Sunday, June 4, 2023
- ማስታወቂያ -
- ማስታወቂያ -

የኤርፖርቶች ድርጅት ከፍተኛ ኃላፊዎችን ጨምሮ 15 ሠራተኞች በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ተከሰሱ

- ማስታወቂያ -

ተዛማጅ ፅሁፎች

– በክሱ ባልና ሚስት ተካተዋል

የሙስና ወንጀል በመፈጸም የተጠረጠሩት የኢትዮጵያ ኤርፖርቶች ድርጅት ከፍተኛ ኃላፊዎችን ጨምሮ 15 ሠራተኞች ላይ፣ የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ዓቃቤ ሕግ ጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም. ክስ መሠረተባቸው፡፡

በፌዴራል በከፍተኛ ፍርድ ቤት 18ኛ ወንጀል ችሎት ክስ የተመሠረተባቸው ተጠርጣሪዎች፣ አቶ ማስረሻ ምትኩ ፈንቴ የድርጅቱ የሰው ኃይል ልማትና ማኔጅመንት ዳይሬክተር፣ አቶ አስቻለው አወቀ የስትራቴጂክ ፕላኒንግና ፋይናንስ ዳይሬክተር፣ አቶ ፍቅረ ማርያም አያሌው የሰው ኃይል አስተዳደር ሥራ አስኪያጅ፣ አቶ ጌታቸው ደበበ የፋይናንስ ኦፊሰር፣ የአቶ ጌታቸው ባለቤት ወ/ሮ ስሜነሽ ጌታቸው አበጋዝ (የግል ሠራተኛ)፣ መቅደላዊት ባንቱ የወ/ሮ ስሜነሽ ወንድም ሚስት፣ ወ/ሮ ገነት አረጋ የአቶ ጌታቸው እናት፣ አቶ ሚካኤል አበበ የድርጅቱ የፋይናንስ አገልግሎት የክፍያና የሒሳብ ማጠቃለያ ማስተባበሪያ ኃላፊ፣ አቶ ንጉሤ ካህሳይ የፋይናንስ ኦፊሰር፣ እፀገነት ብርሃኑ ከፍተኛ የሒሳብ ሠራተኛ፣ ሔለን ብርሃነ የከፍተኛ ጥቅማ ጥቅምና መረጃ ኦፊሰር፣ አቶ መላኩ ወርቅነህ የፋይናንስ አገልግሎት ኃላፊ፣ እሌኒ ኤልያስ የፋሲሊቲዎች ዳይሬክቶሬት ኦፊስ ኢንጂነር የነበረች፣ አቶ ዘነበ ወሰኔ የራንዌይ ቴክኒሻን የነበረና አቶ መልካሙ አበበ በቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት አስተዳደር ጀማሪ የፋይናንስ ኦፊሰር ናቸው፡፡

ባልና ሚስት የሆኑት አቶ ጌታቸውና ወ/ሮ ስሜነሽ በመመሳጠር ድርጅቱ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር ያለውን የሠራተኞች ደመወዝና ጥቅማ ጥቅም ክፍያዎች አገልግሎት ውልን በመጠቀም፣ ሠራተኞች ባልሆኑ 189 ሰዎች ስም በድምሩ 3,335,950 ብር ወደ ግል አካውንታቸው ማስገባታቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡

ተከሳሾቹ የሐምሌና የነሐሴ ወር ደመወዝ ፔሮል በመሥራትና በተለያዩ ደረጃዎች ያሉ ኃላፊዎችን በማስፀደቅ፣ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ኤርፖርቶች ቅርንጫፍ ከድርጅቱ ገንዘብ ላይ ተቀናሽ በማድረግ፣ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጀሞ ቅርንጫፍ በወ/ሮ ስሜነሽ ስም በተከፈተ አካውንት ውስጥ ማስገባታቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡ በግለሰቧ ስም ብቻ የተከፈተውን አካውንት (Joint and/or Account) በጥምረት በማድረግ ወደ አቢሲኒያ ባንክ ጀሞ ቅርንጫፍ ማዛወራቸውንም ክሱ ይተነትናል፡፡

አቶ ጌታቸው በድርጅቱ የሚከፈላቸው የተጣራ ደመወዝ 1,173 ብር የነበረ ቢሆንም ደመወዛቸውን ወደ 9,816 ብር ከፍ በማድረግ፣ የተሰጣቸውን ኃላፊነት ያላግባብ በመጠቀም በመንግሥትና በድርጅቱ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ማድረሳቸውን የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ያቀረበው ክስ ያስረዳል፡፡

