፡፡
  • የምን ጥበብ?
  • “ልማታዊ አርቲስቶች” የሚተውኑት ነዋ፡፡
  • እኛም ከእነሱ ጋር እንተውን እንዴ?
  • የግድ ይላል ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እኛ የምንተውነው ለምንድነው?
  • በዚህ ዘመን ማንም በድፍረት መተወን ስለሚችል፡፡
  • ያለ ሙያችን?
  • ክቡር ሚኒስትር ማን ሙያ ኖሮት ነው የሚተውነው? ለምሳሌ ልማታዊ የሚባሉት አርቲስቶቹም በጨበጣ እኮ ነው የሚተውኑት፡፡
  • እነሱ እኮ መድረኩን፣ ቴሌቪዥኑን፣ ሬዲዮኑን፣ ፊልሙን ሳይቀር በሙያቸው ተቆጣጥረውታል፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር አይመኗቸው፡፡ በጨበጣ መተወን ስለቻሉ እኮ ነው እኛንም…
  • እኛንም ምን?
  • በቁጥጥር ሥር ያዋሉን፡፡
  • በል ዝም በል!

[የክቡር ሚኒስትሩ አማካሪ ከወጣ በኋላ ጸሐፊያቸው የዳያስፖራ እንግዳ እንዳለ ነግራቸው እንዲገባ ተደረገ]

  • እስካሁን ወደ አሜሪካህ አልተመለስክም እንዴ?
  • አለሁ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምነው እዚህ ቆየህ እባክህ?
  • አዲሱን ዓመት ከቤተሰብና ከወዳጆቼ ጋር አክብሬ ልመለስ ብዬ ነው፡፡
  • በዓል አገር ቤት ማክበር ደስ ይላል አይደል?
  • በጣም እንጂ፡፡ ባቡሩን ባየንበት ዓይን ሌላው ግን…
  • ሌላው ምን?
  • አንዳንድ የማያቸውና የምሰማቸው ነገሮች ግን እርምት ያስፈልጋቸዋል፡፡
  • ለምሳሌ?
  •  በአዲሱ ዓመት ዋዜማ የሰማሁት አናዶኛል፡፡
  • ምን አናደደህ?
  • ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት በተገኙበት ሥነ ሥርዓት ላይ የሰማሁት ነገር አበሳጭቶኛል፡፡
  • እስኪ ንገረኝ፡፡
  • መድረኩን የሚመሩት አስገራሚ ጉዶች አዲሱ ዓመት የሚጀምረው ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት ነው ብለው አረፉት፡፡
  • እነማን ናቸው?
  •  “ልማታዊ አርቲስቶች” የምትሉዋቸው፡፡
  • ዘመኑ የሚቀየረው መቼ ነበር?
  • አገሪቱ በራሷ ካላንዴር መሠረት ቀኗ የሚቀያየረው ሁሌም ከንጋቱ አሥራ ሁለት ሰዓት ነው፡፡
  • ነው እንዴ?
  • አዎን፡፡
  • ማረጋገጫ አለው?
  • መንግሥት ለበዓላት መድፍ የሚተኩሰው በዚያ ሰዓት መሆኑ እኮ የአገሪቱ ልዩ መታወቂያ በሆነው ካሌንደር ምክንያት ነው፡፡
  • ልማታዊ አርቲስቶቹ ከየት አመጡት ታዲያ?
  • የዘንድሮ ‘ዕውቀት’ እኮ እንትን ሆኗል፡፡
  • ምን ሆነ?
  • ኮንትሮባንድ፡፡
  • ማለት?
  • ከየትም እየቃረሙ ማውራት የአዋቂነት ምልክት ከሆነ ከኮንትሮባንድ ዕቃ ተለይቶ አይታይም፡፡
  • ይኼ ነው ያበሳጨህ?
  • ሌላም አለ፡፡
  • ምንድነው እሱ?
  • እነዚህ “ልማታዊ …” የምትሉዋቸው ሰዎች በጣም አብዝተውታል፡፡
  • ምንድነው ያበዙት?
  • ጨረታ በውስን እየተባለ ያለ ውድድር ይሰጣቸዋል፡፡ በመንግሥት ስፖንሰርሺፕና በመሳሰሉት ሁሉንም ነገር መቆጣጠራቸው ብዙዎችን ቅር አሰኝቷል፡፡
  • እነሱ በትጋት ሲንቀሳቀሱ መደገፍ ተገቢ አይደለም ነው የምትለው?
  • ድጋፍ ሁሉንም አሳታፊ፣ ትክክለኛ፣ ፍትሐዊና ከሙስና የፀዳ ሲሆን ጥሩ ነው፡፡
  • አሁንስ?
  • አሁንማ የሚታየው አድልኦና መጥፎ መንፈስ የከበበው ድርጊት ነው፡፡
  • መጥፎ መንፈስ ስትል አልገባኝም?
  • ይኼንንማ እርስዎም ያውቁታል፡፡
  • ምኑን ነው የማውቀው?
  • በልማት ስም ከሚያጭበረብረውና ከሚያወናብደው ጋር አብሮ እፍ ማለቱን፡፡
  • ለመሆኑ ልማታዊ ማለት ምን እንደሆን ታውቃለህ?
  • ልማታዊ ማለት በሚገባ ይገባኛል፡፡ አልገባህ ያለኝ ሌላው ነው፡፡
  • ምኑ ነው የማይገባህ ታዲያ?
  • “ልማታዊ አርቲስት፣ ጋዜጠኛ፣ መሐንዲስ፣ ነጋዴ…” ብሎ ነገር ግን አይገባኝም፡፡
  • ለምን አይገባህም?
  • “ልማታዊ እስስት” ማለት ስለሚመስለኝ፡፡
  • እንዴት እባክህ?
  • እስስት በየደረሰበት አይደል ቀለሙን የሚቀያይረው?
  • እና?
  • እነዚህም ልማታዊ የምትሏቸው አካላቸው ከእናንተ ጋር ይምሰል እንጂ ልባቸው ሌላ ጋ ነው፡፡
  • የት?
  • ልባችን እያወቀው?
  • ልብህ ካወቀው ንገረኛ?
  • ሞቅ ሲላቸው ምን እንደሚሉዋችሁ ማየት ይፈልጋሉ?
  • የት?
  • ቺቺኒያ!
  • የባሰ አታምጣ!

