የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን የመርካቶ ቁጥር ሁለት ቅርንጫፍ ከፍተኛ ኦዲተርና ሦስት ኦፊሰሮች ጉቦ በመቀበል ከባድ የሙስና ወንጀል ጥቅምት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ተከሰሱ፡፡
ተከሳሾቹ የግል ተበዳይ አቶ ዮሐንስ ጥጋቡ የተባሉትን በጨርቃ ጨርቅ ንግድ የተሰማሩ ነጋዴ፣ ‹‹ግዢና ሽያጭ አልተጣጣመም፣ በቆጠራ የሚፈጠረውን ጉድለት ባላንስ እናደርግልዎታለን፤›› በማለት ሁለት ሚሊዮን ብር ጉቦ መጠየቃቸውን፣ የፌዴራል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የመሠረተው ክስ ያስረዳል፡፡
የጉቦ መቀበል ከባድ የሙስና ወንጀል ክስ የተመሠረተባቸው የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ሠራተኞች አቶ መሠረት ታደሰ የተባባሪዎች ምልመላና ሥልጠና ኦፊሰር፣ አቶ አበበ ደቦ ቡልቱሜ የኢንቬስትጌሺን ከፍተኛ ኦዲተር፣ አቶ አያና ጋሩማ የኢንተለጀንስ አሰባሰብ ጀማሪ ኦፊሰር፣ አቶ ሀብታሙ ታደሰ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አምቦ ቅርንጫፍ ኦፊሰርና አቶ አብዲሳ ደቦ ቡልቱሜ የባንኩ የሰው ኃይል አስተዳዳር ባለሙያ ናቸው፡፡
ተከሳሾቹ ከላይ የተጠቀሰውን ሁለት ሚሊዮን ብር ጉቦ የጠየቋቸው አቶ ዮሐንስ ባለመስማማታቸው፣ አንደኛ ተከሳሽ አቶ መሠረት አደራዳሪ መስሎ ነጋዴውን በመቅረብ፣ ‹‹ኦዲተሮቹ ብዙ ገንዘብ መቀበል ስለለመዱ አንተ ሁለት መቶ ሺሕ ብር ብትሰጣቸው ምንም አይደለም፤›› ቢላቸውም ተበዳዩ አለመስማማታቸውን ክሱ ይጠቁማል፡፡
የነጋዴውን አለመስማማት የተረዱት ተከሳሾች ያላቸውን ዕቃ ብዛት በጽሑፍ እንዲያቀርቡ ጠይቀዋቸው እንደሰጧቸው የሚገልጸው የዓቃቤ ሕግ ክስ፣ በዝርዝር የሰጡት ዕቃ ጉድለት እንደሚያመጣና ጠቅላላ የዕቃውን ብዛት እንዳልሰጧቸው ሲገልጹላቸው፣ ተበዳዩም ካልተቆጠረ እንደማይታወቅ በመግለጽ እንደተከራከሯቸው ክሱ ያስረዳል፡፡
የግል ተበዳዩን በተለያየ መንገድ ስላስጨነቋቸው ግንቦት 15 ቀን 2007 ዓ.ም. ለአንደኛ ተከሳሽ አራት መቶ ሺሕ ብር መስጠታቸውን፣ በድጋሚ በተለያዩ ቀናት በድምሩ ሁለት መቶ ሺሕ ብር መስጠታቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡ ተከሳሾቹ ሰነዱን ሲመረምሩ ተበዳዩ 12 ሚሊዮን ብር የሚደርስ ከፍተኛ ዕዳ እንደሚመጣባቸው ማወቃቸውን በመንገር፣ ተበዳዩን በማስጨነቅ አራት መቶ ሺሕ ብር እንዲሰጧቸው ማድረጋቸውን፣ በአጠቃላይ በተለያዩ ቦታዎች በመቅጠር ተከሳሾች ከተበዳይ 1.2 ሚሊዮን ብር መቀበላቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡
አቶ መሠረት የተባለው ተከሳሽ ጉቦ በመቀበል ያገኘውን ገንዘብ ለመሰወርና ለመደበቅ፣ አምቦ ከተማ ለሚኖረውና ለአራተኛ ተከሳሽ ወንድሙ አቶ ሀብታሙ አምስት መቶ ሺሕ ብር መስጠቱ በክሱ ተጠቅሷል፡፡ አቶ ሀብታሙ የገንዘቡ አመጣጥ ሕገወጥ መሆኑን እያወቀ፣ አምቦ ከተማ ቀበሌ 02 ውስጥ ስፋቱ 200 ካሬ ሜትር ቦታ በ140 ሺሕ ብር በእናቱ ስም እንደገዛለት፣ 100 ሺሕ ብር ደግሞ ለሌላ ግለሰብ እንዲያስቀምጥለት መስጠቱን ክሱ ያብራራል፡፡ አቶ አበበ ደግሞ ለአቶ አብዲሳ 287,900 ብር ሲሰጠው ገንዘቡን መሬት ውስጥ መቅበሩን፣ አቶ አያና የተባለው ሦስተኛ ተከሳሽ ደግሞ በአምቦ ከተማ 400 ካሬ ሜትር መሬት በ80 ሺሕ ብር በመግዛት በሕገወጥ መንገድ የተገኘን ገንዘብ ሕጋዊ ለማሰመሰል መሥራታቸውን ክሱ ያብራራል፡፡
በአጠቃላይ ተከሳሾቹ ፈጽመዋል በተባለው ጉቦ መቀበል ከባድ የሙስና ወንጀልና በወንጀል የተገኘን ገንዘብ ሕጋዊ አስመስሎ ማቅረብ የሙስና ወንጀል የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ክስ መሥርቶባቸዋል፡፡