አንጋፋውና ታዋቂው ጋዜጠኛና ደራሲ ሙሉጌታ ሉሌ በአሜሪካ ቨርጂንያ አረፈ፡፡ ከቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግሥት ጀምሮ ባለፉት 50 ዓመታት በጋዜጠኛነትና በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች ያገለገለው ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ድንገት ያረፈው በሚኖርበት የአሜሪካ ቨርጂንያ መስከረም 23 ቀን 2008 ዓ.ም. መሆኑን ዘገባዎች አመልክተዋል፡፡
በባይብል አካዴሚ በመምህርነት ሥራውን የጀመረው አቶ ሙሉጌታ በብሥራተ ወንጌል ሬዲዮ (የአብዮታዊት ኢትዮጵያ ድምፅ ዓለም አቀፍ አገልግሎት) በኢትዮጵያ ሬዲዮና በአዲስ ዘመን ጋዜጣ በአዘጋጅነት መሥራቱ፣ በተወዳጇ መነን መጽሔትም አዘጋጅ እንደነበረ ገጸ ታሪኩ ያመለክታል፡፡ በማስታወቂያ ሚኒስቴር ሥር በነበረው የፕሬስ መምሪያ ኃላፊም ነበር፡፡
ከ1983 የመንግሥት ለውጥ በኋላ ከሙያ አጋሮቹ ጋር ባቋቋመው አጥቢያ ኮከብ አሳታሚ (አክፓክ) ድርጅት ሥር ትታተም የነበረችው ጦቢያ መጽሔት ዋና አዘጋጅ ሆኖ ሠርቷል፡፡ በተለይ በጦቢያ መጽሔት ዐምደኛነቱ ‹‹ጸጋዬ ገብረመድኅን አርአያ›› በሚል የብዕር ስም በሰላ ብዕሩ ይጽፋቸው የነበሩት መጣጥፎችም ዝነኛ አድርገውታል፡፡
በ1984 ዓ.ም. ‹‹አጥፍቶ መጥፋት›› የተሰኘ መጽሐፍ በዮሐንስ ሙሉጌታ ስም መጻፉ የሚነገርለት አቶ ሙሉጌታ፣ ለ17 ዓመታት በአሜሪካ በስደት ሲኖር በተለያዩ ድረገጾች ይሠራ እንደነበር ይታወቃል፡፡ አብረውት የሠሩ እንደሚመሰክሩት በተባ ብዕሩ በአማርኛ ሥነ ጽሑፋዊ አቀራረቡ በአርአያነት ያነሱታል፡፡