በመጪው ነሐሴ በብራዚል ሪዮ ኦሊምፒክ የብስክሌት ተወዳዳሪነቷን ያረጋገጠችው ኢትዮጵያዊቷ ሓድነት አስመላሽ ጥቅምት 6 ቀን 2008 ዓ.ም. በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው የብስክሌት ውድድር አሸነፈች፡፡
የደቡብ አፍሪካው ሳይክሊንግ ኒውስ ከሥፍራው እንደዘገበው የ106 ኪ.ሜ እሽቅድድሙን ሓድነት ያሸነፈችው በ3 ሰዓት 00.01 ደቂቃ በሆነ ጊዜ ነው፡፡
‹‹ቤስትሜድ ሳተላይት ክላሲክ›› የሚል መጠርያ ባለው ዓመታዊ ውድድር ሦስተኛ የወጣችው ሌላው ኢትዮጵያዊት ፀጋ ገብሬ ናት፡፡ ከሁለቱ ኢትዮጵያውያት መካከል ገብታ ሁለተኛ የወጣችው ደቡብ አፍሪካዊቷ ካርላ ኦቤርሆልዘር ናት፡፡
ባለድሏ ሓድነት አስመላሽ ከኢዜአ ጋር ባደረገችው ቃለ ምልልስ ‹‹ውድድሩ ከባድ ነፋስ ነበረው፣ ሁሉንም ተወዳዳሪዎች ጥያቸው ተገንጥዬ ብወጣም የአገሬ ልጅ መቅረቷን ሳይ ጠበቅኋት፣ ከዛም 10 ተወዳዳሪዎች ተፋጠጥን፣ በመጨረሻ አፈትልኬ በመውጣት በሰፊ ርቀት ማሸነፍ ችያለሁ፤ የአገሬ ልጅ ሦስተኛ በመውጣቷም ደስተኛ ነኝ፤›› ብላለች፡፡
ሓድነት ባለፈው መስከረም በኮንጎ ብራዛቪል በተካሄደው የመላው አፍሪካ ጨዋታዎች ለኢትዮጵያ የነሐስ ሜዳሊያ ማስገኘቷ ይታወሳል፡፡ አክሱም ተወልዳ ያደገችው ሓድነት በዘንድሮው የሪዮ ኦሊምፒክ ኢትዮጵያን የምትወክል ብቸኛዋ ብስክሌተኛ ሆናለች፡፡