Saturday, June 10, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ለምስክርነት እንዲቀርቡ የተላለፈው ትዕዛዝ ታገደ

አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ለምስክርነት እንዲቀርቡ የተላለፈው ትዕዛዝ ታገደ

ቀን:

– ተጠርጣሪዎች ጠቅላይ ሚኒስትሩና የእንግሊዝ ኤምባሲ እንዲጠየቁ አመለከቱ

አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በሽብር ድርጊት ወንጀል ተጠርጥረው ለተከሰሱት ለእነ ዘመኑ ካሴ በመከላከያ ምስክርነት እንዲቀርቡ፣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ያስተላለፈውን ትዕዛዝ፣ ጠቅላይ ፍርድ ቤት አገደው፡፡

የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት፣ የሥር ፍርድ ቤት አቶ አንዳርጋቸው በመከላከያ ምስክርነት እንዲቀርቡ ሐምሌ 6 ቀን 2007 ዓ.ም. የሰጠውን ብይን ያገደው፣ የፌዴራል ማዕከል ዓቃቤ ሕግ ያቀረበውን ይግባኝ ሲመረምር የሚያስቀርብ ሆኖ በማግኘቱ መሆኑን ባስተላለፈው ትዕዛዝ አስታውቋል፡፡

አቶ አንዳርጋቸው በመከላከያ ምስክርነት በቆጠሯቸው በእነ ዘመኑ ካሴ የክስ መዝገብ (አሥር ሰዎች) የተካተቱት አቶ አሸናፊ አካሉ፣ አቶ ደህናሁን ቤዛ፣ አቶ ምንዳዬ ጥላሁንና አቶ አንሙት የኔዋስ ሲሆኑ እንዲመሰክሩላቸው የፈለጉትም፣ ተከሳሾቹ ኤርትራ ሄደው ከአቶ አንዳርጋቸው ትዕዛዝና መመርያ እንደተቀበሉ ዓቃቤ ሕግ የጠቀሰባቸውን ክስ እንዲያስረዱላቸው እንደነበር መዘገባችን ይታወሳል፡፡

በወቅቱ ከሳሸ ዓቃቤ ሕግ፣ ‹‹አቶ አንዳርጋቸው በተለያዩ ጊዜያት በተመሠረቱባቸው የወንጀል ክሶች በአንዱ ዕድሜ ልክ ሲፈረድባቸው በሌላኛው ሞት ተፈርዶባቸዋል፡፡ በመሆኑም ለምስክርነት ስለማይበቁና ሕግም ስለሚከለክላቸው ቀርበው ሊመሰክሩ አይገባም፤›› ብሎ ተቃውሞ ነበር፡፡ ፍርድ ቤቱ ግን የዓቃቤ ሕግን ክርክር ውድቅ በማድረግ አቶ አንዳርጋቸው ቀርበው እንዲመሰክሩ ሦስት ጊዜያት ትዕዛዝ የሰጠ ቢሆንም፣ ማረሚያ ቤቱ የተለያዩ ምክንያቶችን በመስጠት ሳያቀርባቸው ቀርቷል፡፡ በአራተኛው ቀጠሮ ‹‹አቶ አንዳርጋቸው ማረሚያ ቤት የሉም›› ብሎ ጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም. በደብዳቤ ገልጿል፡፡

ተከሳሾቹ በማረሚያ ቤቱ ምላሽ ተማረው የተወሰኑት ‹‹ብይን ይሰጠን›› ሲሉ፣ አቶ ደህናሁን ቤዛና አቶ ሞንዳዬ ጥላሁን ቀርበው መመስከር እንዳለባቸው በመግለጽ፣ ፍርድ ቤቱ ከውጭ አገር (የመን ሰንዓ) ይዞ ያመጣቸው ፀረ ሽብር ግብረ ኃይሉና ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዲጠየቁ ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው ጠይቀው ነበር፡፡

ጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም. በችሎት ያመለከቱትን አቤቱታ በማጠናከር፣ ጥቅምት 15 ቀን 2008 ዓ.ም. ጉዳያቸውን እያየው ለሚገኘው ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ጽፈዋል፡፡ ተከሳሾቹ ለፍርድ ቤቱ በጻፉት ደብዳቤ እንደገለጹት፣ አቶ አንዳርጋቸው በትውልድ ኢትዮጵያዊ ቢሆኑም በዜግነት እንግሊዛዊ በመሆናቸው፣ በኢትዮጵያ የእንግሊዝ አምባሳደር ጉዳያቸውን እንደሚከታተሉ ጠቁመዋል፡፡ በመሆኑም የእንግሊዝ ኤምባሲ፣ የፀረ ሽብር ግብረ ኃይሉና ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዲጠየቁ ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው አመልክተዋል፡፡

የሥር ፍርድ ቤት በተከሳሾቹ ደብዳቤ ላይ ብይን ከመስጠቱ በፊት ዓቃቤ ሕግ ያቀረበውን ይግባኝ የመረመረው ጠቅላይ ፍርድ ቤት፣ የሥር ፍርድ ቤት ትዕዛዝ እንዳይፈጸም በማገድ፣ ያስቀርባል ባለው ጉዳይ ላይ ብይን ለመስጠት ለኅዳር 8 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

አያሌ የውኃ “ጠርሙሶች”ን በጫንቃ

መሰንበቻውን በአይቮሪ ኮስት መዲና አቢጃን የምትኖር አንዲት ሴት፣ በሚደንቅ...

ወልቃይትን ማዕከል ያደረገው የምዕራባዊያን ጫና

በትግራይ ክልል የተከሰተው የዕርዳታ እህል ዘረፋ የዓለም አቀፍ ተቋማት...

ከቀጣዩ ዓመት በጀት ውስጥ 281 ቢሊዮን ብሩ የበጀት ጉደለት ነው ተባለ

ለቀጣዩ በጀት ዓመት ከቀረበው 801.65 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ በጀት...