እሑድ መስከረም 9 ቀን 2008 ዓ.ም. አገልግሎቱን ከጊዮርጊስ እስከ ቃሊቲ የጀመረው የቀላል ባቡር አገልግሎት፣ ደኅንነቱ የተጠበቀና ለአደጋ የተጋለጠ እንዳይሆን ያላሰለሰ ጥረት መደረግ አለበት፡፡ ይኼ ዘመናዊ የባቡር አገልግሎት የከተማውን ነዋሪዎች የትራንስፖር ፍላጎት በማርካት፣ የሚጠበቅበትን አስተዋጽኦ ያበረክት ዘንድ ለአደጋ ተጋላጭ እንዳይሆን የሚመለከታቸው አካላት በሙሉ መትጋት ይኖርባቸዋል፡፡ መንግሥት የተጠቃሚዎችን ግንዛቤ ከማሳደግ ጀምሮ ደኅንነቱ የተጠበቀ የትራንስፖርት አገልግሎት ለመስጠት በሚከተሉት ዋነኛ ጉዳዮች ላይ ትኩረት ማድረግ ይኖርበታል፡፡
- የትራፊክ አደጋ ይታሰብበት
በአሁኑ ጊዜ በመላ አገሪቱ አውራ ጎዳናዎች ላይ የሚታዩት አሰቃቂ የትራፊክ አደጋዎች ከቁጥጥር ውጪ ከመሆናቸውም በላይ፣ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥም በጣም የከፉ አደጋዎች በተደጋጋሚ ደርሰዋል፡፡ የቀላል ባቡር የሙከራ አገልግሎት በተጀመረ ሰሞን በተደጋጋሚ በባቡር መስመሩ መከለያ አጥሮች ላይ የተለያዩ ተሽከርካሪዎች አደጋ አድርሰዋል፡፡ በከተማው ጎዳናዎች ላይ የሚታዩት ግድ የለሽ የማሽከርከር ተግባራት በዜጎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሱ ሲሆን፣ በአዲሱ የባቡር ትራንስፖርት ላይ ሊደርሱ የሚችሉ አሰቃቂ አደጋዎችን ከወዲሁ ለመከላከል ርብርብ ያስፈልጋል፡፡
በአገሪቱ አውራ ጎዳናዎች ላይ በቸልተኝነት፣ በችሎታ ማነስ፣ በሥነ ምግባር ጉድለቶች፣ በመንጃ ፈቃድ አሰጣጥና በቁጥጥር መላላት ምክንያት የዜጎችን ሕይወት እየቀጠፈ ያለው የትራፊክ አደጋ ወደ ባቡር አገልግሎቱ ከተዛመተ፣ አገሪቱ ከምትቋቋመው በላይ ይሆንባታል፡፡ በቀንም ሆነ በምሽት በፍጥነት እያሽከርከሩ የባቡር መስመሩን ሕገወጥ በሆነ መንገድ ለማቋረጥ ወደኋላ በማይሉ ሥርዓተ አልበኞችና ችሎታ አልባዎች ላይ ከፍተኛ ቁጥጥር መደረግ አለበት፡፡ አደጋ ደርሶ በበርካታ ሰዎች ላይ የሞትና የአካል መጉደል ከደረሰ በኋላ መፀፀት እርባና የለውም፡፡
በተለይ የመንገድ ደኅንነት ጉዳይ የሚመለከታቸው ተቋማት በበቂ የሰው ኃይል፣ መሣሪያዎችና ዘመኑ ባፈራቸው ቴክኖሎጂዎች በመታገዝ በኃላፊነት ስሜት ሥራቸውን ማከናወን አለባቸው፡፡ የባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት ተጠቃሚዎች ለአደጋ ከሚያጋልጡ ድርጊቶች ራሳቸውን በማራቅ በሥርዓት መሳፈርና መውረድ ይኖርባቸዋል፡፡ ባቡሩ በሥራ ላይ ባለበት ወቅት እንስሳትን እየነዱ ለመሻገር መሞከር፣ ከተዘጋጁት ማቋረጫዎች ውጪ በሕገወጥ መንገድ መሻገርና አላስፈላጊ ተግባራትን መፈጸም ብዙኃንን ለሞት ይዳርጋል፡፡ ከዚህ ቀደም በቀለበት መንገድ ላይ ለበርካታ ሰዎች ሞት ምክንያት የሆኑ ተግባራት በባቡር መስመሩ ላይ ከተደገሙ በአንድ ጊዜ የሚደርስ አደጋ የብዙዎችን ሕይወት ይቀስፋል፡፡ ስለዚህ ሁሉም ወገኖች በሥርዓት ኃላፊነታቸውን ይወጡ፡፡ ለትራፊክ አደጋ ልዩ ትኩረት ይሰጥ፡፡
- ሕገወጥ ተግባራት ይወገዱ
በባቡር አገልግሎቱ ላይ ትኩረት ከሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች መካከል ሕገወጥ ተግባራት ተጠቃሽ ናቸው፡፡ እነዚህም በተሳፋሪዎች ላይ ዝርፊያ መፈጸም፣ የባቡሩን የውስጥ ቁሳቁሶች መዝረፍ ወይም ማበላሸት፣ ሰዎችን በማስገደድ የማይፈልጉትን ተግባር ማከናወን (ፆታዊና ሌሎች ትንኮሳዎች)፣ ወዘተ. የመሳሰሉት ናቸው፡፡ እነዚህ ሕገወጥ ድርጊቶች በሕግ የሚያስጠይቁ ቢሆንም፣ የባቡሩን አገልግሎት በማደናቀፍ ለአደጋ የሚዳርጉ ናቸው፡፡ የባቡር አገልግሎቱ ለተጠቃሚዎች ቀልጣፋና የሚያረካ አገልግሎት እንዲሰጥ የግድ በመሆኑ፣ የሕገወጦች መደበቂያና የተገልጋዮች ሥጋት እንዳይሆን ከፌርማታዎች ጀምሮ እስከ መጨረሻው የጉዞ ማብቂያ ድረስ ፀጥታው አስተማማኝ መሆን አለበት፡፡ በተጨማሪም ከተገልጋዮች ፍላጎት ጋር የማይጣጣሙ ማናቸውም ዓይነት ሕገወጥ ድርጊቶች እንዳይከሰቱ ጠንካራ ቁጥጥር ያስፈልጋል፡፡
- የባቡር ፕሮጀክቱ ንብረቶች ጠንካራ ጥበቃ ይሻሉ
የአዲስ አበባ የቀላል ባቡር መስመር ፕሮጀክት ጠቅላላ የግንባታ ወጪ 474 ሚሊዮን ዶላር ሲሆን፣ ለኦፕሬሽንና ተያያዥ ሥራዎች ማከናወኛ ደግሞ 110 ሚሊዮን ዶላር ይወጣበታል፡፡ ከቻይና መንግሥት በብድር የተገኘ ከፍተኛ የአገር ሀብት የተከሰከሰበት የመሠረት ልማት ጠንካራ ጥበቃና እንክብካቤ ያስፈልገዋል፡፡ በብድር የተገኘው ገንዘብ ከነወለዱ የሚከፈልበት ይህ የአገር ሀብት፣ ለሌሎች ቀጣይ የመሠረተ ልማት ግንባታዎችም ፈሰስ የሚጠበቅበት በመሆኑ የዜጎችን ጥበቃና እንክብካቤ መፈለጉ የግድ ነው፡፡
ቀላል ባቡሩ በሚያልፍባቸው አካባቢዎች ውስጥ የሚገኙ የኤሌክትሪክና የስልክ መስመሮች፣ የባቡር ሐዲዶች፣ በግራና በቀኝ የሚገኙ የአጥር መከለያዎች፣ ፌርማታዎች፣ መወጣጫዎችና ሊፍቶች፣ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫዎችና የመሳሰሉት ንብረቶች ቀንና ሌሊት በባለቤትነት ስሜት መጠበቅ አለባቸው፡፡ ለአገሪቱ አዲስ የሆነው ይኼ የከተማ ዘመናዊ የባቡር አገልግሎት ቢስተጓጎል ታክሲ ጥበቃ በፀሐይና በውርጭ የሚቃጠለው ሕዝብ ነው የሚጎዳው፡፡ በአንድ የጉዞ መስመር ላይ በሚያጋጥም የንብረት ዝርፊያ ምክንያት የሚደርሰው ኪሳራ አገሪቱንም ችግር ውስጥ ይከታታል፡፡
