የሕዝብ ግንኙነት ዋና ተልዕኮ በአገልግሎት ሰጪና ተቀባይ መካከል ሊኖር የሚገባውን የመረጃ ፍሰት ማቀላጠፍ ነው፡፡ የመንግሥት የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊነትና ተልዕኮ ደግሞ መጠኑና አድማሱ የሰፋ ነው፡፡ በተለይ በዚህ ዘመን የመንግሥት ቃል አቀባይ ከመሆን አልፎ የመንግሥት ዋነኛ የመረጃ ቋት ነው፡፡ የተለያዩ መንግሥታዊ መልዕክቶችን በማዘጋጀትና በማሰራጨት፣ በአገር አቀፍና በዓለም አቀፋዊ ክስተቶች ላይ የመንግሥት አቋም ማሳወቂያ ይፋዊ ተቋም በመሆንም ያገለግላል፡፡ ለአንድ አገር ደግሞ እንደ መስታወት ሆኖ ያገለግላል፡፡ በአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ሲታይ ግን፣ የመንግሥት የሕዝብ ግንኙነት አገልግሎት ከልማዳዊ አሠራር ያልተላቀቀ ነው፡፡
የመንግሥትን የሕዝብ ግንኙነት ሥራ ያቀላጥፋል ተብሎ በአዋጅ የተቋቋመው የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት፣ ከተሰጠው ሥልጣንና ተግባር አንፃር ሲገመገም ኃላፊነቱ ከፍተኛ ቢሆንም፣ ብዙ ሥራዎች ይቀሩታል፡፡ ምንም እንኳ ጽሕፈት ቤቱ የመንግሥትን የኮሙዩኒኬሽን ሥራ የሚመራ ቢሆንም፣ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊዎችና ሠራተኞችን አጠቃላይ እንቅስቃሴና አፈጻጸሞችን ቢከታተልም፣ የመንግሥት ተቋማትን ልዩ ልዩ ኹነቶች ለሚዘግቡ የሚዲያ ድርጅቶች መልዕክት አስተላላፊ መሆኑ ቢታወቅም፣ ከዚህ በላይ ሄዶ ማከናወን ያለበት በርካታ ሥራዎች አሉት፡፡ በተግባር ግን እየታዩ አይደሉም፡፡
ከጽሕፈት ቤቱ ጋር በቀጥታ ግንኙነት ያላቸው የመንግሥታዊ ተቋማት የሕዝብ ግንኙነት ክፍሎች የመረጃ አደረጃጀታቸውና ሥርጭታቸው አቅም ምን ያህል እንደሆነ አይታወቅም፡፡ ብዙዎቹ መንግሥታዊ የሕዝብ ግንኙነት ተቋማት እንኳን መረጃ አደራጅተው ለሚዲያ ሊሰጡ ይቅርና የተቋማቱን መረጃዎች ስለማወቃቸው በጣም ያጠራጥራሉ፡፡ በፕሬስና በመረጃ የማግኘት ነፃነት ሕግ ላይ በተቀመጠው መሠረት እንኳ መረጃ ለመስጠት የማይፈልጉ ብዙ ከመሆናቸውም በላይ፣ በመረጃ ሥርጭት ረገድ አድሎአዊነት ይታይባቸዋል፡፡ በጣም ውስን ከሆኑ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊዎች ወይም ሠራተኞች ውጪ፣ ብዙዎቹ በተለይ የግል ሚዲያዎችን ለማስተናገድ ያላቸው ፍላጎት እጅግ በጣም ቀዝቃዛ ነው፡፡ በደብዳቤ ሳይቀር ተጠይቀው እንኳ መረጃ ለመስጠት አይፈልጉም፡፡ በልማዳዊ አሠራር የተተበተቡ ናቸው፡፡