 

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

ተመድንና ዓለም አቀፋዊ ሕግን ከእነ አሜሪካ አድራጊ ፈጣሪነት እናድን!

በገነት ዓለሙ በእኔ የተማሪነት፣ የመጀመርያ ደረጃ ተማሪነት ጊዜ፣ የመዝሙር ትምህርት...

የሰላም ዕጦትና የኢኮኖሚው መንገራገጭ አንድምታ

በንጉሥ ወዳጅነው ፍራንክ ቲስትልዌይት የተባሉ አሜሪካዊ ጸሐፊ ‹‹The Great Experiment...

ድህነት የሀብት ዕጦት ሳይሆን ያለውን በአግባቡ ለመጠቀም አለመቻል ነው

በአንድነት ኃይሉ ድህነት ላይ አልተግባባንም፡፡ ብንግባባ ኖሮ ትናንትም ምክንያት ዛሬም...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ ለሁለት ሳምንት ያክል የፓርቲ ስብሰባ ላይ ቆይተው አመሻሹ ላይ ወደ ቤታቸው ሲመለሱ ባለቤታቸው በአግራሞት ተቀብለው ስለቆይታቸው ይጠይቋቸው ጀመር]

እኔ እምልክ...? ውይ... ውይ... በመጀመሪያ እንኳን በሰላም መጣህ፡፡ እሺ ...ምን ልትጠይቂኝ ነበር? ይህን ያህል ጊዜ የቆያችሁት ለስብሰባ ነው? ስብሰባ ብቻ አይደለም። ከስብሰባ ውጪ ምን ነበር? በተለያዩ መሪ ሐሳቦች የተዘጋጁ ሥልጠናዎችን...

[ክቡር ሚኒስትሩ ለሁለት ቀናት የተካሄደውን የፓርቲያቸውን የሥራ አስፈጻሚ ስብሰባ አጠናቀው ወደ ቢሯቸው ሲመለሱ ቢሯቸው ውስጥ አማካሪያቸው አንድ ጽሑፍ በተመስጦ እያነበበ አገኙት]

ምንድነው እንደዚህ መስጦ የያዘህ ጉዳይ? መጡ እንዴ ክቡር ሚኒስትር፣ የፓርቲው ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ያወጣውን መግለጫ እያነበብኩ ነው፡፡ ግን እኮ ፊትህ ላይ የመገረም ስሜት ይነበባል፡፡ አዎ፣ መግለጫው ላይ...

[ክቡር ሚኒስትሩ እየጠራ ያለውን ሞባይል ስልካቸውን ተመለከቱ፣ የህዳሴ ግድቡ ተደራዳሪ መሆናቸውን ሲያውቁ ስልኩን አነሱት]

ሃሎ... ጤና ይስልጥኝ ክቡር ሚኒስትር? ጤና ይስልጥልኝ ክቡር ተደራዳሪ... የጥረትዎን ፍሬ በማየትዎ እንኳን ደስ አለዎት፡፡ እንኳን አብሮ ደስ አለን፣ ምን ልታዘዝ ታዲያ? የውኃ ሙሌቱንና አጠቃላይ የግድቡን የግንባታ ሁኔታ...