Friday, December 8, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊየሞ ኢብራሒም ፋውንዴሽን ሪፖርት ኢትዮጵያን በመልካም አስተዳደር አነስተኛ ደረጃ ሰጣት

የሞ ኢብራሒም ፋውንዴሽን ሪፖርት ኢትዮጵያን በመልካም አስተዳደር አነስተኛ ደረጃ ሰጣት

ቀን:

በየዓመቱ የአፍሪካ አገሮችን የመልካም አስተዳደር ደረጃን ይፋ በማድረግ የሚታወቀው የሞ ኢብራሒም ፋውንዴሽን ባወጣው ሪፖርት ኢትዮጵያ  በመልካም አስተዳደር ረገድ ዝቅተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ይፋ አደረገ፡፡ ባለፈው ሰኞ በለንደን ይፋ ባደረገው እ.ኤ.አ. የ2015 የአፍሪካ አገሮች መልካም አስተዳደር ደረጃ ከ54 የአፍሪካ አገሮች 21 የሚሆኑት በመልካም አስተዳደር ዝቅጠት እንዳሳዩ ጠቁሟል፡፡

ባለፉት አራት ዓመታት ከአንድ እስከ አሥር ከተቀመጡት መሪ አገሮች መካከል ግማሽ ያህሉ ብቻ መሻሻል እንዳሳዩ የሚገልጸው ሪፖርቱ፣ እ.ኤ.አ. ከ2011 በኋላ የአፍሪካ አገሮች በመልካም አስተዳደሩ ረገድ የተወሰነ መሻሻል በጥቅሉ በማስመዝገብ ባለፈው ዓመት 50.1 ዕድገት ማስመዝገባቸውን ሪፖርቱ ያሳያል፡፡

‹‹የአፍሪካ አገሮች ከ15 ዓመት በፊት ከነበረው ሁኔታ አንፃር ዛሬ ጤናማና ዴሞክራሲያዊ በሆነ ሁኔታ ውስጥ እየኖሩ ቢሆንም፣ የ2015ቱ ሪፖርት እንደሚያሳየው ወሳኝ በሆኑ መስኮች የታየው መሻሻል በተጠበቀው ደረጃ አልተመዘገበም ወይም በተቃራኒው ተፈጽሟል፡፡ ለዚህ ደግሞ ጥሩ የመሻሻል መስመር ላይ የነበሩት ጥቂት አገሮች ሳይቀር እየተንገዳገዱ መሆናቸው የማስጠንቀቂያ ደውል ሊሆነን ይገባል፤›› ሲሉ አስተያየታቸውን የገለጹት የሞ ኢብራሒም ፋውንዴሽን ሊቀመንበር ዶ/ር መሐመድ ኢብራሒም፣ ሁሉንም የአፍሪካ አገሮች ያማከለና ቀጣይነት ያለው መሻሻል በሁሉም መስክ ሲመዘገብ ብቻ የአፍሪካ የወደፊት ዕጣ ፈንታዋ ብሩህ እንደሚሆን ጠቁመዋል፡፡

ከአንድ እስከ 20 ደረጃን ይዘው ከሚገኙት መሪ አገሮች መካከል የመጀመሪያዎቹ አምስት አገሮች እ.ኤ.አ. በ2015 ሪፖርት ከፍተኛ ለውጥ ያመጡ መሆናቸው ሲጠቆም፣ ከእነዚህም መካከል ሴኔጋል ከነበረችበት የ9ኛ፣ ኬንያ ከነበረችበት የ14ኛ፣ ሞሮኮ ከነበረችበት የ16ኛ፣ ሩዋንዳ ከነበረችበት የ11ኛና ቱኒዝያ ከነበረችበት የ8ኛ ደረጃ ተነስተው ወደ መጀመሪያዎቹ አምስት አገሮች ተርታ መካተታቸው ተገልጿል፡፡

እ.ኤ.አ. ከ2011 ጀምሮ ኢትዮጵያ በጠቅላላው የመልካም አስተዳደር ግምገማ ከአሥሩ የመጀመሪያዎቹ አገሮች ተርታ ውስጥ የተካተተች ቢሆንም፣ በአዲሱ ሪፖርት አጠቃላይ ውጤቷ 48.6 በመቶ ነው፡፡ ይህም ከአፍሪካ አገሮች መካከል 31ኛ ደረጃን እንድትይዝ ሲያደርጋት ከቀጣናዋ ደግሞ 5ኛ አድርጓታል፡፡ ከአራቱ ዋና ዋና የመልካም አስተዳደር እመርታ ከሚታይባቸው ዘርፎች መካከል ሕዝባዊ ተሳትፎና ሰብዓዊ መብት፣ የሰው ሀብት ልማትና በተለይም ደኅንነትና የሕግ የበላይነት በቀዳሚነት ለምዘና የሚቀርቡ መሆናቸውን የሚገልጸው ሪፖርቱ፣ በደኅንነትና በሕግ የበላይነት ኢትዮጵያ በአኅጉሩ 26ኛ ደረጃ ሲኖራት በምሥራቅ አፍሪካ ደግሞ 5ኛ መሆኗን ያሳያል፡፡ በዚህ ዘርፍ 13.8 የመሻሻል ዕድገቷን እ.ኤ.አ. ከ2011 ጀምሮ ጠብቃ ብትገኝም፣ በአገር ውስጥ የእርስ በርስ ግጭቶችና በድንበር አካባቢ በሚታዩ ግጭቶች የመንግሥት ጣልቃ ገብነት ታክሎበት ለውጦች ቢመዘገቡም፣ በአገር ውስጥ በሚፈናቀሉ ዜጎችና በውጭ አገሮች የፖለቲካ ጥገኝነት በሚሹ ዜጎች ቁጥር ረገድ ሲታይ ግን፣ ደካማ አፈጻጸሞች መኖራቸውንም ሪፖርቱ ይፋ አድርጓል፡፡