የመንግሥት የሕዝብ ግንኙነት ሥራ በጣም ከመሽመድመዱ የተነሳ፣ በአገሪቱ የተለያዩ ጉዳዮች ላይ ለሚዲያ ፍጆታም ሆነ ለምርምር መረጃ ሲጠየቅ ማግኘት ብርቅ እየሆነ ነው፡፡ መረጃ የማግኘት ነፃነት አዋጁ ከፀደቀ ከበርካታ ዓመታት በኋላ እንኳ፣ የመረጃ ቋታቸውን ያላደራጁና ከጊዜው ጋር ለመራመድ የተሳናቸው በርካታ መንግሥታዊ መሥሪያ ቤቶች አሉ፡፡ የሕዝብ ግንኙነት ሥራ ለአንድ ተቋም እንደ ትልቅ ገጸ በረከት መታየት ሲገባው፣ የሥራ ፈቶች መሰብሰቢያ እየመሰለ ነው፡፡ ይኼ በጣም የሚያሳፍር ነው፡፡ የኋላ ቀርነትና ከዘመኑ ጋር መራመድ አለመቻል ማሳያ ሆኗል፡፡
ጠንካራ የሕዝብ ግንኙነት ሥራ አንድን አገር በዓለም አቀፍ ደረጃ ከማስተዋወቁም በላይ፣ ኢንቨስተሮችንና ቱሪስቶችን በብዛት ለመሳብ ጠቃሚ ነው፡፡ አገሪቱ ያላትን የሰው ኃይል፣ የተፈጥሮ ዕምቅ ሀብት፣ የቱሪዝም መስህቦች፣ የኢንቨስትመንት አማራጮች፣ ባለችበት አኅጉርም ሆነ ክፍለ አኅጉር የገነባችውን ሰላምና መረጋጋት፣ ወዘተ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ማስታዋወቅ የሚቻለው ጠንካራ መንግሥታዊ የሕዝብ ግንኙነት ሲኖር ብቻ ነው፡፡ በደካማ የሕዝብ ግንኙነት ምክንያት ግን በተበላሸው የድሮ ገጽታዋ ነው አሁንም ስሟ የሚነሳው፡፡
መረጃ ኃይል ነው፡፡ መረጃ ሀብት ነው፡፡ መረጃ የበርካታ አጋጣሚዎችና ዕድሎች መገኛ ነው፡፡ መረጃን በአግባቡ ማሠራጨት ባለመቻል ብቻ አገር ትጎዳለች፡፡ ሕዝብ የማወቅ መብት አለው ሲባል፣ በአገሪቱ ውስጥ የሚከናወኑ ተግባራትን በንቃት በመከታተል የዕድገትና የብልፅግና መሪ ተዋናይ ለመሆን ያስችለዋል ማለት ነው፡፡ በዕውቀት ላይ የተመሠረተ ማንኛውም ውሳኔ ፍሬ የሚያፈራው መረጃ በተቀላጠፈ ሁኔታ ስለሚፈስ ነው፡፡ ይህ ባልሆነበት ግን ግራ መጋባትና መደናገር ብቻ ነው የሚኖረው፡፡ በመረጃ እጥረት ምክንያት ዜጎች የተሳሳተ ግንዛቤ ሊይዙ ይችላሉ፡፡ በሕዝብና በመንግሥት መካከል ሊኖር የሚገባው ጤናማ ግንኙነት ሊሻክር ይችላል፡፡ ከትክክለኛው ነባራዊ ሁኔታ ይልቅ አሉባልታ ገንኖ በመውጣት አደጋ ይፈጠራል፡፡ የሕዝብ ግንኙነት ሥራ ባልተጠናከረበት ወይም በሚድህበት ሥፍራ የሚገኘው ጥፋት ብቻ ነው፡፡
በመንግሥት ፖሊሲዎችና በተለያዩ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ግንዛቤ መፍጠር የሚያስችሉ ሕዝባዊ ውይይቶች በስፋት ከሌሉ፣ በመንግሥትና በሕዝብ መካከል መተማመን የሚፈጥሩ ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለባቸው አሠራሮች ካልታዩ፣ መንግሥታዊ ተቋማት በራፋቸውን ለሕዝብና ለሚዲያ ክፍት ካላደረጉ፣ የመንግሥት ባለሥልጣናት ለሕዝብ ወቅታዊ ጥያቄዎች ምላሽ ካልሰጡ፣ የሕዝብ አቤቱታዎችና ቅሬታዎች በግልጽ ቀርበው ካልተሰሙ፣ ወዘተ መንግሥት እንዴት የሕዝብ ግንኙነት አለኝ ብሎ ያምናል? እስካሁን የተመጣበት ጉዞ ተመርምሮ የሕዝብ ግንኙነት ገጽታው ካልተለወጠ በስተቀር፣ አሁን በሚታየው ሁኔታ የትም መድረስ አይቻልም፡፡
