– ከ1948 ዓ.ም. ጀምሮ ተወዳጅነትን ያተረፉ ሥራዎች ለዕይታ ይበቃሉ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር የ60ኛ ዓመት ክብረ በዓሉን አንጋፋዎቹን በመዘከር እንደሚያከብር አስታወቀ፡፡ ከጥቅምት 29 እስከ ኅዳር 5 ቀን 2008 ዓ.ም. በሚካሄደው ሥነ ሥርዓት በተለያዩ የኪነ ጥበብ ዘርፎች ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ የቴአትር ቤቱ ባለሙያዎች ምስጋና ይቀርባል፡፡
‹‹ቴአትር ቤቱ ዛሬ ለደረሰበት ደረጃ ትልቅ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ባለሙያዎች ለልፋታቸው ዕውቅና ይሰጣቸዋል፤ ዛሬ ብዙዎች እዚህ የደረሱት እነሱ ለፍተው ባቆዩት መድረክ በመሆኑ ስለልፋታቸውም እናከብራቸዋለን፤›› ያሉት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ተስፋዬ ሽመልስ፣ ለስድስት ቀናት በሚቆየው የአከባበር ሥነ ሥርዓት ከቴአትር ቤቱ አንጋፎች ጎን ለጎን ወጣት የኪነ ጥበብ ባለሙያዎችም ተሳታፊ እንደሚሆኑ ገልጸዋል፡፡
ቴአትር ቤቱን ለዓመታት ያገለገሉና በርካታ ኪነ ጥበባዊ ሥራዎችን ያበረከቱ ባለሙያዎችን ከመዘከር በተጨማሪ፣ በዓሉ በልዩ ልዩ መንገድ ይከበራል፡፡ ከነዚህ መካከል ቀደምትና በብዙ ሕዝብ ተወዳጅነትን ያተረፉ ኪነ ጥበባዊ ሥራዎች ዳግም ለዕይታ የሚቀርቡበት መድረክ መዘጋጀቱ ይጠቀሳል፡፡ ከ1948 ዓ.ም. ጀምሮ በቴአትር ቤቱ መድረክ ከቀረቡ ሥራዎች የተመረጡት ተካተዋል፡፡
የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች የሚሳተፉበት የፓናል ውይይትና የቴአትር ቤቱን ጉዞ የሚያስቃኝ ዐውደ ርዕይም በዝግጅቱ ተካተዋል፡፡ ቴአትር ቤቱ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ በርካታ ውጣ ውረዶችን ማለፉን የጠቀሱት አቶ ተስፋዬ፣ የስድስት አሠርታት ጉዞው በዐውደ ርዕዩ እንደሚንፀባረቅ ገልጸዋል፡፡ ሌላው የሙዚቃ ዝግጅት ሲሆን፣ የቴአትር ቤቱ ሙዚቀኞችን እንዲሁም ከፖሊስ ኦርኬስትራና ክብር ዘበኛ የተውጣጡ ባለሙያዎችን ያካትታል፡፡
ከክብረ በዓሉ ጋር በተያያዘ ትኩረት የተሰጣቸው ጉዳዮች ቴአትር ቤቱ በትውፊታዊ ትውን ጥበባት ዙሪያ የሚያደርገው እንቅስቃሴና አዲስ የሚገነባው ቴአትር ቤት ናቸው፡፡ ግንባታው በያዝነው ዓመት እንደሚጀመር የሚጠበቀውና 500 ሚሊዮን ብር በጀት የተመደበለት ቴአትር ቤት፣ አዲስ አበባ እንደ አፍሪካ መዲናነቷ ከሚያስፈልጓት ግዙፍ የኪነ ጥበብ መድረኮች አንዱ እንደሚሆን አቶ ተስፋዬ እምነታቸውን ገልጸዋል፡፡
በተያያዥም የብሔር ብሔረሰቦች ባህልና ታሪክ የሚንፀባረቅባቸው ትውፊታዊ ተውኔቶች ቴአትር ቤቱ ትልቅ ቦታ እንደሚሰጣቸው ሥራ አስኪያጁ ገልጸው፣ አሁን እየተሠራ ካለው በበለጠ ሌሎም ተውኔቶች ለመድረክ እንደሚበቁ ተናግረዋል፡፡
የ60ኛ ዓመት ክብረ በዓሉ ቴአትር ቤቱ ራሱን የሚፈትሽበት እንደሚሆንም ከገለጻቸው ለመረዳት ተችሏል፡፡ ያለፉት ዓመታት ደካማና ጠንካራ ጎኖችን በመንቀስ ለቀጣዩ ጉዞ መሠረት የሚጣልበት እንደሚሆንም ተናግረዋል፡፡
ቴአትር ቤቱ እንቅስቃሴውን ከሚያጠናክርባቸው መካከል የቴአትር ቤቱ ባለሙያዎች በተለያዩ አገሮች እየተዘዋወሩ የኢትዮጵያን ባህል የሚያስተዋውቁበት አቅጣጫ ይጠቀሳል፡፡ ባለሙያዎቹ ወደ አፍሪካ አገሮች እንዲሁም ሌሎች አህጉሮች በመጓዝ የተለያዩ ኪነ ጥበባዊ ሥራዎችን የሚያቀርቡ ቢሆንም፣ ለወደፊት የበለጠ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተገልጿል፡፡
ቴአትር ቤቱ የሚያዘጋጃቸው የሙዚቃ ትርዒቶች በበዓላት ብቻ መወሰናቸው የሚጠቀስ ሌላ ነው፡፡ እንደ ሥራ አስኪያጁ ገለጻ፣ የሙዚቃ ሥራዎች ለዐውደ ዓመት ብቻ ሳይሆን በሌሎችም ጊዜያት ለሕዝቡ የሚደርሱበት መንገድ ይመቻቻል፡፡ በቴአትር ቤቱ የሚቀርቡ ቴአትሮች ተደራሽነታቸው እንዲሰፋም ከአዲስ አበባ ውጭ የሚታዩበት ዕድል ይፈጠራል፡፡