መስከረም 14 ቀን 2008 ዓ.ም. በሳዑዲ ዓረቢያ የሐጅ ፀሎት ወቅት ሚና በተባለው ቅዱስ ሥፍራ በደረሰው አደጋ የሞቱት ኢትዮጵያውያን ቁጥር 53 መድረሱን፣ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት አስታወቀ፡፡ ለሟቾች በመጪው ዓርብ ጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም. አገሪቱ ውስጥ በሚገኙ መስጊዶች በሙሉ የፀሎት ሥነ ሥርዓት ይከናወናል ተብሏል፡፡
የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚዳንት ሼክ መሐመድ አሚን ጥቅምት 9 ቀን 2008 ዓ.ም. በሰጡት መግለጫ፣ የእስልምና ዕምነት ተከታዮችና የሃይማኖት አባቶች በሚደረገው የፀሎት ሥነ ሥርዓት ሟቾችን እንዲያስቡ አሳስበዋል፡፡
በዘንድሮ የሐጅ ፀሎት ላይ ለመሳተፍ ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ ከሄዱ አሥር ሺሕ ኢትዮጵያውያን የዕምነቱ ተከታዮች መካከል፣ 53 ያህሉ በአደጋው ሕይወታቸውን ማጣታቸው ተረጋግጧል፡፡
የእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት በሰጠው መግለጫ መሠረት፣ 48 ሟቾች ለሐጂ ፀሎት የሄዱበት ሥፍራ ቅዱስ በመሆኑ ሥርዓተ ቀብራቸው እዚያው እንዲፈጸም ቤተሰቦቻቸው በማሳሰባቸው ተግባራዊ ተደርጓል፡፡
በሐጅ የፀሎት ሥነ ሥርዓት ወቅት በተፈጠረው መጨናነቅና መረጋገጥ ሕይወታቸው ካለፈው 53 ኢትዮጵያውያን መካከል 43ቱ ከኢትዮጵያ የተጓዙ ናቸው፡፡ አሥሩ ደግሞ በሳዑዲ ዓረቢያ ነዋሪ መሆናቸውን ከመግለጫው ለመረዳት ተችሏል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ ከመላው ዓለም ለሐጅ ፀሎት ከተሰባሰቡት ሁለት ሚሊዮን ያህል የዕምነቱ ተከታዮች መካከል፣ እስካሁን 2,177 ያህሉ መሞታቸው መረጋገጡን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ የሳዑዲ ዓረቢያ የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትርና አልጋ ወራሽ መሐመድ ቢን ናይፍ አደጋው የደረሰበትን ቦታ ባለፈው እሑድ ሲጎበኙ፣ የአደጋው መንስዔ በጥብቅ እየተመረመረ መሆኑን መግለጻቸው ተነግሯል፡፡
ከዚህ በፊት በተለያዩ ጊዜያት በደረሱ አደጋዎች የዕምነቱ ተከታዮች መሞታቸው የሚታወስ ሲሆን፣ የዘንድሮው ግን እጅግ የከፋ ነው ተብሏል፡፡ በሚና ከደረሰው ቀደም ብሎ መካ ውስጥ በተከሰተ የክሬን ተገርስሶ መውደቅ አደጋ 111 ሰዎች ሞተዋል፡፡
በዘንድሮው አደጋ ኢራን 465፣ ማሊ 254፣ ናይጄሪያ 199፣ ግብፅ 182፣ ካሜሩን 76፣ ኒጀር 72፣ ሴኔጋል 61፣ ኢትዮጵያ 53፣ አይቮሪኮስትና ቤኒን 52፣ ሱዳን 30፣ ታንዛኒያ 20፣ ሶማሊያ 10 ዜጐች ከሞቱባቸው አገሮች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