መንግሥት የአገሪቱን ገጽታ ለመለወጥ እየሠራሁ ነው ሲል፣ ይህ ገጽታ እንዴት መተዋወቅ እንዳለበት በቅጡ ሊረዳ ይገባዋል፡፡ ፖስተሮችንና በራሪ ወረቀቶችን በየኤምባሲው መበተንና ይህንን ደካማ አሠራር በአፈጻጸም ሪፖርት እያቀረቡ መኩራራት ጊዜ ያለፈበት እንደሆነ መታወቅ አለበት፡፡ መንግሥት በሩን ገርበብ አድርጎ የአገር ውስጥና የውጭ ሚዲያዎችን በስፋት መጋበዝ አለበት፡፡ ጥሩ የተሠራው እየተበረታታ ጥሩ ያልሆነው ደግሞ እንዲነቀፍ ወይም እንዲተች ተነሳሽነቱን መውሰድ ይኖርበታል፡፡ ሕዝቡም እውነታው ሳይጋነንና ሳይንኳሰስ የማወቅ መብት እንዳለው ሲረጋገጥ፣ የግልጽነትና የተጠያቂነት መንፈሱም በዚያው ደረጃ ይዳብራል፡፡ በር በተዘጋጋ ቁጥር ግን ሐሰተኛ ሪፖርቶችና የማያሳምኑ የፕሮፓጋንዳ ወሬዎች ይበዛሉ፡፡ በዚህ ደግሞ ማንም አይጠቀምም፡፡ ይህ ልማዳዊ አሠራር በቃ መባል አለበት፡፡
የሕዝብ ግንኙነት ሥራ በመርህ እንጂ በገጠመኝ የሚከናወን አይደለም፡፡ መንግሥት በሕዝብ ግንኙነት ተቋሙ ተጠቃሚ ካልሆነ፣ ከሕዝብ ጋር እንዴት ነው የሚገናኘው? የመረጃ ፍሰቱ በሁለቱም ወገን በተቀላጠፈ መንገድ እንዲካሄድ ካልተደረገ ሕዝብም መንግሥትም ይጎዳሉ፡፡ መንግሥት እጅ ያለ መረጃ ወደ ሕዝቡ፣ ሕዝቡ ዘንድ ያለ መረጃ ደግሞ ወደ መንግሥት ፍትሐዊ በሆነ መንገድ መተላለፍ አለበት፡፡ አቶ እከሌ ወይም ወ/ሮ እከሊት ደስ ሲላቸው፣ ወይም ሲከፋቸው እየተባለ እንደ አየሩ ፀባይ የሚለዋወጥ ከሆነ ከመርህ ይልቅ ገጠመኝ ይሆናል፡፡ ይህ ደግሞ ኋላቀርነት ነው፡፡
የመንግሥትን የሕዝብ ግንኙነት ሥራ የሚመራው የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት በቅርብ በተሾሙት አዲስ አመራሮቹ አማካይነት ለለውጥ ይትጋ፡፡ በሕዝብና በመንግሥት መካከል ድልድይ ይሁን፡፡ ሁሉንም የሚዲያ ተቋማት በእኩልነት ያስተናግድ፡፡ ከልማዳዊና ከቀርፋፋ አሠራሮች ተቋሙን በማላቀቅ ዘመኑ በሚጠይቀው መሥፈርት መሠረት ተግባሩንና ኃላፊነቱን ይወጣ፡፡ አገሪቱ አሁን ባለችበት ደረጃ በሚመጥናት ገጽታዋ በስፋት ያስተዋውቃት፡፡ የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያዎችን አቅም ያጎልብት፡፡ ከነበሩበት ደካማ አሠራር ያውጣቸው፡፡ ከዘመኑ ጋር እንዲራመዱ ያብቃቸው፡፡ መረጃ የመደበቅ አጉል ባህሪያቸውን ይለውጥ፡፡ አዲሱ አመራር ለዘመናዊ የሕዝብ ግንኙነት አስተምህሮዎች በሩን በመክፈት፣ ልማዳዊውን አሠራር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንዳይመለስ ያድርገው፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ግን የመንግሥት የሕዝብ ግንኙነት ሥራ አፈጻጸም ተከድኖ ይብሰል ነው የሚባለው፡፡ ምክንያቱም ከልማዳዊ አሠራር አልተላቀቀምና!