- ንፅህና በእጅጉ ይታሰብበት
የባቡር አገልግሎቱን ሊያውኩ ይችላሉ ተብለው ከሚታሰቡት ችግሮች መካከል አንዱ የንፅህና መጓደል ነው፡፡ በተለያዩ የሕዝብ ትራንስፖርቶች ላይ የሚታየው የንፅህና ጉድለት በዚህ ዘመናዊ ባቡር ላይ ፈጽሞ ሊታይ አይገባም፡፡ የባቡር አገልግሎቱ ዘመናዊነት መገለጫው ለተገልጋዮች ምቹና ፅዱ የሆነ አገልግሎት መስጠት መቻሉ ነው፡፡ ስለዚህ ለፅዳት እንከን የሆኑና ምቾት የማይሰጡ ችግሮች የባቡር አገልግሎቱን ዕድሜ ያሳጥራሉ፡፡ ለንፅህና መጓደል መንስዔ የሚሆኑ የምግቦችና የፍራፍሬዎች ትራፊዎች፣ የማስቲካና የከረሜላ ልጣጮች፣ ወዘተ. የመሳሰሉትንና ለፅዳት ተቃራኒ የሆኑ ድርጊቶችን ማስወገድ ተገቢ ነው፡፡ ባቡሩ ውስጥ መመገብም ሆነ ለፅዳት የማይመቹ ተግባራትን መፈጸም በፍጹም መከልከል አለበት፡፡ ንፅህና ለዘመናዊ የባቡር አገልግሎት ወሳኝ ነውና፡፡
- የባቡር አገልግሎቱ የኢንሹራንስ ሽፋን ይጠናከር
በዘመናዊ የትራንስፖርት ሥርዓት ውስጥ ወሳኝ ከሆኑ ጉዳዮች መካከል አንዱ ኢንሹራንስ ነው፡፡ ይህ ከፍተኛ የአገር ሀብት የኢንሹራንስ ሽፋን ማግኘት ያለበት ሲሆን፣ የሦስተኛ ወገን ኢንሹራንስም አስገዳጅ በመሆኑ መግባት ግድ ይላል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ በአገሪቱ በከፍተኛ ደረጃ የሚስተዋለውን የትራፊክ አደጋ ለመቀነስና አደጋ ሲያጋጥም ለተጎጂዎች ካሳ ለመክፈል ሲባል፣ አስገዳጅ የሆነ የሦስተኛ ወገን የመድን አዋጅ ፀድቆ ተግባራዊ ሆኗል፡፡ ይህ አዋጅ የባቡር ትራንስፖርትን የሚመለከት በመሆኑ፣ የባቡር አገልግሎቱም በአዋጁ መሠረት ግዴታውን አጠናክሮ መቀጠል አለበት፡፡
በአጠቃላይ የባቡር አገልግሎቱ ለአደጋ እንዳይጋለጥ፣ ደኅንነቱ የተጠበቀ እንዲሆንና የተገልጋዮችን ፍላጎት የሚያረካ የአገር ሀብት መሆኑ እንዲመሰከርለት ያስፈልጋል፡፡ መንግሥትም ሆነ በየደረጃው ያሉ የሚመለከታቸው አካላት በከፍተኛ የአገር ፍቅር ስሜት በመነሳሳት፣ ለኅብረተሰቡ በመገናኛ ብዙኃንና በተለያዩ ዘዴዎች ተከታታይ የሆነ ግንዛቤ ሊያስጨብጡ ይገባል፡፡ ከፍተኛ የአገር ሀብት የፈሰሰባቸው መሠረተ ልማቶች ጤናቸው ተጠብቆ ዘለግ ላለ ጊዜ አገልግሎት እንዲሰጡ ሲፈለግ፣ የንብረቶቹ ባለቤት የሆነው ሕዝብ ሀብቱን በንቃት እንዲጠብቅ ተሳትፎው መጨመር አለበት፡፡ በሌሎች መሠረተ ልማቶች ላይ ሲፈጸሙ የነበሩ አሳዛኝ ድርጊቶች በባቡር መሠረተ ልማቱ ላይ በፍጹም መደገም የለባቸውም፡፡ በመሆኑም የቀላል ባቡር አገልግሎቱ ለአደጋ መጋለጥ የለበትም!