እሌኒ ኤልያስ የተባለች ተከሳሽ ድርጅቱን ከየካቲት 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ በራሷ ፈቃድ የለቀቀች መሆኗ እየታወቀ፣ አቶ ጌታቸው ከየካቲት እስከ ነሐሴ 2007 ዓ.ም. ድረስ በፔሮል ውስጥ በማካተት በወር 3,420 ብር በድምሩ 23,943 ብር እንዲከፈላት ማድረጋቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡ አቶ ዘነበ ወሰኔ የተባለው ተከሳሽም ከአቶ ጌታቸው ጋር በመመሳጠር፣ ከታኅሳስ 1 እስከ ነሐሴ 30 ቀን 2007 ዓ.ም ድረስ በወር 1,562 ብር በድምሩ 14,058 ብር እንዲከፈለው መደረጉም በክሱ ተጠቅሷል፡፡ አቶ ጌታቸው ለአቶ መልካሙ አበበ 13,178 ብር በባንክ ሒሳባቸው እንዲገባላቸው ማድረጋቸውንም ክሱ ያብራራል፡፡

አቶ ጌታቸውና ወ/ሮ ስሜነሽ ከድርጅቱ በተጭበረበረ መንገድ ወስደዋል የተባለውን ገንዘብ፣ በዘመዶቻቸውና በራሳቸው የተለያየ መጠን በማድረግ በባንክ በማስገባት፣ በወንጀል ድርጊት የተገኘን ገንዘብ ሕጋዊ አስመስለው ማቅረባቸውን፣ እንዲሁም ሽብርተኝነትን በገንዘብ መርዳትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የወጣውን አዋጅ ቁጥር 780/2005 አንቀጽ 29(2ሀናመ) ሥር የተደነገገውን መተላለፋቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡

አቶ ፍቅረ ማርያም፣ ማስረሻ፣ ሚካኤልና ንጉሤ የተባሉት ተከሳሾች ደግሞ በደመወዝ መክፈያ ፔሮልና መሸኛ ደብዳቤው ላይ የተገለጸው ደመወዝ ቀድሞ ከነበረው ጋር ሲነፃፀር ልዩነቱ ፍፁም የተጋነነ ሆኖ እያለ፣ የሰነዱን ትክክለኛነት ሳያረጋግጡና ሳይፈትሹ በፊርማቸው በማፅደቃቸው በድርጅቱና በመንግሥት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንዲደርስ ማድረጋቸውን ክሱ ይዘረዝራል፡፡ እፀገነት ብርሃኑ፣ ሔለን ብርሃነ፣ አስቻለው አወቀና መላኩ ወርቅነህ የተባሉት ተከሳሾች ደግሞ፣ እሌኒ ኤልያስ የተባለችው ተከሳሽ ከድርጀቱ ከየካቲት 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ በራሷ ፈቃድ ሥራዋን መልቀቋን የካቲት 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ለሰው ሀብት ልማትና ማኔጅመንት በደብዳቤ ካሳወቀች በኋላ፣ ያልሠራችበት ጊዜ ደመወዝ ተመላሽ እንዲሆን ማድረግ ሲገባቸው ሳያደርጉ በመቅረታቸው፣ ግለሰቧ 23,943 ብር ያላግባብ እንዲከፈላት በማድረጋቸውና ግዴታቸውን በአግባቡ አለመወጣታቸውን ገልጿል፡፡

በአጠቃላይ ተጠርጣሪ ተከሳሾቹ በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን ያላግባብ ሥልጣን መጠቀም፣ የመንግሥትን ወይም የሕዝባዊ ድርጅት ሥራን በማያመች አኳኋን መምራት፣ በሙስና ወንጀል የተገኘን ገንዘብ ሕጋዊ አስመስሎ ማቅረብ  የሚሉ አምስት የሙስና የወንጀል ክሶች ቀርበውባቸዋል፡፡

ክሱን የሚመረምረው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 18ኛ ወንጀል ችሎት ክሱን ካሰማ በኋላ፣ ተከሳሾቹ ዋስትና እንዲከበርላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ የአቶ ጌታቸው፣ ወ/ሮ ስሜነሽ፣ ወ/ሮ መቅደላዊትና ወ/ሮ ገነት አረጋን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ በማድረግ፣ ሌሎቹ ተከሳሾች ከ8,000 ብር እስከ 15,000 ብር በሚደርስ ዋስ እንዲፈቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ በክሱ ላይ መቃወሚያ ካላቸው እንዲያቀርቡ ለኅዳር 28 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጥሯል፡፡    

spot_img
- Advertisement -spot_img

የ ጋዜጠኛው ሌሎች ፅሁፎች

- ማስታወቂያ -

በብዛት ከተነበቡ ፅሁፎች