በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ተጠሪ ሚኒስትርና የካቢኔ አባል ሆነው በቅርቡ የተሾሙት አቶ አስመላሽ ወልደ ሥላሴ፣ ‹‹የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከት›› ይታይባቸዋል ያሏቸውን የፓርላማ አባላት አስጠነቀቁ፡፡
አቶ አስመላሽ ይኼንን የተናገሩት ባለፈው ሐሙስ ፓርላማው የቋሚ ኮሚቴዎች አመራሮችንና አባላት በደለደለበት ወቅት ነው፡፡
ፓርላማው ለመሠረታቸው 18 ቋሚ ኮሚቴዎች የሰየማቸውን አመራሮችና አባላት ድልድልን አስመልክቶ ሁለት ጥያቄዎች ቀርበዋል፡፡ እነዚህም ‹ከተማርንበት የትምህርት ዘርፍ ጋር ወደሚቀራረብ ኮሚቴ ውስጥ አልተደለደልንም፤› እንዲሁም ‹አንዳንድ አካላት ቋሚ ኮሚቴዎችን ደረቅና እርጥብ ብለው ይፈርጃሉ፡፡ የዚህ ምክንያቱም አንዳንድ ቋሚ ኮሚቴዎች የኢኮኖሚ ጥቅምና የውጭ ጉዞ የሚገኙባቸው በመሆኑ ነው፤› የሚሉ ናቸው፡፡
ለጥያቄዎቹ ምላሽ የሰጡት አቶ አስመላሽ፣ ለቋሚ ኮሚቴ አመራርነትና አባልነት በዋነኛነት እንደ መሥፈርት የሚታየው የፖለቲካ ቁርጠኝነት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የትምህርት ዘርፍና ደረጃ የሚጠይቁት ጥቂት ኮሚቴዎች ናቸው ብለዋል፡፡
የኢኮኖሚ ጥቅም ወይም የውጭ አገር የጉዞ ዕድል በሚያስገኙ ቋሚ ኮሚቴዎች ላይ ለመመደብ ያለ ፍላጎትንና እነዚህን ዕድል የሚያስገኙ ቋሚ ኮሚቴዎችን ‹‹እርጥብ›› አድርጎ፣ ሌሎቹን ‹‹ደረቅ›› ብሎ የመፈረጅ አባዜ በምክር ቤት ውስጥ መኖሩን የተናገሩት አቶ አስመላሽ፣ ይኼንን አስተሳሰብ ማስወገድ ይገባል ሲሉ በጥብቅ አሳስበዋል፡፡
‹‹እዚህም እዚያም እንደዚህ ዓይነት አመለካከት ይነሳል፡፡ የፖለቲካ ኢኮኖሚው ነፀብራቅ ነው፡፡ ይኼንን ፍረጃ እናስወግዳለን፤›› ብለዋል፡፡
ኮሚቴ የሌለው ምክር ቤት ምንም ሊሠራ እንደማይችል በማስረዳት፣ አንዳንድ ቋሚ ኮሚቴዎች የውጭ ጉዞ ዕድል የሚፈጥሩ ቢሆንም ጉዞው የሚደረገው ለሥራ ነው ብለዋል፡፡ ‹‹ይኼ አመለካከት ችግር ያለባችሁ ችግሩን አስወግዱ፤›› ሲሉ አስጠንቅቀዋል፡፡