በግለሰብ ደኅንነት ረገድ በአኅጉሩ 12ኛ ደረጃን እንደያዘች የሚያሳየው ሪፖርት፣ በዚህ ንዑስ ዘርፍ በተለይም በብጥብጥና ወንጀል እንዲሁም በሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ከአኅጉሪቱ በቀዳሚነት እንድትቀመጥ የሚያደርጋትን ሥራዎች ባለፉት አራት ዓመታት ውስጥ መሥራቷን የሞ ፋውንዴሽን የ2015 ሪፖርት ያስረዳል፡፡ በአንፃሩ በሕዝባዊ ተሳትፎና በፆታ እኩልነት አገሪቱ ዝቅተኛውን ደረጃ መያዟ ብቻ ሳይሆን፣ ባለፉት አራት ዓመታት ከፍተኛ ዝቅጠት ማሳየቷም ተመልክቷል፡፡ በዚህም ዘርፍ በሕዝባዊ ተሳትፎ ከአኅጉሩ 39ኛ ደረጃን ስትይዝ ለዚህም በዋነኝነት እንደማሳያ የቀረበው ፍትሐዊና ነፃ የሆነ ምርጫን የማካሄድ አቅሟ በኔጋቲቭ (-11.1) የተመዘገበ መሆኑ ታይቷል፡፡ በሴቶች ላይ በሚደርስ አድልኦና ጥቃትም አገሪቱ ኔጋቲቭ (-25.00) ያስመዘገበች መሆኑ ተገልጿል፡፡

የሪፖርቱን ይፋ መሆን ተከትሎ በተለያዩ ዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኃን ከተዘገቡት ጉዳዮች መካከል ኢትዮጵያን ያካተተው የቀዳሚዎቹ አሥር አገሮች ዝርዝር፣ በአፍሪካ መፃኢ ዕድል ከፍተኛ ሚና የሚኖራቸው አገሮች መኖራቸው ነው፡፡ ለዚህም ኢትዮጵያ በብሔራዊ ደኅንነት፣ በመረጃ ነፃነት፣ በማኅበራዊ አለመረጋጋትና መንግሥትን ያማከለ ግጭቶችን የመፍታት፣ የሥልጣን ሽግግርና የሙስና ወንጀልን ከመከላከሉ ጋር በተያያዘ እየታየ ያለው መሻሻል እንደሆነ ሜይል ኤንድ ጋርዲያን አፍሪካ የተሰኘ ድረ ገጽ አስፍሯል፡፡ ኢትዮጵያ ይፋ በሆነው አዲሱ ሪፖርት በአጠቃላይ ውጤት በ31ኛ ደረጃ ላይ መቀመጧ ብዙ የሚጠብቃት የቤት ሥራ እንዳለ የሚጠቁም መሆኑን፣ ከላይ በተጠቀሱት ዋና ዋና የመሻሻል ዕርምጃዎች ታግዛ ደረጃዋን ልታሻሽል እንደምትችልም ግምት መኖሩ ተጠቁሟል፡፡ እንደ አገር ምዕራብ አፍሪካዊቷ ኮትዲቯር እጅግ በጣም መሻሻልን ያሳየች አገር ሆና ስትገኝ፣ በአንፃሩ ወጣቷ ደቡብ ሱዳን በከፍተኛ ዝቅጠት የመጨረሻውን ደረጃ ይዛለች፡፡   

የሞ ኢብራሒም ፋውንዴሽን በሱዳናዊ ብሪታኒያዊ ቢሊየነር ዶ/ር ሞሐመድ ኢብራሒም የተመሠረተ ሲሆን፣ በአፍሪካ በመልካም አስተዳደርና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ምርምር የሚያደርግና የተለያዩ ስኬታማ የሥራ ውጤቶችን የሚደግፍ ድርጅት ነው፡፡ እ.ኤ.አ. ከ2006 ጀምሮ በዚህ ሥራ ላይ ሲገኝ መቀመጫውም ለንደን ነው፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ታዋቂው የኤሌክትሮኒክስ ብራንድ አይቴል የስትራቴጂ ለውጥ አካል የሆነውን አዲስ አርማ እና መለዮ ይፋ አደረገ።

በአለማችን ታዋቂ ከሆኑት የኤሌክትሮኒክስ ብራንዶች መካከል አንዱ የሆነው እና...

የጠቅላላ ጉባኤ ስብሰባ ጥሪ ለሸገር አነስተኛ የፋይናንስ ተቋም አ.ማ ባለአክሲዮኖች በሙሉ

ለሸገር አነስተኛ የፋይናንስ ተቋም አ.ማ ባለአክሲዮኖች በሙሉ የሸገር አነስተኛ የፋይናንስ...

[የክቡር ሚኒስትሩ ጸሐፊ፣ የሌላ ሚኒስትር ጸሐፊ ከሆነችው የቅርብ ወዳጇ ጋር በስልክ እየተጨዋወቱ ነው]

አንቺ ግን ምን ሆነሽ ነው? ጠፋሁ አይደል? ጠፋሁ ብቻ?! ምን ላድርግ ብለሽ...

በሱዳን ላይ ያጠላው የመከፋፈል ዕጣና ቀጣናዊ ተፅዕኖው

የሱዳን ጦርነት ስምንተኛ ወሩን እያገባደደ ይገኛል፡፡ ጄኔራል አብዱልፈታህ አልቡርሃን...